22/09/2025
የጸሎት መጀመሪያ
***
"ከዓመፀኛ ከንፈር ከሸንጋይም አንደበት፥ አቤቱ፥ ነፍሴን አድናት።" (መዝ. 119/120፥2)
***
ከእግዚአብሔር ፊት ስንቆም ቀድመን ስለምን እንጸልያለን? ብለን እንጠይቃለን። በርግጥ መንፈሳዊ ሕይወት በደረቅ ፎርሙላ አይመራም። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ፊት ስንቀርብ ቀድመን ልናስበው የሚገባን ነገር አለ፦ እግዚአብሔርን በሽንገላ ኅሊና እና አንደበት እንዳንቀርበው። እግዚአብሔር ሽንገላን ይጸየፋልና። ሽንገላ ማለትም ያልሆኑትም መስሎ መታየት፣ የማያምኑትን እንደሚያምኑ ሆኖ ለማሳየት መሞከር፣ ከልብ ያልሆነ ምስጋና እና ውዳሴን ማቅረብ ነው። ወዳጄ በእግዚአብሔር ፊት ከልብህ ያልሆነ ነገርን ይዘህ ከምትቀርብ ዝም ብለህ አንገትህን ዝቅ አድርገህ በብዙ ድካምህ የተነሣ ከእግዚአብሔር ፊት ለመቆም የማትችል ነገር ግን ከእግዚአብሔር ቸርነት እና ትእግስት የተነሣ በፊቱ የቆምህ መሆኑን አውቀህ "ኃጢአተኛ መሆኔን በጥቂቱ አውቃለሁ፤ በሚገባ እንዳውቅ ደግሞ አንተ ግለጥልኝ፤ በፊትህ ያልሆንኩትን መስዬ እልዳልቆም፣ አንተንም እንዳልሸነግልህ ስለራሴም ስለአንተም እውነቱን የማውቅበትን ቅን ኅሊና ስጠኝ፤ አርነትን የሚያወጣ እውነትህን ግለጥልኝ" ብሎ መለመን ይሻላል። ከዚያ ቀጥሎ ለተደረገልን መልካም ነገር ሁሉ አመስግነን የምንፈልገውን ሳይሆን የሚያስፈልገንን ይሰጠን ዘንድ እንደ አባት መጠየቅ ይገባል። ከሽንገላ አንደበት ከወጣን እግዚአብሔር በድካማችን ይረዳናል፤ ኃይል የእርሱ ነውና። በግርጥም ከሽንገላ አንደበት የሚያድነንም እርሱ ነው፤ ክቡር ዳዊት ""ከዓመፀኛ ከንፈር ከሸንጋይም አንደበት፥ አቤቱ፥ ነፍሴን አድናት፤" እንዳለ። (መዝ. 119/120፥2)"