
04/08/2025
ቸሩ መድኃኒአለም የቀራንዮ ንጉስ የድንግል ማርያም ልጅ ከኃጢያት በቀር የልባችን መሻት ይፈጽምልን!!!
==============/////==============
በመለኮቱ ሕያው ሲሆን በስጋው ግን ሞትን ቀመሰ፡፡
የአዳምን ሞት በሞቱ ሊሽር መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን በገዛ ፈቃዱ አሳልፎ ሰጠ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ለኤፌሶን ክርስቲያኖች ሲጽፍ “ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን… አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን” ይላል፡፡ ካሕናት አባቶቻችን የስቅለተ ዕለተ የዘጠኝ ሰዓት ስግደት ሲሰገድ “ኦ ዘጥዕመ ሞተ በስጋ” “በስጋው ሞትን የቀመሰ ኢየሱስ ክርስቶስ” እያሉ ልብን በሚያሳዝን ዜማ ያዜማሉ፡፡ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቄርሎስም “ለቤተ ክርስቲያን ስትል በአደባባይ በጥፊ የተመታህ አቤቱ ይህን ማድረግህ እርስዋን በከበረ ደምህ ትቀድሳት ዘንድ ነው፡፡ ለእርስዋ ሲል ታሥሮ መጎተት የቻለ የበደለውም በደል ሳይኖር፣ ርኩስ ምራቅን ሲተፋበት የታገሠ መድኃኔ ዓለም በእንጨት መስቀል ላይ ተሰቀለ” በማለት ገለጸው፡፡
አምላካችን እግዚአብሔር ሰው ሆኖ እንደሚያድነን በመጀመሪያ ለአዳም ቃል ገባለት፡፡ ከዚያም በነቢያት ትንቢት አስነገረ፡፡ በስጋ በተገለጠ ጊዜም የሰቀሉትና የገደሉት አይሁድ ሳይቀሩ እንዲናገሩ አፋቸውን አስከፈታቸው፡፡ አልአዛርን ለአራት ቀናት በመቃብር ከቆየ በኋላ ከሙታን ሲያስነሳው ከአይሁድ ወገን ብዙዎች አመኑ፡፡ አንዳንዶች ግን ወደ ፈሪሳውያን ሄደው ኢየሱስ ያደረገውን ነገሯቸው፡፡ በዮሐንስ 11 እንደተጻፈው ከተአምራቱና ከትምህርቱ የተነሳ ሕዝቡ ሁሉ ትቷቸው እንዳይሔድ የፈሩት አይሁድ ሲማከሩ በዚያች ዓመት ሊቀ ካህናት የነበረ ቀያፋ የሚሉት ከእነርሱ አንዱ፡- “እናንተ ምንም አታውቁም፤ ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም” አላቸው።
ይህንም የተናገረ ከራሱ አይደለም፤ ኢየሱስ ስለ ሕዝቡ ሊሞት እንዳለው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ትንቢት አናገረው፡፡ “ስለ ሕዝቡም ሁሉ አይደለም፣ ነገር ግን የተበተኑትን የእግዚአብሔርን ልጆች በአንድነት እንዲሰበስባቸው ነው እንጂ።” ተብሎ ተጽፏልና፡፡ የቀድሞው የግብጽ ኦርቶዶክሳውያን ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሺኖዳ “እኛ ወደ እርሱ መውጣት ሲያቅተን መድኃኔ ዓለም ወደኛ ወረደ” በማለት ይገልጹታል፡፡ የማዳኑ ስራ ለሰው ልጅ ቤዛነት የተደረገ፣ ፍጹም ፍቅሩ የታየበት ከሰው ሕሊና በላይ የሆነ አባትነቱን ያሳየበት ነው፡፡ አምላክነትን ሲሻ የወደቀው የሰው ልጅ፣ የወደደውን አምላክነት ያገኝ ዘንድ የሰውን ባሕርይ ተዋህዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ በድንቅ ተዋህዶ አምላክ ሰው፣ ሰውም አምላክ ሆኗልና ከኛ በነሳው ስጋም ወደ ሰማይ አረገ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ሔዋንን ዲያብሎስ አሳታት የሞት ምክንያት የሚሆን ቃየልን ወለደች፡፡ ድንግል ማርያም ግን መልአክ በአበሠራት ጊዜ ሁሉን ወደ ዘለዓለም ሕይወት የሚመራ አካላዊ ቃልን በሥጋ ወለደች፡፡” ይለናል፡፡ በማዳኑ ስራ ውስጥ የቅድስት ድንግል ማርያም ድርሻ ታላቅ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በገላ 4÷4 “የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ልጁን ላከ፡፡” ሲል ጽፏል፡፡ ስለፍጹም የሰው ልጆች ፍቅር መድኃኔ ዓለም ተላልፎ ተሰጠ፡፡ ለዚህም ነው በፊልጵ 2÷8 “በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፣ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ” ተብሎ የተጻፈው፡፡