26/10/2025
ማህበረሰብ ግቡ ሰው ማፍራት ነው ፤ አካላዊ እና ህሊናዊ ጤንነቱ የተሟላ ደስተኛ ግለሰብ ፤ የሚያስብ ግለሰብ ። እንዲህ አይነት ሰው ማፍራት የቻለ ማህበረሰብ በተራው ፖለቲካዊ እና ማህበረ-ባህላዊ ጤንነቱ ይጠበቃል ፤ ህልውናው ፈተና ላይ አይወድቅም ። ግለሰብ የማያፈራ ማህብረሰብ ማህበራዊ መሰረቱ እንደተጠበቀ ሊቀጥል ያዳግተዋል ይፈራርሳል ።
፧
ሰውን ያላፈራ ማህበረሰብ የሚጠበቅበትን ሀላፊነት ሊወጣ አይችልም ። ማህበራዊ ሀላፊነቶች የግለሰብ ተግባራት ናቸው ። "ህዝቡ እንዴት ዝም ይላል?" "ህዝቡ እንዴት አያምጽም?" ...እያልን የምናላዝነው ፣ እንደማህበረሰብ መንፈሳዊ እና አካላዊ ጤንነቱ የተጠበቀ ፣ ሀላፊነቱን የሚያውቅ ፣ ግዴታውን የሚወጣ ሰው ስላላፈራን ነው ። የሚናገር ሰው ያላፈራ ማኅበረሰብ አይናገርም ። ግፍን የሚጸየፍ ሰው ያላፈራ ማኅበረሰብ አያምጽም ። አበበች ጎበናን ያላፈራ ማህበረሰብ ህፃናቱን ሰብሳቢ አያገኝም ። ቢንያም በለጠን ያላፈራ ማህበረሰብ አዛውንቱን ጎዳና ይበትናል ።
፧
ማህበረሰብ መጽሐፍ ነው ፣ እያንዳንዱ ግለሰብ ደግሞ የመጽሐፉ አንድ ገጽ ። የማህበረሰብን መጽሐፍ ስታነብ የምታነብበው እያንዳንዱን ግለሰብ ነው ። የእያንዳንዱ ገጽ ጽሑፍ አንድ አይደለም ፤ ርኩስ እና ቅዱስ _ ፍቅር እና ጥላቻ _ ድብልቅ ነው ። ማህበረሰቡ አድምቆ የፃፈው፣ ጎልቶ እንዲነበብ የፈቀደለት መልኩን እንዲመስልለት የመረጠው የትኛው ገጽ ነው? የሚለው ነው ዋናው ። ርኩሱ ወይስ ቅዱሱ? ጥላቻው ወይስ ፍቅሩ? ስስቱ ወይስ ቸርነቱ? የሂትለርን ገጽ ያደመቀ ማህበረሰብ "ናዚ ጀርመንን" ሆኖ ተነብቧል ። በተቃራኒው እነ አብረሀም ሊንከን ፣ ማርቲን ሉተር ኪንግ ፣ ማህተማ ጋንዲ....የኖሩበትን ማህበረሰብ በበጎ ያስነበቡ አንዳንድ ገጾች ናቸው ።
፧
የማህበረሰብ ልእልና የሚጻፈው በግለሰቦች ላይ ነው ። ደርግ "ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ ነው!"ን እየፎከረ ፣ ህወሀት "ብሔር ብሔረሰብ"ን እየዘመረ ሰው ሳያፈሩ ቀሩ ። የማህበረሰቡ ልእልና የሚፃፍበት ገጽ አጣ ። አብዛኛው የማህበረሰባችን ገጽ የውድቀታችን እና የሽንፈታችን መጻፊያ ሆነ ። ሰው ያላፈራ ማህበረሰብ ሀሳብ ሊኖረው አይችልም ...መዝሙር እና መፈክር እንጂ! ማሰብም ሆነ ማብሰልሰል የሰው እንጂ የማህበረሰብ ሀብት አይደለም ። አሳቢ ሰው ያፈራ ማህበረሰብ ያስባል ፤ ብሔርብሄረሰብ ያፈራ ማህበረሰብ ብዙ መዝሙር እና መፈክር ይኖረዋል ፤ የሚያሳዝነው መዝሙሮቹ እና መፈክሮቹም ሀሳብ የላቸውም ፤ ሰው የሌለው ማህበረሰብ ሀሳብ ከየት ያመጣል ። አንድ ማህበረሰብ ሀላፊነቱን እንዲወጣ አሳቢ ሰው ያስፈልገዋል ።
፧
.. እንደ ማህበረሰብ ለመቀጠል ሰው ያስፈልገናል ።
✍ በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር) የህይወት ፍልስፍና የህይወት ፍልስፍና