03/15/2024
መንታ ዓለሞች፣
የሃብትና የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤትነት ሁለት የማኅበራዊ ኑሮ ግሥጋሴ ጣሪያዎች ናቸው:: ሁለቱም በየፊናቸው ሰፋፊ ዓውድ ያላቸው ምድቦች ሲሆኑ ግለሰቦች በአንዱም ይሁን በሌላው ስኬታማና ባለቤቶች ለመሆን ስለሚፈልጉ ይነሳሉ ይወድቃሉ፣ ያሸንፋሉ ወይም ይሸነፋሉ:: ጉዳዬን ስዘነግግ ለምን አንዳንዶች ባለሃብትና ባለስልጣን ሲሆኑ የቀሩት ደፍሞ ድሆችና ተገዥዎች ለመሆን በቁ በሚል ጥያቄ እጀምራለሁ::
ሚስጥሩ ፈተና ነው:: ፈተናውን የማለፍና ያለማለፍ አቅማችን ማኅበራዊ ደረጃችንና ተሳትፏችንን ይወስነዋል:: ከዓመታት በፊት ልጆቸ ገና የመለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ይከታተሉ በነበረበት ወቅት ያጋጠመኝንና የተማርኩበትን ጉዳይ አልረሳም:: በቻልኩት አጋጣሚ ሁሉ ቻፕተርስ (Chapters) ወደሚባል የመፅሃፍ መደብርና ማንበቢያ ቦታ ይዣቸው እሄድ ነበር:: ይህ ተቋም ከብዙዎቹ ቤተ መፅሃፍት ይባልጣል ብሎ ለማስተዋወቅ የሚገባ ባይሆንም ላዋቂዎችና ለልጆች የሚሆን ብዙ ምርጥ መፅሃፍትን የሚይዝና በተጓዳኝ መዝናኛዎች ያሉት ነው:: አንዱን ዕለት በዚያው ከልጆቼ ጋእ እንዳለሁ እነሱ የሚፈልጉትን መራርጠው ገዝተው ከመውጣቸው በፊት (መግዛት እንጅ መዋስ አይቻልም) በአንዲት ጥግ ምንባባቸውን ከመውደዳቸው የተነሳ የዓለም ሃሳባቸውን ጥለው በየግላቸው የሚወዷቸውንና የሚከታተሏቸውን ተከታታይ ህትመት (Series) ያላቸውን መፅሃፍት እያነቡ እያሉ እኔም የሚጥመኝ አገለባብጥ ነበር:: በአንድ ትንሽዬ ጠንካራ ሽፋን ባላት መፅሃፍ ላይ አይኔ አረፈና አነሳኋት:: ይህን ስፅፍ ለጊዜው መፅሃፏን ካለቺበት ማግኘት ባልችልም(በእርግጠኝነት ከሆነ ነገር ጋር ታሽጋለች- ቤት በማሳደስ ላይ ነኝና) ርዕሷ "የሂሳብ መርሆዎች- (Mathematical Principles)" የሚል ይመስለኛል:: የመፅሃፏን መግቢያ እንዳነበብኩ በጣም ጠቃሚ መፅሃፍ ልትሆን እንደምትችል ገምትሁና ለልጆቸ ትሆናለች ብዬ ለመግዛት ወስኜ ገዛሁዋት:: ጊዜ ሰጥቸ መፅሃፏን አንብቤ ስረዳ መግዛቴን በጣም ወደድኩት:: የመፅሃፏ ዓላማ ሂሳብ ትምህርትን በሁለንተናዊ ባህሪው ለማስተማርና ከሰዎች የዕለት ተዕልት ህይወት ጋር የተቆራኘ መሆኑን በሚያስገርሙ ምሳሌዎች የሚያስረዳ ነው::
