01/10/2026
ነዳጅ መሬት ላይ በማርከፍከፍ ምረቃውን ያከበረው ማደያ ተቀጣ
ለህዝብ ጥቅም የሚውልን ነዳጅ ያላአግባብ ያፈሰሱ አካላት እገዳ ተጣለባቸው
ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ወጥቶበት ወደ አገር የሚገባን ነዳጅ ኃላፊነት በተሞላው መንግድ ለህዝብ ጥቅም ማዋል ሲገባው ያለአግባብ እንዲፈስ ያደረገ ማደያ ለሶስት ወር ከነዳጅ ጭነት ትስስር እገዳ ተጣለበት፡፡
በአርሲ ዞን ዳክሲሰ በሚባል ቦታ ሥራ የጀመረ ግሎባል የሚባል ማደያ ከነዳጅ መቅጃ ማሽን ነዳጅን ሲያርከፈክፍ በማህበራዊ ትስስር ገፆች መታየቱን ተከትሎ ባለስልጣኑ ጉዳዩን በማጣራት ድርጊቱን መፈጸሙን በማረጋገጡ ይህን ድርጊት የፈጸመው ማደያ በነዳጅ ግብይት አዋጅ ቁጥር 1363/2017 አንቀጽ 7(10)ስር ያለዉን ግዴታ በመጣስ በአንቀጽ 11(9)መሠረት ህገ ወጥ ድርጊት ፈጽሞ ስለተገኘ የወንጀል ተጠያቂነቱ የሚቀጥል ሆኖ በአዋጁ አንቀጽ 23(1)መሠረት ለ3ወራት ፈቃዱ ታግዷል፡፡
ከባለስልጣን መ/ቤቱ የማደያ ፈቃድ አውጥተው ምርቱን ለህብረተሰቡ በአግባቡ ተደራሽ ለማድረግ ፈቃድ ሲሰጥ ከሚገቡ የፈቃድ ግዴታዎች መካከል አንዱ የነዳጅ ደህንነቱን እና ደረጃውን በጠበቀ ማዳያ በቂ የሆነ የድንገተኛ አደጋ መከላከያ ግብዓቶችን አሟልቶ በወጣው የእለታዊ ዋጋ በጥብቅ ዲስፕሊን እና ጥንቃቄ ለተጠቃሚው መሸጥ ግዴታዎችን የጣሱ በመሆኑ ባለስልጣን መ/ቤቱ ጉዳዩን ተከታትሎ ተገቢው የህግ ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲሆን ክትትል እንደሚያደርግ ይታወቅልኝ ብሏል። ህገወጥ የነዳጅ ግብይትን የመከላከል ስራ የመላው ህዝብ ኃላፊነት በመሆኑ ይህን ድርጊት ለጠቆሙ ወገኖችም ምስጋናውን አቅርቧል።