
16/09/2025
"መንግሥት በሕዝቡ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በራሱ ውስጥ ባሉ ሰዎች ላይ ጭምር ስጋትን ለመፍጠር በሚል የሚወስደው እርምጃ ሊሆን ይችላል" አደም ካሴ።
"በአሁኑ ወቅት ሕዝቡ ታጣቂዎችን ይፈራል፤ በተጨማሪም ይጠብቀኛል የሚለውን መንግሥትንም ይፈራል" ያሬድ ኃይለ ማሪያም።
"ይህ ድርጊት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ሥርዓት አልበኝነት መኖሩን የሚያሳይ ምልክት ነው" ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የሕግ ባለሙያ።
እነዚህ አስተያየቶች እየተደጋገመ የመጣውን ዜጎችን ከሕግ ውጪ አፍኖ በኃይል የመሰወር ድርጊትን በተመለከተ የተሰነዘሩ ናቸው። ትኩረታቸውም ክስተቱ በሕዝቡ ውስጥ ስጋት የሚፈጥር እየሆነ መሄዱ ላይ ነው።
በኢትዮጵያ የተለያዩ ክፍሎች ውስጥ በታጣቂዎች የሚፈፀሙ እገታዎች የዕለት ከዕለት ክስተት ወደ መሆን እየደረሱ ነው። ዋና ከተማዋ አዲስ አበባ አንጻራዊ ደኅንነት ያለባት ብትሆንም ከስጋት ግን ነጻ አይደለችም።
አዲስ አበባ ውስጥ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ የመብት ተከራካሪዎች፣ ጋዜጠኞች እና ተራ ዜጎች በማይታወቁ ኃይሎች ተይዘው ለቀናት ወይም ለሳምንታት ተሰውረው የሚቆዩበት ሁኔታ አነጋጋሪ ሆኗል።
ሰዎች የፀጥታ ኃይል ነን በሚሉ ታጣቂዎች ነገር ግን የሕግ ሥርዓትን ባልተከተለ ሁኔታ ከቤታቸው፣ ከሥራ ቦታቸው እና ከመንገድ ላይ ታፍነው መወሰዳቸው ፍርሃት እና ግራ መጋባትን ፈጥሯል።
የፖሊስ እና የመከላከያ የደንብ ልብስ ወይም ሲቪል በለበሱ ሰዎች የሚፈጸመው አስገድዶ የመሰወር ክስተት የተደጋገመ ከመሆኑ በተጨማሪ የሚመለከታቸው የፀጥታ አካላትም "የማያውቁት" መሆኑ የበለጠ አሳሳቢ ሆኗል።
ቢሆንም ግን የሚታፈኑት ሰዎች በሥራቸው እና በእንቅስቃሴኣቸው የሚታወቁ መሆናቸው ድርጊቱ በመንግሥት አካላት እንደተፈጸመ ይታመናል። ታጋቾቹም ከቀናት ወይም ከሳምንታት በኋላ ሲለቀቁ መሰወራቸው ከመንግሥት አካላት ጋር የተያያዘ መሆኑን ይናገራሉ።
ይህ እየተደጋገመ ያለ እና በፖለቲካው፣ በሲቪል ማኅበረሰብ እና በጋዜጠኝነት ሙያ ላይ ያሉ ሰዎችን ላይ ያነጣጠረው አፈና የሚፈጸመው ምን ለማሳካት ነው? ወደ የትስ ሊያመራ ይችላል?
ውስጥ ሥርዓት አልበኝነት እንዲሰፍን የሚያደርግ ክስተት ነው" ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።
አደም ካሴ በበኩላቸው እንዲህ ዓይነቱ አፈና እና መሰወር በተበራከተ ቁጥር "ሕገ ወጥነት እና የዘፈቀደ አካሄድን በማስፋፋት አደገኛ ሁኔታን የሚፈጥር ድርጊት ነው" ብለዋል።
ቢቢሲ ያነጋገራቸው የሕግ እና የሰብአዊ መብት ባለሙያዎች ይህ እየተደጋገመ የመጣው ከሕግ ውጪ ሰዎችን የመሰወር ድርጊት ሕግ እና ሥርዓትን በማፍረስ፣ ሥርዓት አልበኝነትን ሊያስከትል እንደሚችል በአጽንኦት አስጠንቅቀዋል።
አፈናውን የሚፈጽመው ማን ነው?