የዕልት ተዕልት ህይወታችን ማሰሪያና ማያያዣ የሆነውን የሂሳብ ትምህርትና እውቀትን ከባድ ትምህርት አድርገን እንዳንሸሸውና በህይወት ውስጥ ልናከውናቸው የምንችለውን ስኬታች እንዳናጣ የሚያሳስብና የሚያስገነዝብ ነው:: የመፅሃፉ አቀራረብ መንፈስ ንድፈ ሃሳባዊና ፍልስፍናዊ (theoretical & Philosophical) ቢሆንም ማንም ሰው እንደ አቅሙ ሊረዳውና ሊጠቀምበት የሚችል ነው:: ከልጆቸ ጋር ብዙ ጊዜ ተወያይቸበታለሁ:: መተረክ ስጀምርላቸው ያጣጥሉብኝና አባታችን ጃጃብን ብለው ነው መሰል ይሳሳቁብኝ ነበር:: ምሳሌውን መተርጎም ስጀምር ደግሞ በጣም በመመሰጥ "ልክ ነው፣ ትክክል" እያሉ ይከታተሉኛል:: በዚህም የራሳቸውን የሂሳብ ትምሀት ዓውድ ያሳደጉበት ይመስለኛል:: ለምሳሌ ታህል ስትራመድ ሂሳብ እየሰራህ ነው፣ ምግብ ስታበስይም ሂሳብ ላይ ነሽ፣ ወዘተ የመሳሰሉትን የመፅሃፉ ምሳሌዎች ብንወስድ ስንራመድ ከብዙ ሌሎች የሂሳብ ቀመሮች በተጨማሪ የምናልፈውን ርቀት በማይል ለክተን፣ የተራመድንበትን ፍጥነት በሰዓት አስበን፣ የሰራነውን ሂሳብ መልስ እንገኛለን:: ምግብ ስናበስልም ሠርተን የምናቀርበው ያማረና የጣፈጠ ምግብ እያንዳንዱ የምግብ አጣፋጭ መጠንና ልክ ተነፃፅሮ አንድ የምግብ ውጤት እንዲሆን በማድረግ ሂሳብ ሰርተናል:: የይህን ሁሉ የምለው ወደተነሳሁበት ለማምራት ነው:: ስለ እውነቱ ከሆነ ሂሳብ አዋቂ ማትማትሻኖች ብዕር ይዘው የፃፉልን ብቻ ሳይሆኑ አውቀውም ይሁን ሳናውቁ በልምዳቸውና በተመክሯቸው የተራቀቁ ሂሳብ አዋቂዎች በኅብረተሰብ ውስጥ ቁጥራቸው ብዙ ነው:: ጥሩ ጠማቂ፣ ጥሩ ምግብ ሰሪ፣ ጥሩ ሯጭ፣ ጥሩ ዘማሪ/ዘፋኝ፣ ወዘተ የሚባሉ ግለሰቦችን ታውቃላችሁ? እነዚህና መሰሎቻቸው በተግባር የሚገለጹ ሂሳብ አዋቂዎች ናቸው:: የእያንዳንዳቸው ስኬታዊ ሂሳብ በአራቱም መደበኛ የሂሳብ መደቦች የሚገለፅ ቀመር አለው- የሚደመር፣ የሚቀነስ፣ የሚባዛና የሚካፈል::
ማኅበራዊ እንቅስቃሴያችን በሂሳብ የተሞላውን ያህል የከፍተኛ ስኬታችን ማረጋገጫው ቀመሩን በትክክል አስቀምጠን በየዘርፉ የሚቀርብልንን የኑሮ ፈተና ማለፍ መቻላችን ነው:: ኑሮ ለብዙ ነገር ውድድር ነውና ሁሉም በአንደኛ ደረጃ አሸናፊ አይሆንም:: የውድድሩ እድል ለሁሉም ቢሆንም ውድድሩን በአጥጋቢ ሁኔታ አሸንፈው የሚሸለሙት ጥቂቶች ናቸው:: ከአሸናፊዎች በታች ደግሞ እንደ ስሌታቸውና ፍጥነታቸው ደረጃቸውን እየጠበቁ የሚጨርሱት እልፍ አዕላፍ ናቸው::
ከዚህ አኳያ "ገንዘብ ገንዘብን ይሰራል" ብለው በሚያምኑት "የሃብታሞች ዓለም" የሃብት ባለቤትነትን ፀጋ በመጎናፀፍ በአሸናፊነት የሚወጡት ጥቂቶች ለሁሉም የቀረበውን የስኬት ቀመር በሚገባ አሰላስለውና ደክመው ማሳካት የቻሉ ናቸው::
የሂሳቡ ቀመር:-
መነሻ ገንዘብ ሲደመር ጊዜ ሲደመር/ሲቀነስ ወለድ ሲቀነስ ታክስ ይሆናል ሃብት::
