Silta Mass Media

የስልጤ ማህበረሰብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በአብሮነት የመኖር ባህል የዳበረ ከመሆኑም ባለፈ  የሄደበትን አካባቢ በማልማት የሚታወቅ ህዝብ ነው ሲሉ  የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር...
27/07/2025

የስልጤ ማህበረሰብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በአብሮነት የመኖር ባህል የዳበረ ከመሆኑም ባለፈ የሄደበትን አካባቢ በማልማት የሚታወቅ ህዝብ ነው ሲሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ወ/ሮ ሙፈሪሀት ካሚል ተናገሩ ።

ሚኒስትሯ ይህንን ያሉት የስልጤ ልማት ማሕበር ለ2ኛ ጊዜ ያዘጋጀው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በስልጤ ዞን በአልቾ ውሪሮ ወረዳ በተካሄደበት ወቅት ነው ።

የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈርያት ካሚል በዚህ ወቅት እንዳሉት የስልጤ ማህበረሰብ የሄደበትን አካባቢ ከማልማት በተጨማሪ የትውልዱ አካባቢውንም የማልማትና የማሳደግ ሃላፊነት እንዳለበት ተናግረዋል።

ማህበረሰቡ በኢትዮጵያ ከሚገኙ ብሄር ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ጋር አብሮ የመኖር ባህልን ያዳበረ ከመሆኑም ባለፈ የሄደበትን አካባቢ በማልማት የጠንካራ የስራ ባለቤት መሆኑን አስመስክሯል ብለዋል።

የስልጤ ማህበረሰብ ጥንካሬ ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚደረገውን እንቅስቃሴ እውን ለማድረግ ያግዛል ያሉት ሚኒስትሯ የልማት ማህበሩ ከምስረታው ጀምሮ በአካባቢ የሚታዩ የጤና፣ የትምህርት የመንገድና የአረንጓዴ ልማት የመሳሰሉ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ከመቅረፉም ባለፈ የህብረተሰቡን ማህበራዊ ግንኙነት ለማጠናከር ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ገልፀዋል።

ዞኑ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የቱሪስት መዳረሻዎች ባለቤት በመሆኑ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን በማልማት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ መሰራት እንደሚገባ ተናግረዋል።

አቶ አደም ኑሪ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ፕላንና ልማት ቢሮ ሃላፊና የስልጤ ልማት ማህበር ምክትል ሰብሳቢ በበኩላቸው የስልጤ ልማት ማህበር ከተመሠረተበት 1994 ዓ.ም ጀምሮ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል።

የስልጤ ልማት ማህበር የማህበረሰቡን ችግር ለመቅረፍ በርካታ ስራዎችን ሲሰራ መቆየቱን የጠቀሱት ምክትል ሰብሳቢው ይህንን ተግባሩን በውጤታማነት ለማስቀጠል የአስር ዓመታት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።

የስልጤ ልማት ማህበር ከሚሰራቸው የልማት ስራዎች ጎን ለጎን የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የችግኝ ተከላ ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸው የልማት ማህበሩን እቅድ ከግብ ለማድረስ ተግባር ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል ።

የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ በበኩላቸው በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወነ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ካለው ፋይዳ በተጨማሪ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።

የስልጤ ልማት ማህበር ከሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች በተጨማሪ በየዓመቱ የሚከናወን የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አንዱ መሆኑን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው ሀገራዊ የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ ከተጀመረ ወዲህ በዞኑ ከ400 ሚሊዮን በላይ ችግኝ በመትከል የዞኑን የደን ሽፋን 19.5 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል ።

የዞኑ መንግስት ማህበሩ የሚያደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች በማገዝ የበኩሉን እንደሚወጣ ገልፀዋል ።

