03/05/2026
የአማራ ሊግ ውድድር በደሴ ከተማ ተጀመረ፣
በታሪካዊቷ የደሴ ከተማ የሚካሄደው የ2018 ዓ.ም የአማራ ሊግ የእግር ኳስ ውድድር በይፋ ተጀምሯል። ከሚያዚያ 25 እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ለሁለት ሳምንታት በሚቆየው በዚህ ክልላዊ መድረክ ላይ አስር ክለቦች በሁለት ምድብ ተከፍለው ብርቱ ፉክክር እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።
ውድድሩ በክልሉ ያለውን የስፖርት እንቅስቃሴ ከማነቃቃት ባለፈ በፀጥታ ችግሮች ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን ማህበራዊ ትስስር ዳግም ለማጠናከር ትልቅ ተስፋ ሰንቋል።
የደሴ ከተማ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይድ አራጋው ፤ ከተማ አስተዳደሩ ውድድሩ በሰላም ተጀምሮ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን የሜዳና የሎጂስቲክስ ዝግጅት በከፍተኛ ጥንቃቄ የተከናወነ ሲሆን፣ ውድድሩ ለደሴ ከተማ ልዩ ትርጉም እንዳለው የገለጹት ኃላፊው፣ በሂደቱ የሚገኘው ተሞክሮ በቀጣይ ከተማዋ ለምታስተናግዳቸው ክልላዊና አገር አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች ልምድ የሚወሰድበት መሆኑን ጠቁመዋል።
በአማራ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ የስፖርት ማህበራት ስልጠናና ውድድር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ሉሌ ፤ ባለፉት ዓመታት በክልሉ በነበረው የሰላም እጦት ምክንያት የስፖርቱ ዘርፍ ክፉኛ ተጎድቶ መቆየቱን አስታውሰዋል። ይሁን እንጂ ይህ ውድድር ከሦስት ዓመታት መቋረጥ በኋላ ዳግም መጀመሩ ለተጫዋቾችና ለስፖርት ቤተሰቡ ትልቅ የምስራች መሆኑን ገልጸዋል።
ዳይሬክተሩ አክለውም መሰል መድረኮች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራትና ብቁ ክለቦችን ለመገንባት ያላቸው ፋይዳ የጎላ መሆኑን በመጥቀስ፣ የክልሉ መንግስት ዘርፉን ለመደገፍ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በአጠቃላይ በክልሉ በሁለት ምድብ ተከፍለው ሲወዳደሩ ከቆዩ ሀያ ክለቦች መካከል የማጣሪያ ጨዋታዎች ተካሂደው "የአሸናፊዎች አሸናፊ" የሚለየው ክለብ ክልሉን በመወከል በአገር አቀፍ ደረጃ በሚካሄደው ውድድር ላይ ተሳታፊ ይሆናል።
ለዚህ ውድድር ዝግጅታቸውን ሲያደርጉ የቆዩ ተጫዋቾች በሰጡት አስተያየት፣ ውድድሩ ዳግም መጀመሩ የአካል ብቃትና የክህሎት ደረጃቸውን ለመለካት ዕድል ከመስጠቱም በላይ፣ በተለያዩ አካባቢዎች ከሚመጡ ስፖርተኞች ጋር የእርስ በርስ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር እንደሚያግዛቸው ገልጸዋል።
ዘጋቢ:- ሰልሀዲን ሰይድ
ደሴ፣ ሚያዚያ 25/2018 ዓ.ም (አሚኮ ደሴ)