11/04/2026
ተንሥአ (ተነሥቷል) ሉቃ 24፥6
------------------------
በመልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ (ቆሞስ) የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ
÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷÷
ነገረ ክርስቶስን በስተማርን ጊዜ ኹሉ ቅዱሳን መላእክትን እንዘክራቸዋለን።
ኢየሱስ ክርስቶስን ተጸነ፣ ተወለደ፣ ተሰደደ፣ ከስደት ተመለሰ እያሉ ብሥራትን ያመጡ፣ በሚጾምበት ጊዜ ቀርበው ያገለገሉ ማቴ 4፤ በሰርግ ቤት ሳለ መጥተው ሰማይ ዙፋንህ ምድር የእግርህ መረገጫ ስትሆን በተናቀች ጎጆ በሰርግ ቤት መገኘትህ ምን ይደንቅ? ብለው ያደነቁት (ሃ.አ.ዘቅዱስ ኤፍሬም)፤ የእኛን መከራ ሊቀበል ጊዜው በመድረሱ በጸሎተ ሐሙስ ሲጸልይ "አባት ሆይ ይኽች ጽዋዕ ከእኔ ትለፍ..." በሚል ጊዜ ከሰማይ መጥተው ያበረቱት (ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም) በማለት የሰገዱት) ሉቃ 22፤ ጎኑ በጦር በተወጋ ጊዜ በወርቅ ጽዋዕ ቀድተው ዓለምን የረጩት፣ በተነሣም ጊዜ "ተነሥቷል በዚህ የለም" ብለው ምሥራችን የሰበኩት፣ ወደ ሰማይ ሲያርግ ሲሔድ እንዳያችሁት እንዲሁ ይመጣል ብለው ለደቀ መዛሙርቱ የመሠከሩ፣ ዳግመኛም ሲመጣ መለከት እየነፉ "ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት... ንቃህ መዋቲ" በማለት አዋጅ የሚናገሩ መላእክተ ብሥራት (አብሣሪ መላእክት) ናቸው። የኢየሱስን ሥጋ ሽቱ ቀብተው ለመሰናበት ፎቅሩ ሲያንገበግባቸው አድረዋልና ገና ሳይነጋ ገሥግሠው ፍለጋ ሒደው ሥጋውን አጥተው የመቃብሩን ባዶ መሆን ተመልክተው ሲጨነቁ ለነበሩ ሴቶች፦
" ? ፤ ተዘከራ ዘይቤለክን በገሊላ ሀለዎ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይግባእ ውስተ እደ ሰብእ፤ ወይሰቅልዎ፤ ወይቀትልዎ፤ ወይትነሣእ በሣልስት ዕለት ። "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ ? #አንድም ስለምን ትሹታላችሁ? ተነሥቷል እንጂ በዚህ የለም ። የሰው ልጅ በኃጥአን እጅ ተላልፎ ሊሰጥና ሊሰቀል፣ ሊገደል በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ግድ ነው እያለ ገና በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንደ ተናገረ አስቡ ።"ሉቃ 24:5-7 አሏቸው።
ዐራቱም ወንጌላውያን ይኽንን የምሥራች ዘግበውልናል::
“መልአኩም መልሶ ሴቶቹን አላቸው! እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና፤ እንደ ተናገረ ተነሥቷልና በዚህ የለም፤ የተኛበትን ስፍራ ኑና እዩ:: ፈጥናችሁም ሂዱና፡፡ ከሙታን ተነሣ እነሆም ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል በዚያም ታዩታላችሁ ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው›› ማቴ ፳፰ እነርሱም መልአክ ዐይተዋልና እየፈሩ ትንሣኤውን ሰምተዋልና ደስ እያላቸው ለደቀ መዛሙርቱ ይነግሯቸው ዘንድ ፈጥነው ሔደው የክርስቶስን ትንሣኤ አበሠሩ።
“ወደ መቃብሩም ገብተው ነጭ ልብስ የተጎናጸፈ ጎልማሳ በቀኝ በኩል ተቀምጦ አዩና ደነገጡ፡፡ እርሱ ግን አትደንግጡ ፤ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ትፈልጋላችሁ ፤ ተነሥቷል በዚህ የለም! ነገር ግን ሄዳችሁ ለደቀ መዛሙርቱ #ለጴጥሮስም ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፤ እንደ ነገራችሁ በዚያ ታዩታላችሁ ብላችሁ ንገሩአቸው አላቸው>> ብሎ አስፍሮታል:: ማር ፲፬, ፭
ደግሞ “እነርሱም በዚህ ሲያመነቱ እነሆ ሁለት ሰዎች የሚያንጸባርቅ ልብስ ለብሰው ወደ እነርሱ ቀርበው "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቷል እንጂ በዚህ የለም:: የሰው ልጅ በኀጢአተኞች እጅ ታልፎ ሊስጥና ሊስቀል በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ግድ ነው እያለ ገና በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንደ ተናገረ አስቡ" አሉአቸው። ሉቃ 28: 6
