01/03/2026
#በረከት በተስፋዬ ሲንድረም በኩል!
(በማዕረግ ጌታቸው)
የተስፋዬ ገብረአብ ትልቁ ጥፋቱ በታሪክም ሆነ በሳይንስ የማይረጋገጡ ጉዳዮችን ፖለቲካዊ ማዕቀፍ እየሰጠ ሕዝባዊ ለማድረግ መጣሩ ነው። ይህን ችግር ተስፋዬ ሲንድረም ብዬ እጠራዋለሁ። ሲንድረሙ ዝንቅ ነው። መነሻው እውነት መድረሻው ግነት/ ውሸት። በረከት በላይነህ ባለፉት ጥቂት ወራት በሚሰጣቸው ቃለ-መጠይቆች በዚህ ጎዳና እያመራ ይመስለኛል። ልዩነት አብዛኛው ሕዝብ መሰማት የሚፈልጋቸውን ጉዳዮች በማውራቱ የረባ ጥያቄ ሲቀርብበት አለመሰማቱ ነው።
የቆየውን ትተን ትናንት በሰጠው ቃለ-መጠይቅ ላይ ብቻ እናተኩር። በረከት በቆይታው ኢትዮጵያ ዛሬ ያለችበት ዲፕሎማሲያዊ ቁመና የአሰብ ወደብን ለማስመለስ የሚችል ነው ብሎ እንደሚያምን ጠቀሷል። የሚያስገርመው ግን ቆየት ብሎ የተናገረው ነገር ነው። ዳዊት ተስፋዬ "እንዴት?" የሚል ጥያቄ ሲያቀርብለት "በጉልበት" ሲል መለሰ። ተቃርኖው የዋዛ አይመስለኝም። የበረከት ሕሊናዊ መዝገበ ቃል ብዙ ጊዜ ከታሪክና ሳይንስ ጋር የሚጋጭ ነው። ለዚህ ማስረጃው በዓለም ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ጦርነትን ዲፕሎማሲ አድርጎ መግለጹ ብቻ አይደለም። ይልቁኑስ የሕግና የታሪክ አረዳዱም ከተስፋዬ ሲንድርም አላስመለጠውም።
በረከት በላይነህ በደጃፍ ቲቪ ደጋግሞ የኢትዮጵያን የአሰብ ወደብ ይገባኛል ጉዳይ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሕግ (Accese to the sea) ሊዳኘው ይሞክራል። ይሁን እንጂ እዚህም ላይ ያለው ግንዛቤ እርስ በእርሱ የሚጣረስ ነው። አንድ ጥያቄ ነገሩን ግልጽ ያደርገዋል። በረከት "አሰብ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ግዛት ነው ብሎ ያምናል?" ምላሹ አጭርና ግልፅ ነው::
አዎ!
ታዲያ ተቃርኖው የሚወለደውም እዚህ ሥፍራ ላይ ነው። እርሱ ደጋግሞ የሚጠራው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የባሕር በር ለሌላቸው አገራት የሰጠው የመጠቀም መብት (Accese to the sea) ከወደብ ግዛት ይገባኛል ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም። ማንም አንባቢ በቀላሉ በበየነ መረብ ሊያረጋግጥ እንደሚችለው UN የባሕር በርን አስመልክቶ ያቀረባቸው አምስት የሕግ አንቀጾች አንዳቸውም ከበረከት መከራከሪያ ጋር ቅርበት የላቸውም፡፡ እውነታው እንዲህ ከሆነ ድንጋጌውን አላነበበውም አልያም አጣሞ ተረድቶታል ብሎ መናገሩ ድፍረት አይሆንም፡፡
