01/10/2025
ግሸን ደብረ ከርቤ
የግሸን ደብረ ከርቤ አንድ ጠባብ በር ብቻ ባለው አምባ ላይ የምትገኝ ድንቅ ሀይማኖታዊ መዳረሻ ናት፡፡ ከደሴ ከተማ ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ 82 ኪ/ሜ ርቀት ላይ የምትገኘውንና ዳግማዊት እየሩሳሌም በመባል የምትታወቀው ግሸን ደብረ ከርቤ ይሄን ስሟን ከመያዟ በፊት በተለያዩ ስሞች ትጠራ እንደነበረ በታሪክ ተመዝግቧል፡፡ የግሸን አምባ ለዘመናት የእምነት እና የአስተዳደር ቦታ ሆኖ በመቆየቱ የስም መቀያየሩ በጊዜው ከነበረው ነባራዊ ሁኔታ ጋር ይያያዛል፡፡
የግሸን አምባ ለመጀመሪያ ጊዜ ለቤተ ክርስቲያን መስሪያ ቦታነት የተመረጠው በአፄ ካሌብ ዘመነ መንግስት አባ ፈቃደ ክርስቶስ በተባሉ አባት ነበር፡፡ እኒሁ አባት በንጉሡ ይሁንታ በ517 ዓ.ም የመጀመሪያውን ቤተ ክርስቲያ በአምባው ላይ ሰርተዋል፡፡ በዘመኑ አባ ፈቃደ ስላሴ የሰሩት የእግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያንን ሲሆን አሰራሩም በገጠሩ የአማራ ክልል አካባቢ በተለመደው የሳር ክፍክፍ ነበር፡፡
በንጉሥ/ቅዱስ ላሊበላ ዘመነ መንግስት የግሸን አምባ ደብረ እግዚአብሔር ተብሎ እንዲጠራ ሆኖ ነበር፡፡ ንጉሡ ይሄን ስያሜ እንዲሰጡ ያደረጋቸው የእግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን በአንባው መገኘቱ እንደሆነ የሀይማኖት አባቶች ይናገራሉ፡፡ ደብረ እግዚአብሔር የተባለው የግሸን አምባ ብዙም ሳትቆይ በንጉሥ ይኩኖአምላክ ዘመነ መንግስት ድጋሚ ስያሜው ተቀይሯል፡፡ በዘመኑ አምባው ከእምነት ቦታነቱ በተጨማሪ የአስተዳደር ቦታ ሆኖ በመመረጡ አካባቢው የነገሥታት ልጆች መኖሪያ መሆኑንን ለማመልከት ደብረ ነገሥት የሚል ስያሜ ተሰጥቶት ነበር፡፡
ግሸን አሁን የምትጠራበትን ግሸን ደብረ ከርቤ የሚለውን ስያሜ ያገኘችው በአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመነ መንግስት ነው፡፡ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ ግማደ መስቀሉን ከሲናር ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት በዚህ አምባ ሲያሳርፉ አምባው የመስቀሉ መገኛ ነው በማለት ደብረ ከርቤ ብለው ሰይመውታል፡፡ ከዚያ ዘመን ጀምሮ የግሸን አምባ ግሸን ደብረ ከርቤ በመባል እየተጠራ ይገኛል፡፡
ግሸን ደብረ ከርቤን ከአፄ ካሌብ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድረስ በርካታ ነገሥታት ልዩ ትኩረት ይሰጧት ነበር፡፡ በገዳሟ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን በልዩ ሁኔታ ለመስራት ቅዱስ ላሊበላ፣ አፄ ይኩኖአምላክ፣ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ፣ እማሆይ ዕሌኒ፣ አፄ ሰርፀ ድንግል፣ አድያም ሰገድ ኢያሱ፣ ራስ አሊ፣ አፄ ተክለ ጊዮርጊስ፣ ዳግማዊ ምኒሊክ፣ እቴጌ መነን፣ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወዘተ በዘመነ መንግስታቸው ግሸንን በማደስ እና ዘመኑ የሚጠይቀውን ነገር ሁሉ በማሟላት እንደተሳተፉ በታሪክ ተመዝግቧል፡፡
በግሸን አምባ ከግሸን ደብረ ከርቤ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የእግዚአብሔር አብ፣ የቅዱስ ሚካኤል፣ የቅዱስ ገብርኤል እና የቅዱስ ኡራኤል አብያተ ክርስቲያናት ይገኛል፡፡
ዛሬ መስከረም 21 በግሸን ልዩ የክብረ በዓል ቀን ነው፡፡ የብዙኃን ማርያም እና የኢየሱስ ክርስቶስ ግማደ መስቀል ግሸን አምባ እግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን የገባበትን ቀን ታሳቢ በማድረግ በሚከበረው በዚህ ታላቅ ዓመታዊ ክብረ በዓል ለመሳተፍ በርካታ ምዕመናን በቦታው ተገኝተዋል። የግሸን ክብረ በዓል ከአጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን ጀምሮ ለረጅም ዓመታት በመከበሩ፣ በርካታ ምዕመናን በማሳተፉ እና በድምቀቱ በኢትዮጵያ ከሚከናወኑ ቀዳሚ ሀይማኖታዊ በዓላት አንዱ ለመሆን ችሏል።
መልካም በዓል!