Yekidanemihret lejoch

Yekidanemihret lejoch የመንግስቱ ወራሾች

11/04/2026
11/04/2026

በሲኦል ያሉትን ነብሳት የጎበኘው ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛንም ቤት ይጎብኝ 🙏
#ትንሳዔ
#ስቅለት

11/04/2026

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤን በማስመልከት ያስተላለፉት መልዕክት ።

የቅዱስነታቸው አባታዊ መልዕክት እንደሚከተለው ይነበባል።
ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ ኣቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት፤
በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ ኣምላክ ኣሜን፡-

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፣
በቤዛዊ መሥዋዕትነቱ ከሞተ ኃጢኣት ታድጎ የትንሣኤ ሙታንን በር የከፈተልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ኣደረሰን ኣደረሳችሁ!

‹‹ወኣነ እሜጡ ነፍስየ ቤዛ ኣባግዕየ ከመ ካዕበ ኣንሥኣ፤
ዳግመኛ ኣነሣት ዘንድ ነፍሴን የበጎቼ ቤዛ ኣድርጌ እሰጣለሁ (ዮሓ 10÷17)

ጌታችን ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰብኣዊ ክዋኔው ሰው ቢሆንም በመለኮታዊ ክዋኔው የኣብና የመንፈስ ቅዱስ ቃል ወይም ወልደ እግዚአብሔር ነው፤
በመሆኑም በሰብኣዊ ክዋኔው መዋች ሲሆን በመለኮታዊ ክዋኔው ተነሽና ኣንሺ ነው፤ ከዚህ ኣንጻር ሥግው ቃል ሁለቱንም ተግባራት በኣንድ ኣካልና ክዋኔ የመፈጸም ሥልጣን ኣለው፤ ይህም በመሆኑ ራሴን የማኖርና የማንሣት ሥልጣን ኣለኝ በማለት እውነታውንና ምንነቱን ኣሳየ፤
ጌታችን ይህንን ኣስመልክቶ ከመሞቱና ከመነሣቱ በፊት ለቅዱሳን ሓዋርያት በተደጋጋሚ ኣስረድቶኣል፤ ስለሆነም የጌታችን ሞትና ትንሣኤ ድንገተኛና የግድ ሳይሆን ታውቆ ያደረና የውድ እንደሆነ ከዚህ እውነታ እንረዳለን፤

ጌታችን ይህንን ተግባር በውድ ፈቃዱ የፈጸመው በእግዚአብሔር ኣሰራር ከዚህ ውጭ የዓለም ድኅነት የሚከናወንበት ዕድል ስለሌለ ነው፤ በእግዚአብሔር ኣሰራር ኃጢኣትና በደል የሚሰረዘው በቤዛዊ መሥዋዕት ብቻ እንደሆነ ከብሉይ ኪዳን ጀምሮ በነበረው የቤዛዊ መሥዋዕት ኣቀራረብ የታወቀ ነው፤

በመሆኑም የሰውን ምልኣተ ኃጢኣት ሙሉ በሙሉ ሰርዞ ሰውን ከሞት ቅጣት ነጻ ለማውጣት ብቃት ያለው ቤዛዊ መሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ነበረበት፤ ይሁን እንጂ ለዚህ ዓይነቱ ቤዛዊ መሥዋዕት ብቁ የሆነ ከፍጡራን ወገን ስላልተገኘ ‹‹ለሊሁ መሥዋዕት፣ ወለሊሁ ሠዋዒ፣ ወለሊሁ ተወካፌ መሥዋዕት ማለትም›› ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ መሥዋዕት ኣቅራቢ ሊቀ ካህናት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት ኣምላክ ሆኖ የቤዛነታችንን መሥዋዕት ራሱ በራሱ ለራሱ ኣቀረበ››፤
በዚህ ቤዛዊ መሥዋዕትም እኛን ከሞት ቅጣት ነጻ ኣደረገን፤ትንሣኤያችንንም በትንሣኤው ኣበሰረ፤ በክርስትና ሃይማኖት የሚገኝ ፍጹም ድኅነትና ነጻነት በዚህ ቤዛዊ መሥዋዕት ላይ የተመሠረተ ነው፤
የተወዳደችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን
ምእመናንና ምእመናት!

