
18/08/2025
የጦር ግንባር ማስታወሻዬ
የካቲት 22 ቀን አመሻሽ ላይ እኔና ሌሎች የልዩ ጥበቃ ኮማንዶ ጓደኞቼ አዛዣችንን መከታው ማሞን አጅበን ወደ አጣዬ አቅጣጫ ገሰገስን። ምሽት ላይ ከአጣዬ 10 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደምትገኘው ይምላዋ ቀበሌ ደረስን። አካባቢው የውጊያ ቀጣና በመሆኑ የመከላከያ ሠራዊት በ3 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኝ ነበር።
ወደዚህ የመጣነው የ7ለ70 ብርጌድ ዋና አዛዥ አርበኛ ተስፋዬ በጦርነት ላይ እያለ በውስጥ ባንዳዎች በመገደሉ ነበር። በተለይም የ"ኢሳያስ ደመቀ" ቡድን አባላት ከጀርባው ተኩሰውበት ሕይወቱ እንዳለፈ ተነገረን። እንደደረስን ወዲያውኑ በአካባቢው ከሚገኙ ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች ጋር ስብሰባ ተቀመጥን። በስብሰባው ላይ ፋኖዎች ከጥር ወር ሁለተኛ ሳምንት ጀምሮ ለአንድ ወር ያህል ያለማቋረጥ ሲዋጉባቸው የነበሩትንና ሙሉ በሙሉ የሚያስተዳድሯቸውን አራት ቀበሌዎች (ማለትም በርግቢ፣ ይምላዋ፣ አላላ እና ፈረዶ ውሃ) ለቀው እንዲወጡና በምትኩ ስልታዊ ቦታዎችን እንዲይዙ አቅጣጫ ተሰጠ። ይህ ከባድ ትዕዛዝም በዚያው ዕለት ተፈጸመ።
ትዕዛዙን ተከትሎ ፋኖዎች አካባቢውን ከለቀቁ ከሦስት እና ከአራት ቀናት በኋላ የመከላከያ ሠራዊት ያለ ምንም ውጊያ ወደ ስፍራው ገባ። በዚህም በርካታ ወንድሞቻችንን ገብረንበት የነበረውን እና መከላከያ በውጊያ ሊቆጣጠረው ያልቻለውን ከአጣዬ እስከ መሀል ሜዳ የሚዘልቀውን የ60 ኪሎ ሜትር አውራ ጎዳና በነፃ አሳልፈን ሰጠነው።
በመጨረሻም የአድዋ ድልን ለማክበር ሌሊቱን ሙሉ ከባድ ጉዞ አድርገን፣ በማግስቱ ጠዋት መንዝ ወገሬ ከተማ ደረስን።
ለአማራ ሕዝብ ክብር ብዬ ሕይወቴን ብሰጥ እንኳ፣ ይህ የእኔ የታሪክ ማስታወሻ ነው።
ዘላለማዊ ክብር ለተሰው ወንድሞቼ፣ ድል ለፋኖ!
አማሮች