28/05/2026
!
በፖለቲካ መድረክ ላይ ትልቁና የመጨረሻው ዳኛ ሕዝብ ነው። ሕዝብ ደግሞ የሚሰጠውን ፍርድ በምሬት ወይም በጩኸት ሳይሆን በሰላማዊ መንገድ በምርጫ ካርዱና ለልማት በሚያሳየው ዝግጁነት ይገልጻል።
ቁሕዴፓ አመራሮች በአዲስ አበባ መግለጫ አውጥተው የፈጠሩት ሁካታ ካለፈው የታሪክ ስህተት ያልተማረና የቁጫን ሕዝብ ንቃተ-ሕሊና የናቀ የከሰረ ፖለቲካ ማሳያ ነው።
ቁሕዴፓ በቁጫ አካባቢ በሕዝብ ዘንድ ሙሉ በሙሉ መተፋቱንና የመደገፊያ መሬት ማጣቱን በሚገባ ያውቀዋል። ለአመታት የሕዝብን ስሜት በመኮርኮርና በማንነት ስም በመነገድ የቆየው የፖለቲካ ቁማር ማብቂያው ላይ ደርሷል።
ፓርቲው በምርጫ ሜዳው ላይ ወርዶ መወዳደርና ማሸነፍ እንደማይችል ሲረዳ መሸነፉን አስቀድሞ በማረጋገጡ ገና ምርጫው ሳይካሄድ የሽንፈት ማስተባበያ ሰበብ ማዘጋጀት ጀምሯል።
የሕግ አንቀጾችን መጥቀስና ተገለልን ማለት ሕዝባዊ መሠረት ማጣትን ለመሸፈን የተዘረጋ የሽንፈት መጋረጃ ነው።
የቁጫ ሕዝብ ዛሬ የትናንቱን የውዥንብር ፖለቲካ ወደ ኋላ ጥሏል። በአካባቢው ለብልጽግና ፓርቲ የወጣውና የታየው ተዓምራዊ የሕዝብ ማዕበል የሚያረጋግጠው አንድ እውነት አለ። ሕዝቡ የሚፈልገው ጩኸት ሳይሆን ልማት፣ ሁከት ሳይሆን ሰላም፣ መገለልን ሳይሆን አብሮነትን ነው።
ያ የታምር ሰልፍ ለቁሕዴፓ አመራሮች የፖለቲካ ሞት የዕርድ አዋጅ ነበር። ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ለብልጽግና ያለውን ታማኝነትና ድጋፍ ሲያሳይ፣ ተቃዋሚዎች የወደፊት ዕጣ ፈንታቸው ጨለማ መሆኑን ተረዱ።
ከዚህ ማዕበል ማምለጥ እንደማይችሉ ሲያውቁም ምርጫው እንዲራዘም ወይም እንዲሰረዝ መጮኽን እንደ ብቸኛ አማራጭ ወሰዱት።
እውነተኛ የሐሳብ ልዕልና ያለው ፓርቲ የሕዝብን ድምፅ አይፈራም ምርጫ እንዲራዘምም አይማጸንም። የቁሕዴፓ ጩኸት የጥንካሬ ሳይሆን የከፍተኛ ፍርሃት መግለጫ ነው። መሸነፍን በፀጋ መቀበል ያቃተው ፖለቲካ፣ ተቋማትንና ሥርዓቱን በመወንጀል የራሱን ውድቀት ለማስታገስ ይሞክራል።
የሕዝብን ልብ ማሸነፍ አቅቶት፣ በምርጫ ሳጥን ውስጥ የሚጠብቀውን ውርደት በመፍራት አዲስ አበባ መሽጎ የሽንፈት መግለጫ የሚያረቅ የከሰረ ኃይል አለ።
የቁጫ ሕዝብ ወደ ኋላ አይመለስም ድምፁንና ውሳኔውን በተግባር አሳይቷል። የቁሕዴፓ ጩኸትም ቀድሞ የተረጋገጠ ሽንፈትን በጩኸት ለመቀየር የሚደረግ የሰነፎች የመጨረሻ ትግል ብቻ ነው።