ብዙ ማኅበራዊና ሥነልቦናዊ ጉዳይ እንደለ አውቀንና ገድፈን ከላይ በቀረበው ቀመር መሰረት ጥርሳችን ነክሰን ከሰራንና ያለማዛነፍ ወደፊት ከገሰገስን የሃብት ባለቤት መሆን እንደሚቻል የፋይናንስ ባለሙያዎች ያረጋግጣሉ::
ወለድን አስመልክቶ ለምን መደመር ወይም መቀነስ ሆነ የሚሉ ይኖራሉ:: ምክንያቱ ስናበድር ትልቅ ወለድ፣ ስንበደር ደግሞ ትንሽ ወለድን ስለምንፈልግ ነው:: ሃብትን ለማፍራት ሁለቱም አይነት ባህሪዎች በእኩልነት ጠቃሚዎች ናቸው:: ለምሳሌ ህንፃ ገንብተን ለማከራየት ከባንክ የምንበደረው ገንዘብ በተቻልው መጠን ወለዱ ዝቅተኛ እንዲሆንልን እንፈልጋለን:: አበዳሪው ባንክም ይሁን ወይም እኛ ራሳችን ስናበድር ደግሞ ወለዱ ከፍ ብሎ ተበዳሪ ብናገኝ ብዙ አተረፍን ማለት ነው::
በለቲካው የሥልጣን ባለቤትነት ስኬትም በበኩሌ ይህ ነው የሚባል ድርሳን አጋጥሞኝ ባላይም የማይታለፍ መሰረታዊ ቀመር አለው ብዬ አስባለሁ:: እንደሚታወቀው የአንዲት ሀገር ሥነመንግሥታዊ ጥያቄና አገልግሎት የእያንዳንዱ ዜጋ ጉዳይና ድርሻ ነው:: የአንበሳውን ድርሻ ወስደው የሚሾሙትና የሚሽሩት ግን በጣም ጥቂት አሸናፊዎች ናቸው:: ይህ ቀመር ምን ሊመስልና ሊሆን እንደሚችል አስባችሁ ታውቃላችሁ? ለእኔ እንዲህ ይመስለኝል- አሁንም እንደ ሥንክሳር የበዙትን ማኅበራዊ ክስተቶችና ሥነልቦናዊ ግዝፈቶች እንዳሉ እያወቅን ወሳኝ መስፍርቶች ላይ በማተኮር::
የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤትነት ቀመር:-
ጥበብ ሲደመር ኃይል ሲደመር ጊዜ ሲደመር ቦታ ይሆናል የፖለቲካ ሥልጣን::
"ጥበብ" የፖለቲካ እምነት ግንዛቤን፣ ስልትን፣ ከሕዝብና ከባላንጋራ ጋር ያለ አግባቦትን፣ የማሰላሰልና የመወሰንን፣ ወዘተ ባሀይ ቢያጠቃልል፣
"ኃይል" ደግሞ ከላይ የተጠቀሱትና የመሳሰሉት ግላዊ እምነትና አመለካከቶች በሶስተኛ ክፍል ከፍላጎት ውጭና በጉልበት እንዳይቀሙና እንዳይዳጡ መጠበቂያ፣
"ጊዜ" ስንል ለመነሳትና ለመተግበር አመች የሆነ ሀገራዊ፣ አካባቢያዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች መስማማታቸውን የሚለካ ግንዛቤ ብቻ ሳይሆን የራስን የተሟላ ጤንነትና የእድሜ ደረጃ አመልካችና ገላጭ ነው ብዬ አስባለሁ::
"ቦታ" ስንል የት ላይ ሁኖ፣ ከማን ጋር፣ እነማን አሉ፣ በምን እንለያለን፣ ከየት እስከየት ለመሄድና ለመድረስ፣ የሚለውን ዓውደ ሃሳብና ተመሳሳይ ነጥቦችን ገላጭ በማድረግ::
====------
ይህን ፅሁፍ ያቀረብኩት "መንታ ዓለሞች" ባልኩት ዓውድ ላይ ለመወያየትና ግንዛቤ ለመውስውድ ነውና አንባቢዎቼ ጉዳዩን ከሀገራችንና ከአጠቃላይ ክስተቶች አንፃር እየተመለከታችሁ ባነሰና በጎደለ ሃሳባችሁን ብትጨምሩበት ትርፉ የጋራችን ይሆናል::