
27/07/2025
የስልጤ ማህበረሰብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በአብሮነት የመኖር ባህል የዳበረ ከመሆኑም ባለፈ የሄደበትን አካባቢ በማልማት የሚታወቅ ህዝብ ነው ሲሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ወ/ሮ ሙፈሪሀት ካሚል ተናገሩ ።
ሚኒስትሯ ይህንን ያሉት የስልጤ ልማት ማሕበር ለ2ኛ ጊዜ ያዘጋጀው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በስልጤ ዞን በአልቾ ውሪሮ ወረዳ በተካሄደበት ወቅት ነው ።
የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈርያት ካሚል በዚህ ወቅት እንዳሉት የስልጤ ማህበረሰብ የሄደበትን አካባቢ ከማልማት በተጨማሪ የትውልዱ አካባቢውንም የማልማትና የማሳደግ ሃላፊነት እንዳለበት ተናግረዋል።
ማህበረሰቡ በኢትዮጵያ ከሚገኙ ብሄር ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ጋር አብሮ የመኖር ባህልን ያዳበረ ከመሆኑም ባለፈ የሄደበትን አካባቢ በማልማት የጠንካራ የስራ ባለቤት መሆኑን አስመስክሯል ብለዋል።
የስልጤ ማህበረሰብ ጥንካሬ ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚደረገውን እንቅስቃሴ እውን ለማድረግ ያግዛል ያሉት ሚኒስትሯ የልማት ማህበሩ ከምስረታው ጀምሮ በአካባቢ የሚታዩ የጤና፣ የትምህርት የመንገድና የአረንጓዴ ልማት የመሳሰሉ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ከመቅረፉም ባለፈ የህብረተሰቡን ማህበራዊ ግንኙነት ለማጠናከር ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ገልፀዋል።
ዞኑ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የቱሪስት መዳረሻዎች ባለቤት በመሆኑ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን በማልማት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ መሰራት እንደሚገባ ተናግረዋል።
አቶ አደም ኑሪ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ፕላንና ልማት ቢሮ ሃላፊና የስልጤ ልማት ማህበር ምክትል ሰብሳቢ በበኩላቸው የስልጤ ልማት ማህበር ከተመሠረተበት 1994 ዓ.ም ጀምሮ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል።
የስልጤ ልማት ማህበር የማህበረሰቡን ችግር ለመቅረፍ በርካታ ስራዎችን ሲሰራ መቆየቱን የጠቀሱት ምክትል ሰብሳቢው ይህንን ተግባሩን በውጤታማነት ለማስቀጠል የአስር ዓመታት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።
የስልጤ ልማት ማህበር ከሚሰራቸው የልማት ስራዎች ጎን ለጎን የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የችግኝ ተከላ ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸው የልማት ማህበሩን እቅድ ከግብ ለማድረስ ተግባር ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል ።
የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ በበኩላቸው በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወነ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ካለው ፋይዳ በተጨማሪ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።
የስልጤ ልማት ማህበር ከሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች በተጨማሪ በየዓመቱ የሚከናወን የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አንዱ መሆኑን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው ሀገራዊ የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ ከተጀመረ ወዲህ በዞኑ ከ400 ሚሊዮን በላይ ችግኝ በመትከል የዞኑን የደን ሽፋን 19.5 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል ።
የዞኑ መንግስት ማህበሩ የሚያደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች በማገዝ የበኩሉን እንደሚወጣ ገልፀዋል ።
በመርኃግብሩ ላይ የተገኙት የአልቾ ውሪሮ ወረዳ ዋና አሰተዳዳሪ ወ/ሮ መህዲያ ሀሰን ወረዳው የአምስቱ የስልጤ ቀደምት እናቶች መገኛ ከዞኑ በቅርብ ርቀት የሚገኝ ፣ ለኑሮ ምቹ እንዲሁም በርካታ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች ባለቤት ከመሆኑም ባለፈ የተለያዩ የሰብልና የፍራፍሬ አይነቶችን ለማልማት ምቹ አካባቢ መሆኑን ተናግረዋል።
የስልጤ ልማት ማህበር ባዘጋጀው ሁለተኛው ዙር የችግኝ ተከላ መርሃግብር ላይ የተሳተፉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በበኩላቸው ሀገራዊ የአረንጓዴ ልማት ተግባር እውን ለማድረግ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ቀጣይ የስልጤ ልማት ማህበር (ስልማ 3) የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ፕሮግራም በዞኑ ከላንፉሮ ወረዳና ጦራ ከተማ አስተዳደር በጋራ የሚያዘጋጁ መሆኑም ተገልጿል ።
በመርሃ ግብሩ ላይ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚልን ጨምሮ የፌዴራል፣የክልል፣የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የስልጤ ብሔረሰብ ተወላጆች እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል።
በመጂብ ጁሃር