ጌታችን በትንሣኤው ትንሣኤያችንን ሲያበስረን የትንሣኤ ሰዎች ሆነን በመንፈስና በሞራል በማደግ ብርሃናተ ዓለም ልንሆን እንጂ እንደገና የጨለማው ኃይል መሳሪያዎች ልንሆን ኣይደለም፤ የሞቱና የትንሣኤው ምስጢር በንጹሁ ኅሊናችን ካስተዋልነው ውስጣችን እሱን ለመቀበል የሚያዳግተው ኣይደለም፤

ከዚህ ኣንጻር በትንሣኤው ኣምነን ትንሣኤያችንን እየተጠባበቅን የምንገኝ ሕዝበ ክርስቲያን በቅን ኣስተሳሰብ፣በርቱዕ ኣእምሮና በኃይለ ሃይማኖት እየታገዝን ጨለማውን ዓለም ወደብርሃን ለመለወጥ መጣርና መትጋት ይጠበቅብናል፤
የጨለማው ዓለም መንፈስ ሊያጠፋን ካልሆነ በቀር እንደማይጠቅመን በተጨባጭ የምናውቀው ነው፤ወደድንም ጠላንም ያለን ብቸኛ ኣማራጭ ብርሃንን መከተል ነው፤ እሱም እግዚአብሔር ነው፤በብርሃን የሚመላለስ እንደማይጐዳ በእግዚአብሔር የሚኖርም ተጐድቶ ኣያውቅምና ነው፤
ዓለም እንደ ኣጠቃላይ በጨለማ ተውጦ ሲተረማመስ የሚታየው ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ምርጫው ስላደረገ ነው፤ ስለሆነም የኛ ምርጫ ብርሃን የሆነውን እግዚአብሔር እንዲሆን የቤተ ክርስቲያን የዘወትር ጥሪ ነው፤
በመጨረሻም፡-

የትንሣኤ በዓላችንን ስናከብር ዓለም በክፋቱ ያጨለመባቸውን ወገኖች ጦማችው እንዳይውሉ ካለን ከፍለን የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የታረዙትን በማልበስና የዕለቱ ደስታ ተካፋይ እንዲሆኑ በማድረግ ቀኑ ለሁላችንም ፍጹም ብርሃን ሆኖ ይውል ዘንድ ክርስቲያናዊ ግዴታችንን እንድንወጣ ጥሪያችንን በእግዚአብሑር ስም እናስተላልፋለን፤

መልካም የትንሣኤ በዓል ያድርግልን!!
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ”
“ወስብሐት ለእግዚአብሔር”
ኣሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ
ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣
ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

11/04/2026

ተንሥአ (ተነሥቷል) ሉቃ 24፥6
------------------------
በመልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ (ቆሞስ) የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ
÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷

ነገረ ክርስቶስን በስተማርን ጊዜ ኹሉ ቅዱሳን መላእክትን እንዘክራቸዋለን።

ኢየሱስ ክርስቶስን ተጸነ፣ ተወለደ፣ ተሰደደ፣ ከስደት ተመለሰ እያሉ ብሥራትን ያመጡ፣ በሚጾምበት ጊዜ ቀርበው ያገለገሉ ማቴ 4፤ በሰርግ ቤት ሳለ መጥተው ሰማይ ዙፋንህ ምድር የእግርህ መረገጫ ስትሆን በተናቀች ጎጆ በሰርግ ቤት መገኘትህ ምን ይደንቅ? ብለው ያደነቁት (ሃ.አ.ዘቅዱስ ኤፍሬም)፤ የእኛን መከራ ሊቀበል ጊዜው በመድረሱ በጸሎተ ሐሙስ ሲጸልይ "አባት ሆይ ይኽች ጽዋዕ ከእኔ ትለፍ..." በሚል ጊዜ ከሰማይ መጥተው ያበረቱት (ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም) በማለት የሰገዱት) ሉቃ 22፤ ጎኑ በጦር በተወጋ ጊዜ በወርቅ ጽዋዕ ቀድተው ዓለምን የረጩት፣ በተነሣም ጊዜ "ተነሥቷል በዚህ የለም" ብለው ምሥራችን የሰበኩት፣ ወደ ሰማይ ሲያርግ ሲሔድ እንዳያችሁት እንዲሁ ይመጣል ብለው ለደቀ መዛሙርቱ የመሠከሩ፣ ዳግመኛም ሲመጣ መለከት እየነፉ "ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት... ንቃህ መዋቲ" በማለት አዋጅ የሚናገሩ መላእክተ ብሥራት (አብሣሪ መላእክት) ናቸው። የኢየሱስን ሥጋ ሽቱ ቀብተው ለመሰናበት ፎቅሩ ሲያንገበግባቸው አድረዋልና ገና ሳይነጋ ገሥግሠው ፍለጋ ሒደው ሥጋውን አጥተው የመቃብሩን ባዶ መሆን ተመልክተው ሲጨነቁ ለነበሩ ሴቶች፦

