22/05/2026
ወደ ሀሰን አንጃሞ መካነ መቃብር
---
ተጓዡ ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም የታላቁን ጀግና የሀሳን አንጃሞን መካነ መቃብር ጎበኘሁት ይለናል፡፡ በኢማሙ የታሪክ አሻራዎች ያደረገውን ቆይታ እንዲህ ተርኮልናል፡፡ / ከሄኖክ ስዩም በድሬቲዩብ
--
ትንሽ መንደር ናት፡፡ ውብና ለም፤ ግዙፍ ሁለት ጎጆዎችን ሾልኬ ገባሁ፡፡ ምሁር አክሊል የሚባለው ወረዳ ውስጥ ነኝ፤ ቀበሌዋ ሴባ ትባላለች፡፡ መንገዱን የሚመራው የሀሰን አንጃሞ የልጅ ልጅ ልጅ ነው፡፡ አራተኛው የኢማሙ ትውልድ፤
ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር እኔ ወጣት ብሆን ሀሳን አንጃሞን ፊልም አደርገው ነበር ያለለትን ጀግና ብርቱ ታዋጊ በመሆን ይታወቃል፡፡ ጀግንነቱ ዛሬም ድረስ በስነ ቃሎች ይሞካሻል፡፡ ታሪክ ከማይረሳቸው ብርቱ ጦረኞች አንዱ ነው፡፡ ኢማም ሀሰን አንጃሞ፤
ከሃድያ እስከ ስልጤ ከእነሞር እስከ ቀቤና ከወለኔ እስከ ሊቢዶ ያሰባሰበው ጦር ከሸዋ ሠራዊት ጋር በጀግንነት እንዲዋጋ የመሪነት ብቃቱን የሚወስድ ስመ ጥር የጦር ጀግና ነው፡፡ ለዲኑ ብሎ ቢሰደድም ብዙዎችን አስከትሏል ይላሉ የወለኔው ሼህ ስለ ኢማሙ በጻፉት ጽሁፍ፤
ጥሮነ ሼህ ኡመር ሼህ በሽር የጻፉት ዜና መዋዕል ነው፡፡ አብዱልፈታህ አብደላህ ለአማርኛ አንባቢያን እንዲደርስ አድርጎታል፡፡ ሰውዬው ኢማም ሀሰን አንጃሞን በተመለከተ ከ150 ዓመት በፊት በጻፉት ጽሑፍ ቁመቱ ረዥም እንደሆነ ይነግሩናል፡፡
እንደ ሼህ ኡመር ገለጻ ኢማም ሀሰን አንጃሞ ብዙ መብላትና መጠጣትን የማይወድ፣ ጥቁር ሆኖ ቆንጆ፣ በሙያው ማንም የማይደርስበት፣ ፈረሰኛና ጀግናና ሲበዛ ቸር ነበር ይሉናል፡፡
እየሄድሁ ያለሁት ወደዚሁ ጀግና መካነ መቃብር ነው፡፡ ጡሃ መሀመድ ኺያርሺፋ ሀሰን የመካነ መቃብሩን ቅጥር ከፈተው፡፡ ወደ ውስጥ ገባን፡፡ ዛፎች የከበቡት አረንጓዴ ስፍራ ነው፡፡ ኢማም ኺያር፣ የሀሰን አንጃሞ አያትና አባትን ጨምሮ የኢማሙ መቃብር ይገኝበታል፡፡
ኢምሬትስ ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ ሀብቴ አባ መላን በጻፉበት መጽሐፍ ኢማም ሀሰን ኢንጃሞ ለእነ ራስ ጎበና ባስቸገረ ሁኔታ ፈተና መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የጀብዱ ሜዳ ጦርነት የሚባለውም በኢማም ሀሰን አንጃሞ በሚመራው የቀቤናና ሃድያ ሠራዊትና በራስ ጎበና መሪነት በሚመራው የዐፄ ምኒልክ ሠራዊት መካከል የተደረገ ነበር፡፡ በዚህ ጦርነት ድል ለራስ ጎበና ሠራዊት ቢሆንም ታላቁ የጦር መሪ የራስ ጎበና ልጅ መርእድ ጎበና ተሰውቷል፡፡ ኢማም ሀሰን አንጃሞም ከሠራዊቱ መፈታት በኋላ ወደ ጅማ ሸሽቷል፡፡
ራስ ጎበናም ከድሉ በኋላ የነበራቸው እድሜ የቀናት ብቻ ነበር፡፡ ተደጋጋሚ ጦርነቶችን ድል አድርጎ በመጨረሻም በንጉሠ ነገሥቱ ስመ ጥር የጦር መሪ የተረታው ኢማም ከዚያ በኋላ ሀሰን አንጃሞ የጀግንነት ምልክት ሆነ ስሙ ገኖ ተወደሰ፡፡