28/02/2026
የፈንገስ በሽታ ስርጭትና ምርመራ ላይ ያተኮረ ዓለም አቀፍ የዕውቀት ሽግግር መድረክ በሰመራ ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ
አፋር-ሰመራ፤ የካቲት 21/2018 (አውሳ ኢንሳይደር)
የሰመራ ዩኒቨርሲቲ ከፈረንሳዩ ሬን ዩኒቨርሲቲ (Rennes University) ጋር በመተባበር በፈንገስ በሽታዎች ስርጭት፣ በምርመራ ተግዳሮቶችና በመፍትሔዎቻቸው ዙሪያ ያተኮረ ከፍተኛ የዕውቀት ሽግግር መድረክ አዘጋጀ።
በመድረኩ ላይ በሕክምና፣ በፓራሳይቶሎጂ እና በማይኮሎጂ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስመ-ጥር የሆኑት ፕሮፌሰር ዣን-ፒየር ጋንግኔክስ (Jean-Pierre Gangneux) ለተሳታፊዎች ሰፊ ገለጻ አድርገዋል።
ፕሮፌሰሩ ባቀረቡት አጠቃላይ ገለጻ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ እየጨመረ የመጣውን የፈንገስ ኢንፌክሽኖች ጫና በጥልቀት መርምረዋል።
በገለጻቸውም አጽንኦት ከሰጡባቸው ነጥቦች መካከል፦
• የበሽታው ስርጭት (Epidemiology): በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ስርጭትና ክሊኒካዊ ተፅዕኖ።
• የምርመራ ተግዳሮቶች: በሽታውን ለመለየት የሚገጥሙ እንቅፋቶች።
• የላብራቶሪ አቅም ግንባታ: በተለይም ውስን ግብዓት ባለባቸው አካባቢዎች የላብራቶሪ አቅምን የማጠናከር እና ቅድመ መከላከል ሥርዓቶችን የመዘርጋት አስፈላጊነት እና የመሳሰሉት ይገኙበታል።
በመድረኩ ላይ የሕክምና ትምህርት ቤት ተማሪዎች፣ የጤና እና ሕክምና ሳይንስ ኮሌጅ ተማሪዎች፣ መምህራን እና የላብራቶሪ ረዳቶች የተሳተፉ ሲሆን፣ ይህም በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሙያዎች አዳዲስ የምርመራ ቴክኖሎጂዎችን እና የሕክምና ዘዴዎችን ለመገንዘብ ትልቅ አጋጣሚ ፈጥሯል።
~~~~~~~~~~~~~~~~~~
#አውሳኢንሳይደር #አፋርክልል #አፋር #ሰመራዩኒቨርስቲ