24/02/2026
የሠላም በር‼
ሳውዲ አረቢያ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል የተፈጠረውን ወታደራዊ ውጥረት ለማርገብ ጥረት እያደረገች መሆኑ ተሰምቷል‼
በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል እየታየ የመጣውን እና ቀጠናዊ ስጋት የደቀነውን ወታደራዊ ውጥረት ለማርገብ ሳውዲ አረቢያ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት መጀመሯ ተነግሯል። በተለይም በዚህ የካቲት ወር የሳውዲ መንግስት ሁለቱን ሀገራት ወደ ንግግር ጠረጴዛ ለመመለስ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል።
የሳውዲ አረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለስልጣናት በቅርቡ በአዲስ አበባ እና በአስመራ ባደረጉት ጉብኝት፣ የሁለቱን ሀገራት መሪዎች እና ከፍተኛ አመራሮች በተጠናጠል በማነጋገር ለማግባባት ጥረት አድርገዋል። ይህ የሳውዲ ጥረት ትኩረት ያደረገው በሁለቱ ሀገራት ድንበር አካባቢ እየታየ ነው የተባለውን የኃይል ማሰባሰብ ሂደት እንዲቆም እና ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ለማድረግ እንደሆነ ተገልጿል።
ሳውዲ አረቢያ በሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ውስጥ ቁልፍ ሚና ስትጫወት የመጀመሪያዋ አይደለም። እ.ኤ.አ. በሴፕቴምበር 2018 በንጉስ ሰልማን ቢን አብዱላዚዝ አደራዳሪነት፡
📌 የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ በጂዳህ ተገኝተው ታሪካዊውን "የጂዳህ የሰላም ስምምነት" መፈራረማቸው ይታወሳል።
📌 ይህ ስምምነት ለሁለት አስርት ዓመታት የዘለቀውን የ"ጦርነትም የሰላምም የሌለበት" ሁኔታ መቋጫ የሰጠ ነበር።
አሁን እየተደረገ ያለው ጥረትም ያንን የሰላም መንፈስ ለመታደግ እና የቀይ ባህር ቀጠናን ደህንነት ለማስጠበቅ ያለመ መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ።
የውጥረቱ መነሻ ምንም እንኳን በይፋ የተገለጸ ምክንያት ባይኖርም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ በኩል የሚሰሙ "የባህር በር" ጥያቄዎች እና ከሰሜኑ ጦርነት ማብቃት በኋላ በሁለቱ ሀገራት መካከል የተፈጠረው የፖለቲካ ቅዝቃዜ ለውጥረቱ መባባስ እንደ ምክንያት ይጠቀሳሉ።
የሳውዲ አረቢያ የሰላም ጥረት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን አለመግባባት ፈቶ ወደ ቀድሞው ወዳጅነት ይመልሳቸው እንደሆነ የሚጠበቅ ይሆናል።
Wasu Mohammed - Mereja