ሐዋርያ - Hawarya

ሐዋርያ - Hawarya በሀገር ውስጥና በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እንደ ብዙኃን መገናኛ መድረክ ሆነን እናገለግላለን።

We serve as a communication medium to Ethiopians who live in country and abroad.

03/15/2024

መንታ ዓለሞች፣

የሃብትና የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤትነት ሁለት የማኅበራዊ ኑሮ ግሥጋሴ ጣሪያዎች ናቸው:: ሁለቱም በየፊናቸው ሰፋፊ ዓውድ ያላቸው ምድቦች ሲሆኑ ግለሰቦች በአንዱም ይሁን በሌላው ስኬታማና ባለቤቶች ለመሆን ስለሚፈልጉ ይነሳሉ ይወድቃሉ፣ ያሸንፋሉ ወይም ይሸነፋሉ:: ጉዳዬን ስዘነግግ ለምን አንዳንዶች ባለሃብትና ባለስልጣን ሲሆኑ የቀሩት ደፍሞ ድሆችና ተገዥዎች ለመሆን በቁ በሚል ጥያቄ እጀምራለሁ::
ሚስጥሩ ፈተና ነው:: ፈተናውን የማለፍና ያለማለፍ አቅማችን ማኅበራዊ ደረጃችንና ተሳትፏችንን ይወስነዋል:: ከዓመታት በፊት ልጆቸ ገና የመለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ይከታተሉ በነበረበት ወቅት ያጋጠመኝንና የተማርኩበትን ጉዳይ አልረሳም:: በቻልኩት አጋጣሚ ሁሉ ቻፕተርስ (Chapters) ወደሚባል የመፅሃፍ መደብርና ማንበቢያ ቦታ ይዣቸው እሄድ ነበር:: ይህ ተቋም ከብዙዎቹ ቤተ መፅሃፍት ይባልጣል ብሎ ለማስተዋወቅ የሚገባ ባይሆንም ላዋቂዎችና ለልጆች የሚሆን ብዙ ምርጥ መፅሃፍትን የሚይዝና በተጓዳኝ መዝናኛዎች ያሉት ነው:: አንዱን ዕለት በዚያው ከልጆቼ ጋእ እንዳለሁ እነሱ የሚፈልጉትን መራርጠው ገዝተው ከመውጣቸው በፊት (መግዛት እንጅ መዋስ አይቻልም) በአንዲት ጥግ ምንባባቸውን ከመውደዳቸው የተነሳ የዓለም ሃሳባቸውን ጥለው በየግላቸው የሚወዷቸውንና የሚከታተሏቸውን ተከታታይ ህትመት (Series) ያላቸውን መፅሃፍት እያነቡ እያሉ እኔም የሚጥመኝ አገለባብጥ ነበር:: በአንድ ትንሽዬ ጠንካራ ሽፋን ባላት መፅሃፍ ላይ አይኔ አረፈና አነሳኋት:: ይህን ስፅፍ ለጊዜው መፅሃፏን ካለቺበት ማግኘት ባልችልም(በእርግጠኝነት ከሆነ ነገር ጋር ታሽጋለች- ቤት በማሳደስ ላይ ነኝና) ርዕሷ "የሂሳብ መርሆዎች- (Mathematical Principles)" የሚል ይመስለኛል:: የመፅሃፏን መግቢያ እንዳነበብኩ በጣም ጠቃሚ መፅሃፍ ልትሆን እንደምትችል ገምትሁና ለልጆቸ ትሆናለች ብዬ ለመግዛት ወስኜ ገዛሁዋት:: ጊዜ ሰጥቸ መፅሃፏን አንብቤ ስረዳ መግዛቴን በጣም ወደድኩት:: የመፅሃፏ ዓላማ ሂሳብ ትምህርትን በሁለንተናዊ ባህሪው ለማስተማርና ከሰዎች የዕለት ተዕልት ህይወት ጋር የተቆራኘ መሆኑን በሚያስገርሙ ምሳሌዎች የሚያስረዳ ነው::
የዕልት ተዕልት ህይወታችን ማሰሪያና ማያያዣ የሆነውን የሂሳብ ትምህርትና እውቀትን ከባድ ትምህርት አድርገን እንዳንሸሸውና በህይወት ውስጥ ልናከውናቸው የምንችለውን ስኬታች እንዳናጣ የሚያሳስብና የሚያስገነዝብ ነው:: የመፅሃፉ አቀራረብ መንፈስ ንድፈ ሃሳባዊና ፍልስፍናዊ (theoretical & Philosophical) ቢሆንም ማንም ሰው እንደ አቅሙ ሊረዳውና ሊጠቀምበት የሚችል ነው:: ከልጆቸ ጋር ብዙ ጊዜ ተወያይቸበታለሁ:: መተረክ ስጀምርላቸው ያጣጥሉብኝና አባታችን ጃጃብን ብለው ነው መሰል ይሳሳቁብኝ ነበር:: ምሳሌውን መተርጎም ስጀምር ደግሞ በጣም በመመሰጥ "ልክ ነው፣ ትክክል" እያሉ ይከታተሉኛል:: በዚህም የራሳቸውን የሂሳብ ትምሀት ዓውድ ያሳደጉበት ይመስለኛል:: ለምሳሌ ታህል ስትራመድ ሂሳብ እየሰራህ ነው፣ ምግብ ስታበስይም ሂሳብ ላይ ነሽ፣ ወዘተ የመሳሰሉትን የመፅሃፉ ምሳሌዎች ብንወስድ ስንራመድ ከብዙ ሌሎች የሂሳብ ቀመሮች በተጨማሪ የምናልፈውን ርቀት በማይል ለክተን፣ የተራመድንበትን ፍጥነት በሰዓት አስበን፣ የሰራነውን ሂሳብ መልስ እንገኛለን:: ምግብ ስናበስልም ሠርተን የምናቀርበው ያማረና የጣፈጠ ምግብ እያንዳንዱ የምግብ አጣፋጭ መጠንና ልክ ተነፃፅሮ አንድ የምግብ ውጤት እንዲሆን በማድረግ ሂሳብ ሰርተናል:: የይህን ሁሉ የምለው ወደተነሳሁበት ለማምራት ነው:: ስለ እውነቱ ከሆነ ሂሳብ አዋቂ ማትማትሻኖች ብዕር ይዘው የፃፉልን ብቻ ሳይሆኑ አውቀውም ይሁን ሳናውቁ በልምዳቸውና በተመክሯቸው የተራቀቁ ሂሳብ አዋቂዎች በኅብረተሰብ ውስጥ ቁጥራቸው ብዙ ነው:: ጥሩ ጠማቂ፣ ጥሩ ምግብ ሰሪ፣ ጥሩ ሯጭ፣ ጥሩ ዘማሪ/ዘፋኝ፣ ወዘተ የሚባሉ ግለሰቦችን ታውቃላችሁ? እነዚህና መሰሎቻቸው በተግባር የሚገለጹ ሂሳብ አዋቂዎች ናቸው:: የእያንዳንዳቸው ስኬታዊ ሂሳብ በአራቱም መደበኛ የሂሳብ መደቦች የሚገለፅ ቀመር አለው- የሚደመር፣ የሚቀነስ፣ የሚባዛና የሚካፈል::
ማኅበራዊ እንቅስቃሴያችን በሂሳብ የተሞላውን ያህል የከፍተኛ ስኬታችን ማረጋገጫው ቀመሩን በትክክል አስቀምጠን በየዘርፉ የሚቀርብልንን የኑሮ ፈተና ማለፍ መቻላችን ነው:: ኑሮ ለብዙ ነገር ውድድር ነውና ሁሉም በአንደኛ ደረጃ አሸናፊ አይሆንም:: የውድድሩ እድል ለሁሉም ቢሆንም ውድድሩን በአጥጋቢ ሁኔታ አሸንፈው የሚሸለሙት ጥቂቶች ናቸው:: ከአሸናፊዎች በታች ደግሞ እንደ ስሌታቸውና ፍጥነታቸው ደረጃቸውን እየጠበቁ የሚጨርሱት እልፍ አዕላፍ ናቸው::
ከዚህ አኳያ "ገንዘብ ገንዘብን ይሰራል" ብለው በሚያምኑት "የሃብታሞች ዓለም" የሃብት ባለቤትነትን ፀጋ በመጎናፀፍ በአሸናፊነት የሚወጡት ጥቂቶች ለሁሉም የቀረበውን የስኬት ቀመር በሚገባ አሰላስለውና ደክመው ማሳካት የቻሉ ናቸው::

