07/08/2026
የፊፋ ስራ አስፈጻሚ ቦርድ ለፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ያለውን ድጋፍ አረጋገጠ
የዓለም አቀፉ እግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (ፊፋ) ስራ አስፈጻሚ ቦርድ፣ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ በኃላፊነታቸው እንዲቀጥሉ ሙሉ ድጋፍ መስጠቱን ቢቢሲ ስፖርት ዘግቧል።
ይህ ውሳኔ የተላለፈው ፕሬዝዳንቱ የፊፋ ውድድሮችን ድርሻ ለግል ባለሀብቶች ለመሸጥ አቅርበውት በነበረው እና ከፍተኛ ተቃውሞ ባስነሳው እቅድ ዙሪያ ለተፈጠሩ "ስህተቶች" ይቅርታ መጠየቃቸውን ተከትሎ ነው።
በሞሮኮ ራባት በተካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ ኢንፋንቲኖ እና የፊፋ ዋና ጸሃፊ ማቲያስ ግራፍስትሮም ሂደቱ ግልጽነት በጎደለው መልኩ መከናወኑን በማመን፣ ለ211 አባል ሀገራት የጽሁፍ ይቅርታ አቅርበዋል።
‘ፊፋ ፎርዋርድ ኢንተርፕራይዝ’ (FFE) የተሰኘው ይህ አወዛጋቢ እቅድ የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበርን ጨምሮ ከበርካታ አካላት ጠንካራ ትችት ገጥሞት የነበረ ሲሆን፣ ፊፋም እቅዱን ለመሰረዝ ተገዷል።
የፊፋ ስራ አመራር ቦርድ የተፈጠሩ ስህተቶችን አምኖ ቢቀበልም፣ በፕሬዝዳንት ኢንፋንቲኖ አመራር ላይ ያለውን ጽኑ እምነት በድጋሚ አረጋግጧል።
በተጨማሪም ማኅበሩ የ2030 የዓለም ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታን ለሞሮኮ ለመስጠት ቃል ገብቷል ተብሎ በመገናኛ ብዙሃን የወጣውን ዘገባ "ሀሰተኛ እና አሳሳች" ሲል አስተባብሏል።
ፊፋ በቀጣይ መሰል ድርጊቶች እንዳይደገሙ እና የማኅበሩን ዝና ለመጠበቅ አስፈላጊውን እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል።
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
•ፌስቡክ፡-https://web.facebook.com/HabeshaTech
• ፌስቡክ፡-https://www.facebook.com/AbayTubeEt
• ቴሌግራም፦https://t.me/HabeshaTechHubs
• ቴሌግራም፦https://t.me/HabeshaUpdate