" ? ፤ ተዘከራ ዘይቤለክን በገሊላ ሀለዎ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይግባእ ውስተ እደ ሰብእ፤ ወይሰቅልዎ፤ ወይቀትልዎ፤ ወይትነሣእ በሣልስት ዕለት ። "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ ? #አንድም ስለምን ትሹታላችሁ? ተነሥቷል እንጂ በዚህ የለም ። የሰው ልጅ በኃጥአን እጅ ተላልፎ ሊሰጥና ሊሰቀል፣ ሊገደል በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ግድ ነው እያለ ገና በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንደ ተናገረ አስቡ ።"ሉቃ 24:5-7 አሏቸው።

ዐራቱም ወንጌላውያን ይኽንን የምሥራች ዘግበውልናል::
“መልአኩም መልሶ ሴቶቹን አላቸው! እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና፤ እንደ ተናገረ ተነሥቷልና በዚህ የለም፤ የተኛበትን ስፍራ ኑና እዩ:: ፈጥናችሁም ሂዱና፡፡ ከሙታን ተነሣ እነሆም ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል በዚያም ታዩታላችሁ ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው›› ማቴ ፳፰ እነርሱም መልአክ ዐይተዋልና እየፈሩ ትንሣኤውን ሰምተዋልና ደስ እያላቸው ለደቀ መዛሙርቱ ይነግሯቸው ዘንድ ፈጥነው ሔደው የክርስቶስን ትንሣኤ አበሠሩ።

“ወደ መቃብሩም ገብተው ነጭ ልብስ የተጎናጸፈ ጎልማሳ በቀኝ በኩል ተቀምጦ አዩና ደነገጡ፡፡ እርሱ ግን አትደንግጡ ፤ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ትፈልጋላችሁ ፤ ተነሥቷል በዚህ የለም! ነገር ግን ሄዳችሁ ለደቀ መዛሙርቱ #ለጴጥሮስም ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፤ እንደ ነገራችሁ በዚያ ታዩታላችሁ ብላችሁ ንገሩአቸው አላቸው>> ብሎ አስፍሮታል:: ማር ፲፬, ፭

ደግሞ “እነርሱም በዚህ ሲያመነቱ እነሆ ሁለት ሰዎች የሚያንጸባርቅ ልብስ ለብሰው ወደ እነርሱ ቀርበው "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቷል እንጂ በዚህ የለም:: የሰው ልጅ በኀጢአተኞች እጅ ታልፎ ሊስጥና ሊስቀል በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ግድ ነው እያለ ገና በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንደ ተናገረ አስቡ" አሉአቸው። ሉቃ 28: 6

"መግደላዊት ማርያም ሁለቱን መላእክት እንዳየችና ከእነርሱም ጋር እንደተነጋገረች ሲገልጽ "ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች: ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች:: እነርሱም አንቺ ሴት ስለ ምን ታለቅሻለሽ? አሉአት::. ሲል መዝግቦልናል:: ዮሐ 20:10

ከላይ እንደተመለከትነው ዐራቱ ወንጌላውያን ትንሣኤውን በተለያየ መንገድ ጽፈዋል፤ ሊቃውንት በትርጓሜ እንዲህ ሲሉ አስተርቀውታል ፣ #ማቴዎስ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አዩ ይላል፤ #ማርቆስ ብዙ ሴቶች በውስጥ አንድ መልአክ አዩ ይላል፤ #ሉቃስ ብዙ ሴቶች ሁለት መላእክት አዩ ይላል #ዮሐንስ አንዲት ሴት ሁለት መላእክት አየች ይላል፤ ይህን አለ ቢሉ አይጣላም ከማታው ጀምረው ሊመላለሱ አድረዋል በተለያየ ቦታ አይተው ተመልሰዋል፤ #አንድም እንደ ማቴዎስ ነው ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አይተው ሲመለሱ:: እንደ ማርቆስ ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በውስጥ አንድ መልአክ አይተው ተመልስዋል:: #ሉቃስ ቦታ ሳይለያዩ ብዙ ሴቶች ሁለት መላእክት አዩ አለ:: #ዮሐንስ አንዲት ሴት ሁለት መላእክት አየች አለ፤ ብሎ

