
24/07/2025
Commercial Bank Of Ethiopia የሠጠው መግለጫ▼
ክቡራን ደንበኞቻችን እና ባለድርሻ አካላት በሙሉ
=================
ሐምሌ 15 ቀን 2017 ዓ.ም. አዲስ ስታንዳርድ፣ አዲስ ሚዲያ ኔትወርክ የተባሉና ሌሎችም የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆች በባንካችን ላይ ተቃጥቶ ከነበረው ብር 7.735 ቢሊየን ገንዘብ ከባንኩ የውስጥ ሂሳቦች ያለሕጋዊ ምክንያትና ሥልጣን በባንካችን በሚገኙ 10 የሌሎች ግለሰቦች ሂሳብ በማዛወር ገንዘቡን ለማይገባው ሰው ጥቅም ወይም ለራሳቸው ለተጠርጣሪዎች ለማዋል የማመቻቸት ተግባርን ባንኩ ባለው ጠንካራ የውስጥ ቁጥጥር ስርዓት ደርሶበት ምንም አይነት ገንዘብ ወጪ ሳይደረግ ገንዘቦቹን ከተላለፉባቸው ሂሳቦች ወደ ትክክለኛዎቹ የውስጥ ሂሳቦቹ ተመላሽ አድርጓል።
ባንካችንም ለሚመለከተው የሕግ አካል ወዲያውኑ የወንጀል ተግባሩን ጥቆማ በማቅረቡ ምርመራዎች ሲካሄዱና ማስረጃዎች ሲሰባሰቡ ቆይቶ በ14 ተጠርጣሪዎች ላይ ለራስ ወይም ለሌላ ሰው የማይገባ ጥቅም ለማግኘት አስቦ ስልጣንን አላግባብ የመገልግል ከባድ የሙስና ወንጀል በዋና ወንጀል አድራጊነትና በልዩ ወንጀል ተሳታፊነት በፌደራል ዓቃቢ ሕግ የሙስና ወንጀል ዳይሬክቶሬት በኩል በ14 ተጠርጣሪዎች ላይ የወንጀል ክስ ተመስርቷል።
በሌላ በኩል ግንቦት 19 ቀን 2017 ዓ.ም. “በኢትዮጵያ ንግድ ባንከ የውስጥ አካውንት ውስጥ ተቀምጦ የነበረ ከ7 ቢሊየን ብር በላይ መዘረፉ ተገለፀ” በማለት ባንካችን ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ እንደተዘረፈ፣ ዘራፊዎቹ እንዳልተያዙ እና ባንካችንም ጉዳዩን አድበስብሶ እንዳለፈው የሚገልጽ የሐሰት መረጃ መሰራጨቱን ተከትሎ ባንካችን ትክክለኛውን እውነታ በመግለፅ ግንቦት 20 ቀን 2017 ዓ.ም. በይፋዊ የማህበራዊ ሚድያ ገፆቹ ባስተላለፈው መልዕክት:-
➢ ባንካችን ሙከራው በተደረገ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ በጠንካራው የውስጥ ቁጥጥር ስርዓታችን አጠራጣሪ ግብይት መፈፀሙን ስለደረሰበት ምንም ዓይነት ገንዘብ ወጪ ሳይደረግ (ሳይመዘበር) ሙከራው ወዲያውኑ እንዲከሽፍ መደረጉን
➢ ሙከራው በጥቂት ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት ባሰቡ ተጠርጣሪዎች የተፈፀመ እንጂ የባንካችንን ሲስተም ተላልፎ የተፈፀመ ጥቃት አለመሆኑን፣
➢ ባንካችን ሙከራ የተደረገበትን ገንዘብ ባለው ጠንካራ የቁጥጥር ስርዓት አማካኝነት ከጥቃት ከተከላከለ በኋላ ጉዳዩን ለሚመለከተው የሕግ አካል በማሳወቅ ተጠርጣሪዎቹ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉና የምርመራ ስራውም ተጠናክሮ እየተከናወነ የሚገኝ መሆኑን መግለፁ ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በፖሊስ በኩል ተገቢው ምርመራ ተደርጎ በ14 ተጠርጣሪዎች ላይ በፌዴራል ዓቃቤ ህግ በኩል ክስ መመስረቱን ተከትሎም ገንዘቡ “በተጠርጣሪዎቹ ወጪ ተደርጎ እንደተወሰደ” በማስመሰል፤ “ባንካችን አጭበርብረውኛል ባላቸው ግለሰቦች ላይ ክስ እንደመሰረተ” እንዲሁም “ተመዘበረ የተባለው ገንዘብ ባንካችን ከፖሊስ ጋር በመተባበር ማሳገዱን” በመጥቀስ ሀሰተኛ መረጃዎች በጥቂት የማህበራዊ ሚድያዎች መሰራጨቱንና የዚህን መረጃ ትክክለኛነት ሳያጣሩ ሌሎች የተወሰኑ ሚዲያዎችም ይህንኑ ሀሰተኛ መረጃ ደግመው እያሰራጩ የሚገኙ እንዳሉም ተገንዝበናል።
ቀደም ብለንም እንዳሳወቅነው ባንካችን እንደማንኛውም የፋይናንስ ተቋም በተለይም እንደ ግዙፍ የፋይናንስ ተቋምነቱ ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት አስበው ለሚንቀሳቀሱ አካላት ኢላማ መሆኑ እሙን ቢሆንም እንዲህ አይነቱን ሕገ ወጥ ተግባር ለመከላከል የሚያስችል ጠንካራ የውስጥ ቁጥጥር ስርዓትና የዘመነ ሲስተም ያለው ለመሆኑ ይህ የሙከራ ድርጊት መክሸፉና ተጠርጣሪዎች ላይም ምርመራ ተጣርቶ የወንጀል ክስ መመስረቱ አንዱ ማሳያ ነው፡፡
በመሆኑም የባንካችንን መልካም ስምና ዝና ለማጠልሸትና ሀሰተኛ መረጃ ለማሰራጨት ሆን ብለው የተዛባና ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ በሚያሰራጩ ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት ላይ በአፋጣኝ ተገቢውን የእርምት ማስተባበያ ካልሰጡ ባንካችን ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን ለመውሰድ የሚገደድ መሆኑን እያሳወቅን ክቡራን ደንበኞቻችንም ባንካችንን የሚመለከቱ መረጃዎችን ከታአማኒ የመረጃ ምንጮችና ከባንካችን ይፋዊ የመረጃ ምንጮች ላይ ማግኘት የሚችሉ መሆኑን እያሳወቅን የመረጃዎችን ትክክለኛነታቸውን ሳያጣሩ ሀሰተኛ መረጃዎችን እንዳይቀበሉ በአክብሮት እንጠይቃለን።