23/02/2025
የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ብፁዕ አቡነ መልከ ጼድቅ ለምእመናን በሙሉ ለ2017 ዓ.ም አብይ ፆም የእንኳን አደረሳችሁ መልእክታቸውን አስተላለፉ።
የካቲት 16/2017 ዓ.ም(ወልቂጤ )
በፆሙ ወራት ምእመናን ከእህልና ውሃ ብቻ ሳይሆን ከክፋት ሁሉ በመጠበቅ ራሳቸውን ለፈጣሪ ማቅረብ እንዳለባቸው አባታዊ መልእክታቸውን ገልፀዋል።
ብፁህ አቡነ መልከ ጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ የ2017 የአብይ ፆምን አስመልክስተው ለምእመናን ባስተላለፉት መልእክት የአብይ ፆም ራሱ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የፆመውና ዲያብሎስን ድል ያደረገበት ወቅት በመሆኑ ምእመናን ይህንኑ በማሰብ መንፈሳዊ በረከትን ለማግኘት ወራቱን በፆምና በፀሎት ማሳለፍ እንዳለባቸው ገልፀዋል።
በፆሙ ወቅት ምእመናን ከእህልና ውሃ በመጠበቅ ብቻ ሳይሆን ይቅር በመባባል፣በመረዳዳትና በመተሳሰብና ሌሎች መንፈሳዊ ተግባራትን በማከናወን ከአምላካቸው ጋር ያላቸውን ቅርበት ማሳደግ እንዳለባቸው ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ ተናግረዋል።
ከክፉ ተግባራት መራቅና መልካም ስራዎችን ማከናወን የሠዎች የሁልጊዜ ግዴታዎች ቢሆኑም በተለይ በፆም ወራት መሠል መልካም እሴቶችን የበለጠ መጎልበት ትልቁ የፆም አላማ መሆኑን ተናግረዋል ብፅዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ ።
ይህንን በመገንዘብ ህዝብ ክርስቲያኑ በልዩ ትኩረት ፆሙን ሊያሳልፈው ይገባል ብለዋል።
ፆም ከመንፈሳዊ አስተዋፅኦ ባሻገር የህብረተሰቡን ማህበራዊ ግንኙነት ለማሻሻል ትልቅ ጥቅም ያለው በመሆኑ በተለይ ሀገራችን በአሁኑ ወቅት ካላችበት አስቻገሪ ሁኔታ ተላቃ ሰላምና ፍቅር እንዲነግስ ከልብ መፆም ይገባል ሲሉ ገልፀዋል።
የታረዙትን በማልበስ ፣የተጠሙትን በማጠጣት፣የተራቡትን በማብላትና በሌሎችም አስቻጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በመደገፍ ማሳለፍ የፆም ወራት ልዩ መገለጫዎች ሊሆኑ ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ሀገራችን ሰላም ሆነ ምእመናን በሰላም ወጥተው እንዲገቡ ፆምና ከልብ የመነጨ ልመና ያስፈልጋል ያሉት ብፁህ አቡነ መልከ ጼድቅ በዚህም የነነዌ ሰዎች በመፆማቸውና በይቅርታ በመመለሳቸው ከጥፋት መዳናቸውን አውስተዋል።
ይህንኑ አብነት በማድረግ ፈጣሪያችን ይቅር እንዲለን ከልብ በመፆምና በመፀለይ ለፈጣሪ መቅረብ ይገባል ብለዋል።
ዘጋቢ ፦ ዘርማ ሚዲያ