"በፀጥታ ኃይሎች" ታፍነው ወዳልታወቁ ስፍራዎች የተወሰዱ ሰዎች እና ይህንን የተመለከቱ የዓይን እማኞች እንደሚሉት ከአለባበስ እና ከንግግራቸው የመንግሥት ኃይሎች መሆናቸውን ይናገራሉ።
ነገር ግን የሚፈልጉትን ሰው ለመያዝ የሚከተሉት መንገድ በአገሪቱ ሕግ ከሚፈቀደው ውጪ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ የያዟቸውን ሰዎች የሚወስዱበት ቦታም በመደበኝነት የሚታወቁ እስር ቤቶች ወይም የማቆያ ስፍራዎች አይደሉም።
ይህ ደግሞ በሚያዙት ሰዎች እና ቤተሰቦቻቸው ላይ ከባድ ሥነ ልቦናዊ ጫናን የሚያስከትል ነው።
የታፈኑት ሰዎች የት እና በማን እጅ መሆናቸውን የማያውቁ ቤተሰቦች ለመደበኛዎቹ የፀጥታ ተቋማት ለሚያቀርቡት ጥያቄ የሚሰጣቸው ምላሽ "የምናውቀው ነገር የለም" የሚል መሆኑ ደግሞ ተስፋ መቁረጥ ያነግሳል።
ያሬድ ኃይለማሪያም ከአንድ የፀጥታ ኃላፊ ጋር ይህንን ጉዳይ በተመለከተ በነበራቸው ንግግር መደበኛው የፖሊስ እና የፀጥታ ኃይል ታገቱ ስለተባሉት ሰዎች ከመስማት ባሻገር የሚያውቁት ነገር እንደሌለ እንደነገሯቸው ገልጸዋል።
በዚህም የተነሳ አፈናውን እና ስወራውን የሚፈጽም የተለየ ኃይል እንዳለ እንደሚያምኑ የሚጠቅሱት ያሬድ፣ እነሱም "ታፋኞቹን ወዳልታወቀ ቦታ ወስደው ለቀናት ካቆዩ በኋላ ጥያቄ እና መነጋገሪያ ሲሆኑ መንገድ ላይ ወይም ፖሊስ ጣቢያ አምጥተው ይጥሏቸዋል" ይላሉ።
ማንነታቸው የማይታወቁ፣ ፊታቸውን የሚሸፈኑ፣ የፖሊስ ወይም የወታደር የደንብ ልብስ የሚለብሱ፣ በመንግሥት ወይም በግል ተሽከርካሪ የሚንቀሳቀሱ ሰዎች የሚፈጽሙት አፈና ግራ መጋባትን በመስከተል ስጋትን ይፈጥራሉ።
ያሬድ እንደሚሉት የመንግሥት አካል መሆናቸው ቢታወቅ እንኳን ሕጋዊውን ሥርዓት ስለማይከተሉ በሕዝቡ ውስጥ በተቋማት ላይ ያለውን ዕምነት የሚያሳጣ "አደገኛ የሆነ የመንግሥታዊ ሥርዓት ውድቀት ማሳያ ነው።"
እነዚህ ሁሉ ድርጊቶች አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ውስጥ ሲከሰቱ የመንግሥት አካላት ዝምታን መምረጣቸው ደግሞ ግራ አጋቢ ሆኗል።
ይህ ደግሞ የመንግሥት እጅ እንዳለበት እና ይሁንታውን የሰጠው ድርጊት ነው የሚያስብል ከመሆኑ በተጨማሪ በሕጋዊ ተቋማት ሚና እና ተቀባይነት ላይ ተስፋ መቁረጥ እያስከተለ መሆኑን ያሬድ ኃይለማሪያም ይናጋራሉ።
ይህንን እገታ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ውስጥ ያሉ ታጣቂዎች በተደጋጋሚ እየፈጸሙ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስን አስፈሪ አድርገውታል። ተመሳሳይ ስጋት በከተሞች ውስጥ መኖሩ ደግሞ ዜጎች ደኅንነት እንዳይሰማቸው ያደርጋል።
"በአሁኑ ወቅት ሕዝቡ ታጣቂዎችን ይፈራል፤ በተጨማሪም ይጠብቀኛል የሚለውን መንግሥትንም ይፈራል" የሚሉት አቶ ያሬድ፣ "ሕገወጥ ቡድኖች ሲያፍኑ መፍትሔው መንግሥት ነው ይባል ነበር። አፋኙ መንግሥት ሲሆን ወደ የት ይኬዳል?" ሲሉ ይጠይቃሉ።
ቢቢሲ እንደዘገበው