እንዲህም ሆኖ አጭር ምሳሌ መስጠት ፍርደ ገምድል ከመባል ስለሚያድነኝ ወደዛው ልለፍ። ቦሊቪያ የባሕር በሯን ተነጥቃ የቀረችው በጦርነት ነው። የሚያስገርመው ግን መሪዎቹ ለዙፋናቸው ሲሉ ባደረጉት ስምምነት የሔደውን ወደባቸውን ለቺሊ ማጽናታቸው ይመስልል። ይህ የታሪክ አውድ ሂደቱ ቢለያይም በመጡንም ቢሆን ለበረከት ክርክር ቅርበት ያለው ነው::
በመሆኑም የሁለቱን አገራት ተሞክሮ ማጤን የባህር በር የመጠቀም ዓለም አቀፍ ሕግና የይገባኛል ጥያቄን ልዩነት ለመረዳት ያግዛል:: ቦልቪያዊያን ከግማሽ ምዕተ ዓመት በኇላ ዛሬ በአገራችን እንደሚታየው ሁሉ የወደብ ጉዳይን የፖለቲካ አጀንዳ ለማድረገው ችለው ነበር:: ይሁንና ጥያቂያቸው ግልፅኔና ቀጥተኛ ነው:: ጉዳያችን የወደብ ባለቤትነት እንጂ የመጠቀም (Accese to the sea) አይደለም አሉ::
ከፍ ብዬ እንደገለፅኩት ሁለቱ የሚታዩበት ዓለም አቀፍ ሕግ ፍፁም የተለያየ ነው::ስለሆነም ቦሊቪያ የተወሰደብኝን የባሕር በርን ልጠቅም ሳይሆን ይገባኛል ብላ ለዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ICJ ከሰሰች። ክርክሩ ለዓመታት ዘልቆም በ2018 ውሳኔ አገኘች። በረከት የተምታታበት እንዲህ ያለው መንገድ ነው:: ታሪካዊ ባለቤተነትን የባህር በር ከመጠቅም መብት ጋር ተሳክሮበታል::
እንዲህ ያለው የታሪክ ተሳክሮ አንድ ቦታ ላይ ብቻ የሚታይ አይደለም:: በየቃለ መጠይቁ የሚደጋግመውን የሰሜን ኢትዮጵያ ፖለቲካ አረዳዱን ላክል። ውስብስቡን የዘመነ መሳፍንት ዘመን አጣቅሶ ለመግለጽ የሞከረው ለራሱም ግልጽ ስላልሆነ ሁለቱን ፓርቲዎች ብቻ እንመልከት። በረከትም ሆነ በርካታ የአደባባይ ተንታኞች የሰሜን ኢትዮጵያ ብሔርነተኝነት የተወለደውና የተዳረው በኤርትራዊያን እንደሆነ አድርገው ጽፈዋል፤ተናግረዋል።
እነዚህ ሰዎች የሚዘነጉት አንድ ትልቅ ሀቅ አለ። እርሱም የኤርትራን ነፃነት ጥንስስ የጣለው፤ ብሎም ግብጽ በመሔድ በካይሮ ራዲዮ የዓየር ሰዓት አግኝቶ በፕሮፖጋንዳ ስራው በርካቶችን ወደ ትግል ያስኮበለለው፤ ቀደሚውንም የአስገንጣይ ድርጅት የመሰረተው የትግራዩ ወልደአብ ወለደማርያም መሆኑን መርሳታቸው ነው።
በረከት እና አንዳንድ የአደባባይ የታሪክ ተንታኞች የትግራይ ብሔርተኝነት የሻዕብያ ዲቃላ መሆኑን ቢገልጹም እውነታው ግን ሻዕቢያ ራሱ የትግራዩ ወልደአብ ወልደማርያም የልጅ ልጅ መሆኑ ነው። የወልደአብን የማንነት ቀውስና የታሪክ ተቃርኖ ለሌላ ጊዜ አቆይተነው በረከት ትናንት በስፋት ሊተነትነው የሞከረውን የሕወሓትና ሻዕቢያ ባንድ ሳምባ ነው የሚተነፍሱ ሙግት እንመልከት። በርግጥ እንዲህ ያለው ሀሳብ አገሩን ከሞላው ከራርሟል። ሁለቱ አማጽያን ሲሰርቁ ተስማምተው ሲካፈሉ ተጣሉም ተብሎ በብዙ ተለፏል።
