19/10/2025
እስራኤል በጋዛ አውቶቡስ ላይ በፈጸመችው ጥቃት 11 ሰዎች ተገደሉ
በሰሜን ጋዛ ከእስራኤል ታንክ በተተኮሰ ጥይት በአንድ አውቶቡስ ተሳፍረው የነበሩ 11 የአንድ ቤተሰብ አባላት መገደላቸውን በሐማስ የሚመራው የሲቪል መከላከያ አስታወቀ።
የአቡ ሻባን ቤተሰብ አባላት ናቸው የተባሉት ሟቾች አርብ ምሽት ላይ በጋዛ ከተማ ዜይቱን ሰፈር የሚገኝ ቤታቸውን ለማየት እየሄዱ ነበር ተብሏል።
ይህ ከስምንት ቀናት በፊት የተኩስ አቁም ስምምነት ከተጀመረ ወዲህ በጋዛ በእስራኤል ጦር የተፈጸመ እጅግ አስከፊው ክስተት ነው።
የእስራኤል ጦር ወታደሮቹ በጋዛ የእስራኤል ጦር የሚገኝበትን እና ቢጫ መስመር በሚል የተከለለውን አካባቢ ያለፈ "አጠራጣሪ መኪና" ላይ መተኮሳቸውን ገልጿል።
በመጀመሪያው የተኩስ አቁም ስምምነት መሠረት የእስራኤል ወታደሮች ከግማሽ በላይ በሚሆነው የጋዛ ሰርጥ እንደተቆጣጠሩ ይቆያሉ።
የሲቪል መከላከያ ቃል አቀባይ ማህሙድ ባሳል ለኤኤፍፒ የዜና ወኪል እንደተናገሩት ግለሰቦቹ የተገደሉት በአካባቢው የሚገኘውን ቤታቸውን ለማየት ሲሞክሩ ነው።
ከሟቾቹ መካከል ሴቶች እና ሕጻናት እንደሚገኙበት የሲቪል መከላከያው አስታውቋል።
የእስራኤል መከላከያ ኃይል አርብ ዕለት "አጠራጣሪ መኪና የእስራኤል ወታደሮች በሚንሳቀሱበት በሰሜን ጋዛ ሰርጥ ቢጫውን መስመር አቋርጦ እየቀረበ እንደነበር ተለይቷል" በማለት በተሽከርካሪው ላይ "የማስጠንቀቂያ ጥይቶችን" መተኮሱን ተናግሯል።
ተሽከርካሪው "ወደ ወታደሮቹ ተጨባጭ ስጋት በሚፈጥር መልኩ መጠጋቱን በመቀጠሉ" እና "በተደረሰው መግባባት መሠረት ወታደሮች ጥቃቱን ለማስወገድ ተኩስ ከፍተዋል" ብሏል።
ሐማስ ቤተሰቡ ያለምክንያት ዒላማ እንደተደረገ ተናግሯል።
የእስራኤል መከላከያ ፍልስጤማውያን በጋዛ በቁጥጥሩ ስር ባሉ አካባቢዎች እንዳይገቡ አስጠንቅቋል።
የኢንተርኔት አገልግሎት ውስን በመሆኑ ብዙ ፍልስጤማውያን የእስራኤል ወታደሮች ያሉበት እና ቢጫ መስመር የተባለው የቱ እነደሆነ አያውቁም።
ይህ መስመር በመሬት ላይ ባለመካለሉ አውቶብሱ የቱ ጋር መስመሩን አንዳቋረጠ ግልጽ አይደለም።
ቢቢሲ አደጋው የተፈጸመበትን ስፍራ የሚያመለክት ኮኦርዲኔትስ እንዲሰጠው የእስራኤል ጦርን ጠይቋል።
የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ አርብ ዕለት ሠራዊቱ የመስመሩን ቦታ የሚጠቁሙ የሚታዩ ምልክቶችን እንደሚያስቀምጥ ተናግረዋል ።
በዩናይትድ ስቴትስ አደራዳሪነት በተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት መሠረት እስራኤል 250 ፍልስጤማውያን እስረኞችን እና 1,718 ከጋዛ በመውሰድ ያጎረቻቸውን ሰዎች ለቅቃለች።
ሐማስ በበኩሉ በሕይወት ያሉ 20 ታጋቾችን በሙሉ ወደ ለእስራኤል አስረክቧል።
መስከረም 26/2016 ዓ.ም. ሐማስ በደቡባዊ እስራኤል በፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት 1,200 ሰዎቸን ሲገድል 251 ግቶ ወስዷል።
የእስራኤል ጦር ይህንን ተከትሎ በከፈተው መጠነ ሰፊ ወታደራዊ እርምጃ ቢያንስ 67,900 ሰዎች መገደላቸውን የሐማስ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
BBC
Benjamin Netanyahu - בנימין נתניהו