በመርኃግብሩ ላይ የተገኙት የአልቾ ውሪሮ ወረዳ ዋና አሰተዳዳሪ ወ/ሮ መህዲያ ሀሰን ወረዳው የአምስቱ የስልጤ ቀደምት እናቶች መገኛ ከዞኑ በቅርብ ርቀት የሚገኝ ፣ ለኑሮ ምቹ እንዲሁም በርካታ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች ባለቤት ከመሆኑም ባለፈ የተለያዩ የሰብልና የፍራፍሬ አይነቶችን ለማልማት ምቹ አካባቢ መሆኑን ተናግረዋል።

የስልጤ ልማት ማህበር ባዘጋጀው ሁለተኛው ዙር የችግኝ ተከላ መርሃግብር ላይ የተሳተፉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በበኩላቸው ሀገራዊ የአረንጓዴ ልማት ተግባር እውን ለማድረግ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።

ቀጣይ የስልጤ ልማት ማህበር (ስልማ 3) የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ፕሮግራም በዞኑ ከላንፉሮ ወረዳና ጦራ ከተማ አስተዳደር በጋራ የሚያዘጋጁ መሆኑም ተገልጿል ።

በመርሃ ግብሩ ላይ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚልን ጨምሮ የፌዴራል፣የክልል፣የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የስልጤ ብሔረሰብ ተወላጆች እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል።

በመጂብ ጁሃር

"ዛሬ ላይ በጡረታ ብገለልም ሀገሬ ተደፍራ አልቀመጥም" በጦር ሜዳ የልተቋጨው የሀገር ፍቅር ፦ የቀድሞው ወታደር ሸምበል ረዲ   ። ። ። ። ። ። ። ።ሻምበል ረዲ ረሺድ መሐመድ ይባላሉ ትው...
20/07/2025

"ዛሬ ላይ በጡረታ ብገለልም ሀገሬ ተደፍራ አልቀመጥም" በጦር ሜዳ የልተቋጨው የሀገር ፍቅር ፦ የቀድሞው ወታደር ሸምበል ረዲ
። ። ። ። ። ። ። ።
ሻምበል ረዲ ረሺድ መሐመድ ይባላሉ ትውልድና እድገታቸው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በስልጤ ዞን በአልቾ ዉሪሮ ወረዳ ቀረሶ ቀበሌ ልዩ ስሙ ጣንዤ በሚባል መንደር ሲሆን በኢፌዴሪ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ ከ23 አመታት በላይ በተለያዩ ግዳጆችና የአመራርነት የስራ ድርሻዎች ሀገራቸውን አገልግለዋል።

ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በዘለቀው የዉትድርና ህይወታቸው በርካታ ውጣ ውረዶችን፣ የመከራና የደስታ ጊዜያትን ያሳለፉ ሲሆን በሀገር መከላከያ ሠራዊት በሰሜን ዕዝ ማሰልጠኛ ትምህርትና ዝግጅት ክፍል አስተባባሪና አሰልጣኝ በመሆን ለበርካታ ዓመታት አገልግለዋል።

በሰሜን ዕዝ የኢፌድሪ የሀገር መከላከያ ስራዊት ከተራ ወታደርነት አንስቶ በውትድርና ሙያ አሰልጣኝነት ፣በቴክኒክና ጥገና ክፍል አስተባባሪነት ያገለገሉ ሲሆን በሀገር መከላከያ ስር በሚገኙ ማሰልጠኛ ተቋማት ላበረከቱት አስተዋጽኦ በ2000 ዓ.ም በሰሜን ዕዝ በተከበረው የሚሊኒየም በዓል ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እጅ የሪዶ ስዓት እና ሰርተፊኬት ተቀብለዋል።

ኢትዮጵያ በሰላም ማስከበር ተልዕኮ በአፍሪካም ይሁን ከአፍሪካ ውጭ ባሉ ሀገራት መልካም ስም ያላት በመሆኑ ከበርካታ ሀገራት ጋር በመልካም ወዳጅነት እንድትታወቅ አድርጎታል የሚሉት ሻምበል ረዲ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ ሰላም መረጋገጥ በምታደርገው ጥረት በተለይም በተባበሩት መንግታት ድርጅት ስር በኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ከ2003 እስከ 2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ የሰላም አስከባሪ ኃይል ጋር በመሆን በሱዳን አብዬና አጎክ ግዛቶች ላይ ለ2 ዓመታት በአካባቢው የነበረውን ግጭት በመፍታት ተልዕኮአቸውን በሚገባ መወጣት ችለዋል።