#አንድም ነገር እንደ ዮሐንስ አንዲት ሴት አይታ ሂዳ ለጴጥሮስና ለዮሐንስ #ነሥእዎ ጌታዬን ከመቃብር ወስደውታል የወሰዱበትን አላውቅም፡፡ ብላ ነገረቻቸው ጴጥሮስና ዮሐንስ አይተው ተመልስዋል ከዚህ በኋላ እንደ ማቴዎስ ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አይተው ሲመለሱ ጌታን በመንገድ አገኙት፤ ከጫማው ወድቀው ሰገዱለት ከዚህ በኋላ ሄዳችሁ ትንሣኤዬን ለሐዋርያት ንገሩ አላቸው ሔደው ነገሩ።

የትንሣኤ አይነቶች
የትንሣኤ አይነቶች ብዙ ናቸው። ትንሣኤ ዘኅሊና፣ ዘልቡና፣ ዘጊባዔ፣ ጊዜያዊ ትንሣኤና የክርስቶስ ትንሣኤ ይባላሉ። ዛሬ የምንመለከተው የጌታችንን ትንሣኤ ነው።

✍️

የክርስቶስ ትንሳኤው ለኛ ሕይወት የሚሰጥ ትንሣኤ ነው። አሥነሽ የሌለው ትንሣኤ ነው። ዳግም ሞት የሌለበት ትንሣኤ ነው። በሐዲስ ሥጋ የተደረገ ትንሣኤ ነው። ትንሣኤ ዘጉባኤ የማያስፈልገው ትንሣኤ ነው። በኅቱም መቃብር የተፈጸመ ትንሣኤ ነው። የትንሣኤያት ኹሉ በኵር ነው። 1ኛ ቆሮ 15፥20 አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል። ሞት በሰው በኩል ስለ መጣ ትንሣኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኖአልና። ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና። #ነገር ግን #እያንዳንዱ #በራሱ ተራ ይሆናል፤ ክርስቶስ እንደ #በኩራት ነው፥ በኋላም በመምጣቱ ለክርስቶስ የሆኑት ናቸው፤ እንዲል

ሐዋርያው ሁሉ በአዳም እንደሚሞት በክርስቶስ ደግሞ ሕያው እንደሚሆን አስረግጦ ከተናገረ በኋላ "አይቴ ሀሎ ሞት ቀኖትከ ወአይቴ ሀሎ ሲኦል መዊኦትከ" 1ቆሮ 15፥55 በማለት ሞትና ሲኦል መሸነፋቸውን ገልጧል፡፡

✍️ የተነሳው እንደተናገረ #በሥልጣኑ ነው። ማቴ 28 ተመልከት እግዚአብሔር አይዋሽም። ዘኁ 23: ሐሰትን ይናገር ዘንድ ሰው አይደለም እንዲል
ሰው ጠዋት ቢናገር ማታ አይደግመውም፣ በተቀመጠበት አይገኝም። እግዚአብሔር ግን አይለወጥም። "እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም" እንዲል

✍️ የተነሣው ግን በሥልጣኑ ነው። ሌሎቹ ትንሤኤያት አሥነሽ ይሻሉ።

በመልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ (ቆሞስ) የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ
ሚያዝያ 3 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ,ኢትዮጵያ

#ትንሣኤ #ፋሲካ #ኢየሱስ #ክርስቶስ

11/04/2026
09/04/2026
05/04/2026
05/04/2026

ጥንተ ስቅለቱ ለመድኃኔዓለም

እንኳን ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥንተ ስቅለት ክብረ በዓል አደረሰን፣አደረሳችሁ!!!