የሂሳቡ ቀመር:-
መነሻ ገንዘብ ሲደመር ጊዜ ሲደመር/ሲቀነስ ወለድ ሲቀነስ ታክስ ይሆናል ሃብት::

ብዙ ማኅበራዊና ሥነልቦናዊ ጉዳይ እንደለ አውቀንና ገድፈን ከላይ በቀረበው ቀመር መሰረት ጥርሳችን ነክሰን ከሰራንና ያለማዛነፍ ወደፊት ከገሰገስን የሃብት ባለቤት መሆን እንደሚቻል የፋይናንስ ባለሙያዎች ያረጋግጣሉ::
ወለድን አስመልክቶ ለምን መደመር ወይም መቀነስ ሆነ የሚሉ ይኖራሉ:: ምክንያቱ ስናበድር ትልቅ ወለድ፣ ስንበደር ደግሞ ትንሽ ወለድን ስለምንፈልግ ነው:: ሃብትን ለማፍራት ሁለቱም አይነት ባህሪዎች በእኩልነት ጠቃሚዎች ናቸው:: ለምሳሌ ህንፃ ገንብተን ለማከራየት ከባንክ የምንበደረው ገንዘብ በተቻልው መጠን ወለዱ ዝቅተኛ እንዲሆንልን እንፈልጋለን:: አበዳሪው ባንክም ይሁን ወይም እኛ ራሳችን ስናበድር ደግሞ ወለዱ ከፍ ብሎ ተበዳሪ ብናገኝ ብዙ አተረፍን ማለት ነው::