ምንም እንኳን በአሁኑ ሰዓት ከሀገር መከላከያ ሰራዊት አባልነት በጡረታ የተገለሉ ቢሆንም "ሀገሬ በፈለገችኝና ባስፈለግኳት ጊዜ ሁሉ ጠላቷን ለመመከት ዝግጁ ነኝ "የሚሉት ሻምበል ረዲ ስለ ኢትዮጵያ ሲነሳ የሀገር ፍቅር ስሜታቸውን በእንባ ይገልፃሉ።

የቀድሞው ወታደር በተለይም ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በሰሜን ዕዝ በሚገኘው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ላይ የተፈፀመውን የክህደት በትር በቀጥታ የተካፈሉ፣ አስቸጋሪውን የቆላ ተንቤን መልክዓ ምድር ችለው የታገሉና የተጋፈጡ ሲሆን በውቅቱ የደረሰባቸውን ሰቆቃና ግፍ ዛሬም ድረስ በቁጭት መንፈስ ሆነው ነው የሚያስታውሱት ።

ከጦር ሜዳ የቀጠለው ትጋታቸው ዛሬም ድረስ ከገጽታቸው ያልጠፋው የቀድሞ ወታደር ሻምበል ረዲ በ 2013 ዓ.ም ከውትድርናው ዓለም በጡረታ ቢገለሉም ወደ ትውልድ አካባቢያቸው በመመለስ በተለያዩ የመንግስት የስራ ሀላፊነት ከማገልገላቸውም ባለፈ ሰዎችን የመርዳትና ችግራቸውን የመካፈል ፣አስታራቂ ሽማግሌ፣ የዝግጅቶች አድማቂ፣ የልማት አርበኛ በመሆን ዛሬም ድረስ በትጋታቸው ቀጥለዋል።

በጡረታ ከተገለሉበት ከ 2013 ዓ.ም ከመጋቢት ወር ጀምሮ በስልጤ ዞን አልቾ ዉሪሮ ወረዳ ሚሊሻ ጽህፈት ቤት ሀላፊ በመሆን በመከላከያ ሰራዊት አባልነት በቆዩባቸው ዓመታት ያካበቱትን እውቀትና ልምድ በመጠቀም አልፎ አልፎ የሚታዩ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ የመፍታት፣ የጽህፈት ቤታቸውን ስራ አፈጻጸም ከፍ ከማድረጋቸውም ባለፈ ወጣቶች አገራቸውን እንዲወዱና ስነ ምግባር እንዲኖራቸው በመምከርና እንደ አባት በመገሰጽ በወረዳው ማህበረሰብ ተወዳጅነትን አትርፈዋል ።

የዞኑ መንግስት ይህንን ልምዳቸውንና ትጋታቸውን በበለጠ ለመጠቀም እንዲቻል በማሰብ ባደረገው ጥረት ከ 2014 ዓ.ም ጀምሮ የዞኑ ሚልሻ ጽህፈት ቤት ሀላፊ በመሆን አገልግለዋል።

በሃላፊነት በቆዩባቸው ጊዜያት የዞኑን ሰላምና ጸጥታ ከማስጠበቃቸውም ባለፈ በተለያዩ ጊዜያት በዞኑ በሚዘጋጁ የተለያዩ ኩነቶች ላይ የክብር እንግዶችን በማጀብ እና ደህንነታቸውን በመጠበቅ ለፕሮግራሞች ድምቀት በመስጠት ይታወቃሉ።