"መግደላዊት ማርያም ሁለቱን መላእክት እንዳየችና ከእነርሱም ጋር እንደተነጋገረች ሲገልጽ "ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች: ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች:: እነርሱም አንቺ ሴት ስለ ምን ታለቅሻለሽ? አሉአት::. ሲል መዝግቦልናል:: ዮሐ 20:10
ከላይ እንደተመለከትነው ዐራቱ ወንጌላውያን ትንሣኤውን በተለያየ መንገድ ጽፈዋል፤ ሊቃውንት በትርጓሜ እንዲህ ሲሉ አስተርቀውታል ፣ #ማቴዎስ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አዩ ይላል፤ #ማርቆስ ብዙ ሴቶች በውስጥ አንድ መልአክ አዩ ይላል፤ #ሉቃስ ብዙ ሴቶች ሁለት መላእክት አዩ ይላል #ዮሐንስ አንዲት ሴት ሁለት መላእክት አየች ይላል፤ ይህን አለ ቢሉ አይጣላም ከማታው ጀምረው ሊመላለሱ አድረዋል በተለያየ ቦታ አይተው ተመልሰዋል፤ #አንድም እንደ ማቴዎስ ነው ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አይተው ሲመለሱ:: እንደ ማርቆስ ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በውስጥ አንድ መልአክ አይተው ተመልስዋል:: #ሉቃስ ቦታ ሳይለያዩ ብዙ ሴቶች ሁለት መላእክት አዩ አለ:: #ዮሐንስ አንዲት ሴት ሁለት መላእክት አየች አለ፤ ብሎ
#አንድም ነገር እንደ ዮሐንስ አንዲት ሴት አይታ ሂዳ ለጴጥሮስና ለዮሐንስ #ነሥእዎ ጌታዬን ከመቃብር ወስደውታል የወሰዱበትን አላውቅም፡፡ ብላ ነገረቻቸው ጴጥሮስና ዮሐንስ አይተው ተመልስዋል ከዚህ በኋላ እንደ ማቴዎስ ባንድ ወገን የሄዱ ብዙ ሴቶች በአፍአ አንድ መልአክ አይተው ሲመለሱ ጌታን በመንገድ አገኙት፤ ከጫማው ወድቀው ሰገዱለት ከዚህ በኋላ ሄዳችሁ ትንሣኤዬን ለሐዋርያት ንገሩ አላቸው ሔደው ነገሩ።
የትንሣኤ አይነቶች
የትንሣኤ አይነቶች ብዙ ናቸው። ትንሣኤ ዘኅሊና፣ ዘልቡና፣ ዘጊባዔ፣ ጊዜያዊ ትንሣኤና የክርስቶስ ትንሣኤ ይባላሉ። ዛሬ የምንመለከተው የጌታችንን ትንሣኤ ነው።
✍️
የክርስቶስ ትንሳኤው ለኛ ሕይወት የሚሰጥ ትንሣኤ ነው። አሥነሽ የሌለው ትንሣኤ ነው። ዳግም ሞት የሌለበት ትንሣኤ ነው። በሐዲስ ሥጋ የተደረገ ትንሣኤ ነው። ትንሣኤ ዘጉባኤ የማያስፈልገው ትንሣኤ ነው። በኅቱም መቃብር የተፈጸመ ትንሣኤ ነው። የትንሣኤያት ኹሉ በኵር ነው። 1ኛ ቆሮ 15፥20 አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል። ሞት በሰው በኩል ስለ መጣ ትንሣኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኖአልና። ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና። #ነገር ግን #እያንዳንዱ #በራሱ ተራ ይሆናል፤ ክርስቶስ እንደ #በኩራት ነው፥ በኋላም በመምጣቱ ለክርስቶስ የሆኑት ናቸው፤ እንዲል
ሐዋርያው ሁሉ በአዳም እንደሚሞት በክርስቶስ ደግሞ ሕያው እንደሚሆን አስረግጦ ከተናገረ በኋላ "አይቴ ሀሎ ሞት ቀኖትከ ወአይቴ ሀሎ ሲኦል መዊኦትከ" 1ቆሮ 15፥55 በማለት ሞትና ሲኦል መሸነፋቸውን ገልጧል፡፡
✍️ የተነሳው እንደተናገረ #በሥልጣኑ ነው። ማቴ 28 ተመልከት እግዚአብሔር አይዋሽም። ዘኁ 23: ሐሰትን ይናገር ዘንድ ሰው አይደለም እንዲል
ሰው ጠዋት ቢናገር ማታ አይደግመውም፣ በተቀመጠበት አይገኝም። እግዚአብሔር ግን አይለወጥም። "እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም" እንዲል
✍️ የተነሣው ግን በሥልጣኑ ነው። ሌሎቹ ትንሤኤያት አሥነሽ ይሻሉ።
በመልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ (ቆሞስ) የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ
ሚያዝያ 3 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ,ኢትዮጵያ
#ትንሣኤ #ፋሲካ #ኢየሱስ #ክርስቶስ