04/06/2026
ትላንት ማህበረሰባችን "የወደፊት እጣ ፈንታዬን ይወስንልኛል፣ የነገ ማንነቴን ይቅርጽልኛል” በሚል ሙሉ እምነት በሰላማዊ መንገድ ተሰልፎ የመረጠበት ሂደት፣ ህዝብ የመንግስት ፅኑ መሰረት፣ መንግስት ደግሞ የህዝብ መጠለያ ጥላ መሆናቸውን በተግባር ያሳየበት ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ ነው። ይህ ህዝባዊ መሰረት ግን ዘላቂና የማይናወጥ ሀገርን መገንባት የሚችለው፣ ዛሬ ላይ በትውልድ ግንባታ ላይ ስልታዊና ጠንካራ ስራ መስራት ሲቻል ብቻ ነው። ምክንያቱም የትውልድ ግንባታ የዘላቂ ሀገር ግንባታ ዋና ምሰሶና ቀዳሚው መነሻ ነው! ትውልድ መገንባት ማለት የሀገርን ነገ መገንባት ነው። ትላንት ወላጆች ለሀገራቸው የወደፊት እጣ ፈንታ በምርጫ ካርዳቸው ያሳዩትን ቁርጠኝነት፣ ዛሬ በዕውቀት፣ በስነ-ምግባር፣ በሀገር ፍቅር እና በበሰለ አስተሳሰብ የተቃኘ ትውልድ በመቅረጽ ማስቀጠል ይገባል።
መንግስት የወጣቱን አቅም፣ የፈጠራ ክህሎት እና የሀሳብ ልዕልና የሚያጎለብቱ ምቹ ሁኔታዎችንና መድረኮችን በስፋት በማመቻቸት እውነተኛ ጥላነቱን ማረጋገጥ ይኖርበታል፤ ማህበረሰቡም በበኩሉ ይህንን ትውልድ በቅንነትና በስራ ወዳድነት በማነጽ የመንግስትና የሀገር ፅኑ መሰረትነቱን በተግባር ሊያሳይ ይገባል።
ይህ በትውልድ ግንባታ ላይ የሚደረግ ከፍተኛ ትኩረት፣ ህዝብና መንግስትን ይበልጥ በማስተሳሰር ምክንያታዊ፣ ፈተናዎችን የሚቋቋምና ወደ መልካም አጋጣሚ የሚቀይር ሀገር ወዳድና ጠንካራ ትውልድ ለመፍጠር ያስችላል። ምክንያቱም ትውልድ ሲገነባ ሀገር በዘላቂነት ትገነባለች፤ መንግስትም እውነተኛ ጥላ፣ ህዝብም የማይናወጥ መሰረት ሆኖ ሀገራችንን ወደ ታላቅ ከፍታ ያሸጋግራታልና!