ከፍ ብለን እንዳደረግነው ሁሉ ይህንንም በጥቂቱ ለመፈተሸ እንሞክር። ሕወሓትን አብዝቶ በመተቸት የሚታወቀው አረጋዊ በርኼ በሦስተኛ ድግሪ መመረቂያው ጽሑፉ ሁለቱ ድርጅቶቹ ፀብ የጀመሩት ፍቅራቸውን ሳያጣጥሙ መሆኑን ያነሳል።እርሱም ከርዕዮተ ዓለም ምርጫ ጋር የተያያዘ ነበር። በጊዜው ሻዕቢያ የሶቪየትን ሶሻላዚም ሲከተል ሕወሓት በአንፃሩ ጨቋኙን ደርግ የምትረዳን አገር ርዕዮተ ዓለም እየተከተሉ ጭቆናን መታገል ዘበት ነው ሲል ሞግቷል።
አለመግባባቱ እዚህ ላይ አልቆመም። ሻዕቢያ በነገው የኤርትራ አገርነት ውስጥ ድንበራችን የት ድረስ ነው ብሎ ጥያቄ ያቀረበው ገና በረሃ እያሉ ነበር። እዚህም ላይ ከሕወሓት ያገኘው ምላሽ የሚጥም አልነበረም። ስለዚህም ሁለቱ አማጽያን ወዳጅነታቸው ተፈቶ ስትራቴጅካዊ ጥምረታቸው ወደ ታክቲካል ወዳጅነት በይፋ መውረዱን የተለያዩ ሰነዶች ያስረዳሉ። በ1977 ዓ.ም ሻዕቢያ ለትግራይ ተረጅዎች እርዳታ የሚታላለፍበትን ኮሪደር ዘግቶ አዕላፍትን በርሃብ እስከመቅጣት የደረሰውም በሕወሓት ጸረ ዴሞክራት ተብያለሁ ግልፍተኝነት ጭምር ነበር::
በእኔ አረዳድ ሁለቱ ድርጅቶች አገር ይዘው ወደ ውጊያ ሜዳ የወረዱት አንድም በሻዕቢያ ስግብግብነት አንድም በታሪካዊ ቁርሿቸው ምክንያት ነው። በረከት ግን በትንታቴው እነዛን የከረሙ ባላንጣዎች ጠላታችን ባሉት ደርግ ላይ ያሳዩትን የአውደ ውጊያ ትብብር ብቻ ተውሶ በአንድ ሳንባ እንደሚተነፍሱ አድርጎ አቅርቧቸዋል። ፈረንጆቹ ቁጥር አይዋሽም የሚል ብሒል ስላላቸው ታሪኩን በቁጥር እንየው።
ሕወሓት ዛሬ የ51 ዓመት አረጋዊ ሲሆን ከሻዕቢያ ጋር በሰላም ያሳለፈበት ጊዜ በድምሩ 20 ዓመት ብቻ ይገመታል። በተቃራኒው ሁለቱ ፓርቲዎች የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትን ተከትሎ ከነበረው የ20 ዓመታት ግጭት ባለፈ ወደ ስልጣን ሳይመጡና ከመጡ በኋላ በድምሩ ከ27 ዓመት በላይ በጥርጣሬና በደመኝነት ሲተያዩ ቆይተዋል::
የበረከት በላይነህ ፖለቲካ ኢትዮጵያን የአካባቢው ራሽያ አድርጎ አሰብን በጉልበት መውሰድ እንደሚቻል ቢገልጽም እመኑኝ ከማለት በቀር እዚህ ግባ የሚባል መከራከሪያ እንኳን ማቅረብ የተሳነው ነው። በመውጫዬ ከቃለ-መጠይቁ ጋር አያያዤ ሁለት ነገሮችን መጠቆም ሳይኖርበኝ አይቀረም። የኤርትራ ፖለቲካ በጅምሩ በሶሪያ ሕገ-መንግሥት የታወጀ፣ በኢራቁ ባሕስ ባርቲ ማኒፌስቶ ላይ የሰፈረ፤ በሱዳንና ሱማሊያ መንግሥት ድጋፍ ዳዴ ማለት የጀመረ መሆኑ ኢትዮጵያን ወደብ አልባ ከማድረግ የዘለለ አጅንዳ እንደሆነ ያረጋግጣል።
ሌላም ላክል፤ በረከት ሥነ-ጽሑፍን ትቶ ባለፈው 10 ዓመት በንባብ ወደ ፖለቲካ ራሱን እንዳሳደገ በገደምዳሜ ነግሮናል:: ይሁንና ከሥነ- ጽሑፍ የተለየ የፖለቲካ መንገድ መኖሩን ለማወቅ የግድ በረከትን መሆን ይጠይቃል:: እኔ ግን እላለሁ:: ከታጎር እስከ ሴንጎር ከሌኒን እስከ ሒተለር የአገራት ሚትና ነፍስ የተሰራው በሥነ-ጽሁፍ ነው::
Maereg Getachew