በተለያዩ አካባቢዎች አልፎ አልፎ በግጦሽ መሬት፣ የድንበርና የቤተሰብ ግጭት በሚያጋጥምበት ጊዜም ቢሆን ለችግሮች አፋጣኝ መፍትሄ በማበጀት የመሪነትና የሽምግልና ሚናቸውን በመወጣት ሰላም በማውረድ አንቱታን አትርፈዋል።

"ዛሬ ላይ በጡረታ ብገለልም ሀገሬ ተደፈራ አልቀመጥም "የሚሉት ሻምበል ረዲ ለሀገር መከላከያ ሰራዊት በሚደረጉ ድጋፎች ላይ ግምባር ቀደም በመሆን የስልጤ ዞን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት የተለያዩ ድጋፎችን ባደረገበት ወቅት ግንባር ድረስ በማቅናት ስጦታዎችን ከማበርከታቸው ባለፈ ኢትዮጵያ ከውስጥና ከዉጭ ፈተናዎች በገጠሟት ያለፉት ወቅቶች ወጣቶች የሀገር መከላከያ ሰራዊት አባል እንዲሆኑ በመመልመልና በማሰልጠን ለአራት ተከታታይ ግዜያት በርካቶችን ወደ ግንባር ሸኝተዋል።

የዘማች የሠራዊት አባላትን ቤተሰቦች በመደገፍ የሚታወቁትና "ሰዎችን መርዳትና ችግራቸውን መካፈል ከፍተኛ ደስታ ይሰጠኛል "የሚሉት ሻምበል ረዲ በግንባር በቆዩባቸው አመታት ከደሞዛቸው በመቀነስ ለተማሪዎች ደብተር፣ እስክርቢቶ ፣ዩኒፎርምና ቦርሳ በመግዛት ድጋፍ ሲያደርጉ መቆየታቸውንና ይህንን በጎ ዓላማ በማስቀጠል የአቅም ውስንነት ላለባቸው ቤተሰቦችና ወላጅ አልባ ህፃናት ከትምህርት ገበታቸው እንዳይርቁ የተለያዩ ድጋፎችን ያደርጋሉ።

የዞኑ መንግስት የህብረተሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት ውስጥ ተሳታፊ በመሆን በተለይም በህብረተሰብ ተሳትፎ ለሚገነቡ ትምህርት ቤቶች፣ ጤና ተቋማት፣ የመንገድና ውሃ የመሳሰሉ የልማት ስራዎች በከተማ የሚኖረውን የነጋዴ ማህበረሰብ ፣ባለሃብቶችንና ታዋቂ ግለሰቦችን በማስተባበር የሚታወቁ ሲሆን ለአብነትም በቅርቡ በትውልድ አካባቢያቸው ለሚገነባው መለስተኛ ጤና ጣቢያ ከሌሎች ባልደረቦቻቸው ጋር በመሆን በርካታ ሚሊዮን ብሮችን በማሰባሰብ የጤና ጣቢያውን ግንባታ አስጀምረዋል።

"ወላጆች ልጆቻቸውን በስነ ምግባርና በእውቀት ኮትኩተው በማሳደግ የሀገር ፍቅር እንዲኖራቸው ማድረግ ይገባል" የሚሉት ሻምበል ረዲ ወጣቶችም ሀገራቸውን በመውደድ ከዚህ አለፍ ሲልም የሀገር መከላከያ ሰራዊት አባል በመሆን እናት ሀገራቸውን ማገልገል ይገባቸዋል ይላሉ።

በአሁኑ ወቅት ኑሮአቸውን በወራቤ ከተማ አስተዳደር ያደረጉት ሻምበል ረዲ የአምስት ልጆች አባትና የአንድ ልጅ አያት ሲሆኑ ልጆቻቸውን በስነ ምግባርና በሀገር ፍቅር ስሜት በማሳደግ በአካባቢው ማህበረሰብ አርአያ ናቸው።

✍️ ሙጂብ ጁሀር

የኢማም ሱጋቶ ዘይኔ የተቀናጀ አመራርና የ"ጎጎት" ስርዓትበ20ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመሪያ አጋማሽ የስልጤን ህዝብ የመሩት ኢማም ሱጋቶ ዘይኔ፣ አመራራቸው በሁለት ጠንካራ ምሰሶዎች ላይ የተመሰ...
12/07/2025

