07/15/2025
የምወዳት የማከብራት እህቴ ተወርቶም አያልቅም የሷ ትጋት።
ለኪነ ጥበብ የተፈጠረ ቤተሰብ።
| አዜብ ለኪነ-ጥበብ ከፍተኛ ፍቅር አላት። ኪነ ጥበብ ለእሴት መጎልበት እና በስነ-ምግባር የታነጸ ትውልድ ለመገንባት ትልቅ አስተዋፅዖ እንዳለው ታምናለች። በሀገራችን የኪነ ጥበብ እድገት የበኩሏን አስተዋጽዖ ለማበርከትም ከዛሬ 25 ዓመት በፊት ባቋቋመችው ማስተር የቪዲዮግራፊና የፎቶግራፊ ማሰልጠኛ ተቋም፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን አሰልጥና የሙያ ባለቤቶች እንዲሆኑ አድርጋለች። አዜብ ሰዎች ጠንክሮ በመስራት እና ለዓላማ በመኖርመሆን የሚሹትን ሁሉ መሆን እንደሚችሉ ታምናለች። አዜብ አስገራሚ ተምሳሌት እና የጠንካራ ስነ ልቦና ባለቤትም ናት።
አዜብ ከሰባት አመት በፊት ኑሮዋን በሀገረ አሜሪካ ካደረገች በኋላ፣ ከልጅነቷ ጀምራ ትወደው ወደ ነበረው የአበባ ንግድ በመግባት፣ የአበባ ስራ ላይ ተሰማርታ፣ በቨርጂኒያ ግዛት ፣ በአርሊንግተን ካውንቲ "እዚ ፍላወር" የተባለ የአበባ መሸጫ መደብር ከፍታለች። አዜብ የዛሬ አራት አመት የአሜሪካው 46ኛው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን በዓለ ሲመታቸውን ሲያከብሩ፣ በነጩ ቤተ መንግስት ዉስጥ ተገኝታ፣ ለበዓለ ሲመታቸውከፊሉን የአበባ ማስዋብ ስራ ያከናወነችው እርሷ ነበረች። እዚ ፍላወር የአበባ መሸጫ መደብር ብቻ ሳይሆን፣ ስለ አበባ ማስዋብ ስልጠና ለመስጠት ተማሪዎችን መመዝገብ ጀምሯል።
አዜብ ከበደ ባለ ትዳርና የሁለት ልጆች እናት ስትሆን፣ ለሰባት አመታት ያህል ከልጆቿ እና ከባለቤቷ ጋር በስደት ምክንያት ተለያይተው ከቆዩ በኋላ ፣ ዘንድሮ ወደ አሜሪካ በመምጣታቸው አብረው ይኖራሉ።
የወ/ሮ አዜብ ቤተሰቦች በኢትዮጵያ ኪነ ጥበብ ዉስጥ የላቀ ተሳትፎ ያበረከቱ ናቸው። ሁለቱ ወንድሞቿ ወንድወሰን ከበደ እና ቢኒያም ከበደ ጋዜጠኞች ናቸው። ወንድወሰን ከበደ በኢትዮጵያ እና በአሜሪካ ትልልቅ የኪነ ጥበብ የንግድ ትርኢቶችን በማዘጋጀት ይታወቃል፣ ሬዲዮ ፋና ውስጥም ለረጅም ጊዜ ጋዜጠኛ ሆኖ አገልግሏል። ቢኒያም ከበደም ጉምቱ ጋዜጠኛ ከመሆኑም በላይ፣ በኢትዮጵያ ብቸኛ የሆነውና የ24 ሰዓት ስርጭት አገልግሎት የሚሰጠው፣ የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቪዥን ጣቢያ መሰራችና ባለቤት ነው።
ቤተሰቡ ለኪነ ጥበብ የተፈጠረ ነው፣ እናታቸው ወ/ሮ አለሚቱ የመጀመሪያውና ፋና ወጊው የዲያና የውበት ማስልጠኛ ተቋም ባለቤት ናቸው፣ በነገራችን ላይበዚህ የውበት ማሰልጠኛ ተቋም ዉስጥ የአርቲስት ቴዲ አፍሮ ባለቤት፣ አምልሳት ሙጬ ተማሪ ነበረች፣ ተቋሙን አሁን ላይ ፀደይ ከበደ ትመረዋለች። በኢትዮጵያ ከአርት ስኩል ቀጥሎ ብቸኛውና የመጀመሪያው የስነ ጥበብ ተቋም፣ አቢሲኒያ የስነ ጥበብ ማሰልጠኛ ተቋምም የዚሁ የዘርፈ ብዙ የስነ ጥበብ አፍቃሪ ቤተሰብ ውጤት ነው፣ ገነት ከበደ ይህንን ተቋም ታስተዳድረዋለች።
ተቋሙ በርከት ያሉ የስነ ጥበብ ፍላጐት ያላቸው ወጣቶችን በስዕል ፣ በቅርፃ ቅርፅ ፣ በዳንስ እና በቲያትር መስክ ስልጠናወችን እንዲያገኙ አድርጓል። ገነት ከበደም በኢትዮጵያ ዉስጥ በኪነ ጥበብ እድገት ላበረከታቸው ላቅ ያለ አስተዋፅኦ፣ የዘንድሮው አመት የአመቱ የበጎ ሰው ሽልማት ተሸላሚ ለመሆን በቅታለች። ይህንን ሽልማት ከ5 ዓመት በፊትም ቢኒያም ከበደ ተሸልሞታል። ወ/ሮ አዜብ ከበደ ለኢትዮጵያ ፊልም እድገት ላበረከቱት አስተዋፅዖም የዘንድሮው ጉማ አዋርድ የህይወት ዘመን ተሸላሚ ሆነዉ ተሸልመዋል።
ይህ ቤተሰብ ባለፉት 30 አመታት ለኢትዮጵያ ኪነ ጥበብ እድገት ላበረከተው አስተዋጽዖ ሊመሰገን እና ሊወደስ ይገባዋል። በሀገረ ካናዳ ኑሮውን ያደረገው ሌላው ወንድማቸው ዮሃንስ ከበደም ከእህቶቹ ጋር በመሆን ማስተር እና አቢሲኒያ ተቋሞችን በማስተዳደር ጉልህ ሚና ነበረው::
ታዋቂውጋዜጠኛ ፡ደራሲ፡ እናየታሪክ ተመራማሪ ንጉሴ አየለ ተካ ፡ከኮሎምበስ ፣ ኦሀዮ ስለ አዜብ ከበደ የፃፈውን አጋርቻችሁ እሰናበታችኋለሁ።
ኮራሁባችሁ!