በመ/ር ጌታቸው በቀለ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት በቀራንዮ ተሰቅሎ ሕይወቱን ለዓለም ቤዛ አድርጎ የሰጠው መጋቢት ፳፯ ቀን ነው፡፡

ይህ ቀን ስለ ክርስቶስ ሕማም፣ ስለመከራ መስቀሉና ስለሞቱ የተነገሩት ትንቢቶችና ምሳሌዎች ሁሉ የተፈጸሙበት ፤ ሰማያዊ አምላክ ስለ ሰው ልጆች ፍቅር ሲል ልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራዎችን የተቀበለበትና በሞቱ ሞትን ሽሮ የአዳምን ዘር ሁሉ ከሞት ሞት ያዳነበት፣ ለዓለሙ ሁሉ ፍቅሩን የገለጠበት፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙም ዓለምን ነፃ ያወጣበት፣ በአጠቃላይ ዐሥራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል ተቀብሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በገዛ ፈቃዱ የለየበት የስቅለቱና የሞቱ መታሰቢያ የሚከበርበት ቀን በመሆኑ “ጥንተ ስቅለት” ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓሉም በዓለ መድኃኔዓለም” እየተባለ በየዓመቱ በመድኃኔዓለም ስም በታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡

መድኃኔዓለም

ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷም ነፍስ ነሥቶ በተዋሕዶ ሰው ሆኖ የተወለደው አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ “የዓለም መድኃኒት” ነው፡፡ መድኃኔዓለም ማለት
ዓለምን ሁሉ የሚያድን፣ በደዌ ሥጋ በደዌ ነፍስ ተይዞ የሚማቅቀውን ዓለም የሚፈውስ፣ መድኃኒተ ሥጋ መድኃኒተ ነፍስ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ “እኛም አይተናል አባትም ልጁን የዓለም መድኃኒት ሊሆን እንደላከው እንመሰክራለን” ብሏል/፩ኛ ዮሐ.፬፥፲፬/፡፡ ነቢዩ ሲሳይያስም “ከእኔም በቀር ሌላ አምላክ የለም፤ እኔ ጻድቅ አምላክና መድኃኒት ነኝ ከእኔም በቀር ማንም የለም” /ኢሳ. ፵፭፥፳፩/፡፡ ነቢዩ ዳዊትም “እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤በምድርም መድኃኒትን አደረገ” ብሎ በትንቢት እንደተናገረ መድኃኔዓለም በማዕከለ ምድር በምትሆን በጎልጎልታ ተሰቅሎ መድኃኒተ ሥጋ መድኃኒተ ነፍስ ሰጠን /መዝ.፸፫፥፲፪-፲፫/፡፡ የሰማርያ ሰዎችም የመሰከሩት ይህንኑ ነው “በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደሆነ እናውቃለን” /ዮሐ.፬፥፵፪/፡፡

መጋቢት ፳፯ ቀን የሚከበረውን የመድኃኔዓለምን በዓል ጥንተ ስቅለቱ ነው ብለን የስቅለቱን መታሰቢያ በዓል ስናከብር በዚሁ ቀን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸሙትን ጸዋትወ መከራዎችና እሱ በመስቀል ላይ እያለ በሰማይና በምድር የተፈጸሙትን ተአምራት አብረን ልናስባቸውና ልብም ልንላቸው ይገባል፡፡ መጋቢት ፳፯ ቀን በዕለተ ዓርብ ከሦስት እስከ ዘጠኝ ሰዓት የተቀበላቸው መከራዎችም እጅግ በጣም ብዙዎች ናቸው፡፡ ጥቂቶቹን ለማስታወስ ያህል፣ በሚያሰቅቅና በሚዘገንን ሁኔታ በጅራፍ ተገርፎአል፤ መስቀሉን ተሸክሞ በቀራንዮ ተራራ እየወደቀ እየተነሣ፣ የገዢው የጲላጦስ ወታደሮችም እያዳፉት፣ ርኩስ ምራቃቸውንም እየተፉበትና እያፌዙበት ወደ ተራራው እንዲወጣ ተደርጎአል፡፡ ስለእሱ የተጻፈው የነቢያት ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ልብሱን ገፈው ከለሜዳ አልበሰውታል፡፡ በልብሱም ላይ ዕጣ ተጣጥለው ተካፍለውታል፧ የእሾህ አክሊል ጕንጕን በራሱ ላይ በማድረግ የሰማይና የምድር ንጉሥ እንዳልሆነ ሁሉ “ንጉሥ ሆይ! ሰላም ለአንተ ይሁን” እያሉ ተሳልቀውበታል፡፡ በመጨረሻም ጐኑን በጦር ወግተውታል፡፡ እጆቹን እና እግሮቹን በአምስቱ ችንካሮች (ቅንዋት) ቸንክረው በመስቀል ላይ ሰቅለውታል፡፡