የኢማም ሱጋቶ ዘይኔ የተቀናጀ አመራርና የ"ጎጎት" ስርዓት

በ20ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመሪያ አጋማሽ የስልጤን ህዝብ የመሩት ኢማም ሱጋቶ ዘይኔ፣ አመራራቸው በሁለት ጠንካራ ምሰሶዎች ላይ የተመሰረተ ነበር፤ ይኸውም የፖለቲካ ብልሀታቸው እና የእምነት መሪነታቸው ነው።

"ጎጎት" የተሰኘው የአስተዳደር ስርዓታቸው፣ የስልጤንና የአካባቢውን ማህበረሰቦች በማሰባሰብ የጋራ ሰላምና ደህንነትን ለማስጠበቅ አስችሏል።

በጀግንነታቸውና በጦረኝነታቸው የውጭ ጥቃቶችን በመመከት ህዝባቸውን ሲከላከሉ፣ በ"ኢማምነታቸው" ደግሞ ፍትህን በማስፈን፣ የሞራል ልዕልናን በማላበስና የማህበረሰቡን ስነ-ምግባር በማነጽ ኢማም ሆነው አገልግለዋል።

📜 የስልጣኔ ማህተም የሆነው ታሪካዊው ፎቅ

የኢማም ሱጋቶ አስተዳደርና ስልጣኔ ህያው ምስክር የሆነው ታሪካዊው ፎቃቸው ሲሆን፣ ከ90-100 ዓመታት እድሜን አስቆጥሯል።

ይህ ፎቅ የመኖሪያቸው ማዕከል ብቻ ሳይሆን፣ ህዝቡን ያስተባበሩበትና የመሩበት የአስተዳደር ማዕከልም ነበር።

ፎቁ የኢማም ሱጋቶ አመራር ጥበብ ከእምነት ጽናት ጋር ሲዋሃድ ምን ያህል ጠንካራና ዘላቂ ማህበረሰብ መገንባት እንደሚቻል በተጨባጭ ያሳያል።

📜 የስነ-ህንጻ ጥበብና ባህላዊ ትስስር

የኢማም ሱጋቶ ፎቅ የተገነባው እንደ ሀበሻ ጥድ እና ቀርከሃ ባሉ የአካባቢው ቁሳቁሶች ሲሆን፣ አሰራሩ ከታሪካዊው የጅማው አባ ጅፋር ቤተ መንግስት ጋር ተመሳሳይነት ማሳየቱ በወቅቱ በነበሩት መሪዎች መካከል የነበረውን ጠንካራ ግንኙነት እና የልምድ ልውውጥ ያመላክታል።

ባለ አንድ ደረጃ፣ ሶስት በሮችና ሶስት መስኮቶች ያሉት ይህ ፎቅ፣ እያንዳንዱ አካሉ የራሱ ትርጉም ያለውና የስልጤን ህዝብ የስነ-ህንጻ ጥበብ፣ የአኗኗር ዘይቤና ማህበራዊ አደረጃጀት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ የኪነ-ህንጻ ጥበብ ውጤት ነው።

ይህ ታሪካዊ ቅርስ በስልጤ ዞን፣ ምዕራብ አዘርነት በርበሬ ወረዳ፣ ከወራቤ ከተማ 83 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ዱና የሚገኝ ሲሆን፣ በአሁኑ ሰዓትም በወረዳው አስተዳደር እንክብካቤ ይደረግለታል።

መረጃዎቹ ከተለያዩ ምንጮች የተገኙና ተጨምቀው የተፃፉ ናቸው። #የኢማምሱጋቶፎቅ #የስልጤታሪክ #የኢትዮጵያቅርስ #ታሪክ #ስልጣኔ

Address

Addis Ababa
Ababa
NO

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Silta Mass Media posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share