በለቲካው የሥልጣን ባለቤትነት ስኬትም በበኩሌ ይህ ነው የሚባል ድርሳን አጋጥሞኝ ባላይም የማይታለፍ መሰረታዊ ቀመር አለው ብዬ አስባለሁ:: እንደሚታወቀው የአንዲት ሀገር ሥነመንግሥታዊ ጥያቄና አገልግሎት የእያንዳንዱ ዜጋ ጉዳይና ድርሻ ነው:: የአንበሳውን ድርሻ ወስደው የሚሾሙትና የሚሽሩት ግን በጣም ጥቂት አሸናፊዎች ናቸው:: ይህ ቀመር ምን ሊመስልና ሊሆን እንደሚችል አስባችሁ ታውቃላችሁ? ለእኔ እንዲህ ይመስለኝል- አሁንም እንደ ሥንክሳር የበዙትን ማኅበራዊ ክስተቶችና ሥነልቦናዊ ግዝፈቶች እንዳሉ እያወቅን ወሳኝ መስፍርቶች ላይ በማተኮር::

የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤትነት ቀመር:-

ጥበብ ሲደመር ኃይል ሲደመር ጊዜ ሲደመር ቦታ ይሆናል የፖለቲካ ሥልጣን::

"ጥበብ" የፖለቲካ እምነት ግንዛቤን፣ ስልትን፣ ከሕዝብና ከባላንጋራ ጋር ያለ አግባቦትን፣ የማሰላሰልና የመወሰንን፣ ወዘተ ባሀይ ቢያጠቃልል፣

"ኃይል" ደግሞ ከላይ የተጠቀሱትና የመሳሰሉት ግላዊ እምነትና አመለካከቶች በሶስተኛ ክፍል ከፍላጎት ውጭና በጉልበት እንዳይቀሙና እንዳይዳጡ መጠበቂያ፣

"ጊዜ" ስንል ለመነሳትና ለመተግበር አመች የሆነ ሀገራዊ፣ አካባቢያዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች መስማማታቸውን የሚለካ ግንዛቤ ብቻ ሳይሆን የራስን የተሟላ ጤንነትና የእድሜ ደረጃ አመልካችና ገላጭ ነው ብዬ አስባለሁ::

"ቦታ" ስንል የት ላይ ሁኖ፣ ከማን ጋር፣ እነማን አሉ፣ በምን እንለያለን፣ ከየት እስከየት ለመሄድና ለመድረስ፣ የሚለውን ዓውደ ሃሳብና ተመሳሳይ ነጥቦችን ገላጭ በማድረግ::

====------
ይህን ፅሁፍ ያቀረብኩት "መንታ ዓለሞች" ባልኩት ዓውድ ላይ ለመወያየትና ግንዛቤ ለመውስውድ ነውና አንባቢዎቼ ጉዳዩን ከሀገራችንና ከአጠቃላይ ክስተቶች አንፃር እየተመለከታችሁ ባነሰና በጎደለ ሃሳባችሁን ብትጨምሩበት ትርፉ የጋራችን ይሆናል::

01/12/2024

የአብሮ መኖር መላው በሥዕል ተስሎ፣
የእናት አባት ሚስጥር በውል ተመስጥሮ፣
ተነግሮኝ ነበረ ተቀምጧል ተብሎ፣
እንዳይላላ ውሉ ተተብትቦ ታሥሮ::
ፈልጌ ካጣሁት ድንገት ከመሸብኝ፣
ሸለብ ካደረገኝ ድካሙ በዝቶብኝ፣
ሌሊቱ ሲነጋ ስትነቁ አግኙትኝ::
---///---