በመስቀል ላይ እያለም ሰባት ዐረፍተ ነገሮችን ተናግሮአል፤ በጣም የሚያስደንቀው ጠላቶቹ እያሰቃዩት፣ እያንገላቱትና እየገደሉትም ሳሉ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው” ሲል የተናገረው ቃል ሲሆን የመጨረሻውም “እነሆ ሁሉም ነገር ተፈጸመ” በማለት ከተናገረ በኋላ ወዲያውኑ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በራሱ ፈቃድ ለይቶ ሞት የማይገባው አምላክ ለሰው ልጆች ሕይወት ሲል ራሱን ለሞት አሳልፎ ሰጠ፡፡

የጌታችን ጥንተ ስቅለት

ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለው በዕለተ ዓርብ ሲሆን ከመቃብር የተነሣውም በዕለተ እሑድ በመሆኑ፤ ስቅለት ከዕለተ ዓርብ፣ ትንሣኤም ከዕለተ እሑድ፣ ዕርገት ደግሞ ከዕለተ ሐሙስ እንዳይወጡ፤ ሌሎቹም በዓላትና አጽዋማት በተወሰነላቸው ቀን እንዲውሉ ማድረግ ይቻል ዘንድ የቀድሞ አባቶችና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሰባት አዕዋዳት አዘጋጅተው እና ቀምረው ሁሉም ሥርዐቱን ጠብቆ ድርጊቱ በተፈጸመበት ቀን እንዲከበር ወስነዋል፡፡ በዚህም መሠረት “ጥንተ ስቅለቱ" መጋቢት ፳፯ ቀን በየዓመቱ እየታሰበ በዓለ ስቅለቱ ደግሞ ከሰሙነ ሕማማቱ ጋር በዓመት አንድ ጊዜ በዕለተ ዓርብ በጾምና በጸሎት እንዲሁም በአክፍሎትና በስግደት እንዲከበር በማድረግ ሕግና ሥርዓት ስለሠሩ በዚሁ መሠረት ሲፈጸም ኖሯል፡፡ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡

እንደ ማጠቃለያ

ጥንተ ስቅለቱ (በዓለ ስቅለት) ክርስቲያኖች ከማዕሠረ ኃጢአት የተፈቱበት፣ ከሰይጣን አገዛዝ ነጻ የወጡበት ዐቢይ በዓል ነው፡፡ ስለሆነም በዓለ ስቅለትን የምናከብረው ክርስቲያናዊ ተግባርን በመፈጸም መድኃኔዓለም ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ሲል በመስቀል ተሰቅሎ ያደረገልን ርኅራኄ፣ ቸርነት፣ መድኃኒትነት፣ በጠቅላላው በደሙ የገዛን መሆኑን በመገንዘብ መሆን አለበት፡፡ “እንግዲህ ይህ የእግዚአብሔር ድኅነት ለአሕዛብ እንደተላከ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን” እንዲል/የሐዋ.፳፰፥፳፰/፡፡ የጥንተ ስቅለቱና መስቀሉም ምስጢር ዓለምን የማዳን ምስጢር ስለሆነ፤ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የስቅለት በዓል የምናከብረው መሠረቱ መጋቢት ፳፯ ቀን እንዲሁም በሰሙነ ሕማማት በስቅለት ዕለት ምእመናን በቤተክርስቲያን በመገኘት መድኃኔዓለምን እየተማጸኑ ዓለምን ለማዳን የተቀበለውን መከራ መስቀል እያስታወሱ እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሥራ እየሠሩ በዓሉን በድምቀት ማክበር ይገባል፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዋቤ መጻሕፍት

✍ መጽሐፍ ቅዱስ
✍ ሃይማኖት አበው
✍ ድርሣነ ማኅየዊ
✍ ግብረ ሕማማት
✍ ከስቅለት እስከ ትንሣኤ
የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/

Address

Ayer Tena
Addis Ababa
KIDANEMIHRETENATE

Opening Hours

Monday 09:00 - 17:00
Tuesday 09:00 - 17:00
Wednesday 09:00 - 17:00
Thursday 09:00 - 17:00
Friday 09:00 - 17:00
Saturday 09:00 - 17:00
Sunday 09:00 - 17:00

Telephone

+251925171704

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Yekidanemihret lejoch posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share

Category