04/11/2025
ኩባ ከአዲስ አበባ - ሀቫና ቀጥታ በረራ እንዲኖር ፍላጎት እንዳላት ገለጸች
+++++++++++++++++
| ኩባ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጎልበት ከአዲስ አበባ- ሀቫና ቀጥታ በረራ እንዲኖር ፍላጎት እንዳላት በኢትዮጵያ የኩባ አምባሳደር ሜይሊን ሱዋሬዝ አልቫሬዝ ገለጹ፡፡
አምባሳደሯ ከኢፕድ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደተናገሩት ኩባ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማጎልበት ከአዲስ አበባ- ሀቫና ቀጥታ በረራ እንዲኖር እየሰራች ነው፡፡
የቀጥታ በረራው መጀመር የሀገራቱን የአሰርት ዓመታት የዲፕሎማሲ ትብብር ወደ ጠንካራ የኢኮኖሚና የባህል ተሳትፎ የሚያሳድግ ይሆናል፡፡
ጅማሮው የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ዋና ከተማ የሆነችውን አዲስ አበባን ከካሪቢያን የባህል ማዕከል ጋር ለማገናኘት ያለመ መሆኑን የገለጹት አምባሳደር ሜይሊን፤ አገራቸው ለፕሮጀክቱ ያላትን ቁርጠኝነት በመጥቀስ በዚህ ረገድ ማንኛውንም ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡
ኢትዮጵያ በርካታ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ እንቅስቃሴዎችን እንደምታስተናግድ የተናገሩት አምባሳደሯ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በመሆን የሚጀመረው የቀጥታ በረራ ኩባን ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከር እንደሚያስችላትም ገልጸዋል።
በተጨማሪም የቀጥታ በረራው መጀመር ከሁለትዮሽ ግንኙነት ያለፈ ጠቀሜታ እንደሚኖረው በመጥቀስ፤ ለሁለቱ አገራት ብቻ ሳይሆን አጠቃለይ ለቀጣናዊ ትብብርም ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል
በግርማቸው ጋሻው
+++++++++++++++
#ኩባ #አየርመንገድ