01/05/2024

ኢትዮጵያ ተዘግቶባትና ታፍና ባለችበት ቀጠና የጋረዳትን ግምብ ሰርስራ በመክፈት ወደሚታያት የብርሃን ጭላንጭል እምር ብላ ወጥታ ለመብረር ስትሞክር የሚያዩዋት ባላንጣዎቿ "ልታመልጥ ነው" በሚል ዓይነት ሥጋት እንዴት ተረባርበው ለማስቆም እንደሚሰለፉ ላጤነ ከአካባቢውና ዓለም አቀፉ የፖለቲካ አንቲካራ ባሻገር እንዲህ ጨርቃቸውን አስጥሎ የሚያጣድፋቸውና የሚያሯሩጣቸው ሚስጥር ከቶ ምን ይሆን የሚስብልና የሚያስገርም ትዕይንት ነው:: የሚያሳዝነው ግን በመረገማችን ይሁን ወይም በመታደላችን እድል እንዲህ በብዙ "ነገሥታቶች" እና ጭፍራዎቻቸው ዐይን ያስገባንን አጥናፋዊ እጣፈንታችንን ብዙዎቻችን መሠረታዊ በሆነ ግንዛቤ ልክ ልብ አለማለታችን ነው:: በሀገሪቱ የዘመነ ታሪክ ውስጥ የምናልፍ መሪዎችና ተሳታፊዎች ሁሉ አባቶቻችን ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ዘላለማዊ ለማድረግ ያሰላሰሉትን አርቆ አሳቢነትና የሄዱበትን የዘመናት ተጋድሎ መንገድ ረስተን ዛሬ ላይ ሰፈር ለሰፈር መርመጥመጣችንና ለሽርፍራፊ ጥቅማጥቅሞች ማጎብደዳችን የሀገሪቱን ጠላቶች ጦርነት 'በብላሽ' በመዋጋት ማንነታችን እያጠፋን መሆኑን ገና የተረዳን አይመስልም:: ማልቀስም ይሁን ማስለቀስ በሀገር ያምራል የምንል ሁሉ፣ እርስ በርሳችን እልህ ተገባብተን ለመሸናነፍ የምንዋደቅና እንዲሁም በፍርፋሪ ጥቅማጥቅም ማንነታችን የምንደልል ሁሉ፣(እረ ከዚያም በላይ በየጊዜው የሚከሰቱትን አደገኛ ሀገራዊ ጉዳዮች እንደ ፖለቲካ ስልት ለመጠቀም በመሻት ለምልሞ የሚታየውንና የሚያስጎመዠውን የገደል አፋፍ ሳር ለመቀነጣጠብ የምንገፋፋ ሁሉ) ሀገር ከጠፋች ሁሉም አልቦ ይሆናልና የነገራችን ሁሉ ማጠንጠኛ መጀመሪያ እኔነቴ -የትውልድ ሀገሬ የሚል ይሁን:: በኋላ እንዳይቆጨን:: ኢትዮጵያ ከሌሎች ፈራርሰውና ማንነታቸው ዘቅጦና ጠፍቶ ካየናቸው ታላላቅ ሀገሮች ሁሉ የተለየች አትሆንም:: በሰዓቱ ልጆቿ ካልነቁና ካልተከላከሉ ሌላ ተጨማሪ የውድቀት ታሪክ ይሆናሉ:: የሚጎነጎነውን ሴራ ሳይረዳ ውስጡ ባለው ችግር ክብደትና የምሬት ስሜት ምክንያት ሁሉ ነገር ተሸፍኖበት በጠላቶቹ ወጥመድ ውስጥ ገብቶ በመውደቅ ላልተከላከለና ራሱን አሳልፎ ለሰጠ ትውልድ ይህ ሃቅ ይሆናል::
---///---

12/25/2023

ለጊዜውም ቢሆን ቀን ካሸጋገረ ከተመቸላቸው ፣
ጤፍ ጋግረው ጤፍ ሰርተው ሁሉን ጤፍ አድርገው፣
ስም ሰጠው ስም ጠቅሰው "እሱ በሱ" ብለው፣
ይበሉታል እመን እንጀራውንም ጤፍ ወጡንም ጤፍ አ'ርገው::
---///---

12/24/2023

ፅኑ አማኝ ነበርኩ የቀሰስኩ፣
የወንጌ ቃል የማወርድ መጽሃፍ ቅዱስ ያነበብኩ፣
ነጭ የጠመጠምኩ ጥቁር ሰይጣን ያባረርኩ፣
ሰምቶ ለማይሰማ ይፍታህ ብዬ የባረኩ፣
አሁን ያረፍኩ ወህ ያልኩ--
እንዳፈረሱት አፍርሸ የደበተርኩ::
የማውቀውን ሳውቅ ያኔም ሆነ ዛሬ ፣
የሚደንቀኝና ግርም የሚለኝ ለእኔ፣
የሚያስፈራኝ ንግርት እሳቤ፣፣
እየደረሰ ሲፈፀም የማየው በሀገሬ
ቁስ ያልሆነው ቁስ የመጽሃፈ ኢያሱ ንባቤ::
---///----

Address

Toronto, ON

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ሐዋርያ - Hawarya posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to ሐዋርያ - Hawarya:

Share