°°°°°°°°°°°°
የአበቦች ማራኪ እልፍኝ ከሆነው ከአዚ ፍላወርስ (Azi Flowers) አራት ግድግዳ ውስጥ፣ ቋንቋ የተማሩ፣ ፍቅር የሚዘሩና ለዓይን የሚያበሩ አበቦች ብቻ አይደለም ያሉት።
ጥረት የቤቱን አድማስ ያሳያል። ከመሀል ወ/ሮ አዜብ ከበደ፣ በራስ መተማመንና የሙያ እውቀት የምትሰጣቸው ማብራሪያዎች፣ እርጋታዋና የቃላት አመራረጧ ገና ከመነሻው ያለፈ ታሪኳን እንድንጠይቅ ያደርጋል። ስለ አበባ ብዙም እውቀት የሌለኝ ሰው፣ እርሷና ድርጅቷን እንግዳ አርጎ ያቀረበው "የእኛ ሰው በአሜሪካ" በተሰኘው የቪዲዮ ስርጭት ላይ ተመለከትኩ።
ስጨርስ "ምነው የኒው ዮርክ ታይምስ ጋዜጠኛ ባገኛት" አልኩ። ጭለማን ማንጋት የሚችሉ፣ ህልቆ መሳፍርት በሌለው የስራ አይነት ውስጥ ፣ ያላወቁትን አውቀውና የወደዱትን ሰንቀው ከባዶ ወደ ነዶ፣ የተለወጡን ስደተኞች ታሪክ በማስነበብ በእጅጉ የሚቀናው ጋዜጣ በመሆኑ ነው።
አዜብ የሀሳብ ሰው ናት። አዜብ ያሰበችውን ለመተግበርም ደፋር ናት። በስልጠናና እውቀት የምታምን፣ ለቤተሰብና ለትዳር አጋሯ ልዩ ክብር ያላት፣ ጭንቀትን መከላከልና ሁኔታን መታገስ የሚያስችል ልብም አላት። ከሁሉም በላይ የእምነቷን ጥንካሬ አይቻለሁ። ክርስትናዋም ያስቀናል።
በታሪኳ ውስጥ ያነሳቻቸውን ሰዎች የገለፀችበት መንገድ፣ አዜብ አመስጋኝና ረቂቅ ምግባር ያላት ሰው መሆኗንም ያሳያል። "ብዙ አሜሪካኖች ሥራና ታታሪነትን ይወዳሉ። ሁሉም አሜሪካዊያን ደግሞ ከሥራ ጀርባ ያለን ታሪክ አብልጠው ይወዳሉ" ይባላል። ሰባት ዓመት ከባለቤቷና ከልጆቿ እርቃ የኖረች እንስት፣ እንደ እናትም እንደ ሚስትም ሆና የሚሰማትን ለሚግምት ሁሉ፣ አዜብ ከዛሬው የስራዋ ፍሬ ጀርባ የጠንካራ ታሪክ ባለቤት መሆኗንም ያሳያል። ባለቤቷም በእርሷ ላይ ያለው እምነት፣ ከጀግና ወንድ ጀርባ እንዳለችው ሴት፣ ከጀግና ሴት ጀርባ ያለ ወንድ መሆኑንም ደርቦ የሚያስረዳ ነው። ሁለት ጀግኖች!
እህቴ ሆይ፣ አበቦችሽን ወደድኳቸው። ስለአበባም ግንዛቤ አግኝቻለሁ። አበባ ከልደት እስከ መቃብር በሰው ልጅ የኑሮ ገጾች ላይ ፍቅርና ክብር የሚገለጽበት ብቸኛ አለም አቀፍ ቋንቋ ነው። እሱን እንደ ማቅረብ ምን መልካም ስራ ይገኛል!? አመሰግናለሁ!
ንጉሴ አየለ
ታህሳስ 12, 2017
(Dec. 22, 2024)
መዝናኛ ሚዲያ፣ ዳንኤል ገብረማርያም፣ ከአሜሪካ