09/05/2026
በባህር ዳር ከተማ ሰዎችን በማገት የተሳተፉ የወንጀል ቡድን አባላትና የመንግስት ተሽከርካሪ በቁጥጥር ስር ዋሉ።
በባህር ዳር ከተማ በሰዎች ላይ እገታ በመፈፀም፣ ገንዘብ በመጠየቅና በመቀበል ወንጀል የተሳተፉ የወንጀል ቡድን አባላትና ለወንጀሉ መፈፀሚያነት የዋለ ተሽከርካሪ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ፖሊስ አስታወቀ።
ተጠርጣሪውቹ ታጋቾቹን አፍነው በመውሰድ ለ11 ቀናት አግተው ያቆዩዋቸው ሲሆን፤ በወቅቱ ታጋቾቹን ለመልቀቅ 3 ሚሊዮን 370 ሺህ ብር ከቤተሰቦቻቸው በመጠየቅና ገንዘቡ ከተከፈላቸው በኋላ እንዲለቀቁ ማድረጋቸውን የምርመራ መረጃው ያመላክታል።
የመምሪያው የወንጀል ምርመራ ምክትል መምሪያ አዛዥ ኮማንደር መኳንንት አድማስ እንደገለጹት ሰኔ 29 ቀን 2018 ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ ቀበሌ 14 (ኤፍራታ) አካባቢ ነዋሪና ነጋዴ የሆኑ ሶስት ግለሰቦች በራሳቸው ተሽከርካሪ ወደ ስራ ቦታቸው በመሄድ ላይ እያሉ በወቅቱ ማንነታቸው ባልታወቁ አካላት እገታ ተፈፅሞባቸዋል ብለዋል።
ተጠርጣሪዎቹ ታጋቾቹን በመንግስት ተሽከርካሪ አፍነው በመውሰድ ለ11 ቀናት አግተው ማቆየታቸውን ያስረዱት ኮማንደር መኳንንት የወንጀሉ አደራጆች እና ተሳታፊዎች በቅንጅት የሰሩ መሆኑን አክለው አስታውቀዋል።
በተደረገው ጥብቅ ክትትልም 1ኛ. ወንጀሉን በዋናነት ያስተባበረው አብርሃም ጫኔ የተባለ በቀበሌ 06 የኤሌክትሮኒክስ ሱቅ ባለቤት፤
2ኛ. ተሽከርካሪን ለወንጀል ያዋለ መለሰ ጌትነት የተባለ አሽከርካሪ ግለሰብ፤
3ኛ. ታጋቾቹን ደብቆ ያቆየውና ወንጀሉን የሸፈነው በቀበሌ 14 እንዘግድብ አካባቢ የሚገኝ ህንፃ አስተዳዳሪ (170 ሺህ ብር ክፍያ በመቀበል ወንጀሉን ያደባበሰ)፤
4ኛ. አበበ ጌቴ፣ ከአዲስ አበባ የተሳተፈ ተባባሪን ጨምሮ እስከ 870 ሺህ ብር በባንክ አካውንት ገቢ በማድረግ ረገድ የተሳተፉ አባላት፤ በአጠቃላይ አምስት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ነው ኮማንደር መኳንንት ያስታወቁት።
በተጨማሪም ለወንጀሉ ማስፈፀሚያነት የዋሉ አንድ ማካሮቭ እና አንድ ክላሽንኮቭ የጦር መሳሪያዎች ከነተሽከርካሪው መያዛቸውን ገልጸዋል።
የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ የመንግስት ተቋማት ለስራ የተመደቡላቸውን ተሽከርካሪዎችና አሽከርካሪዎች ላይ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር ሊያደርጉ እንደሚገባ ያሳሰበ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት ቀሪ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል እና የምርመራ መዝገቡን አጠናቆ ለፍርድ ቤት ለማቅረብ የሚያስችል ጥብቅ የምርመራ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቋል።