23/07/2026
ኢትዮ ቴሌኮም በበጀት ዓመቱ 215.8 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱንና የደንበኞቹ ቁጥር 90 ሚሊዮን ማለፉን ገለጸ
ኢትዮ ቴሌኮም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት 215.8 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱን የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወይዘሪት ፍሬሕይወት ታምሩ በዛሬው ዕለት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታወቁ።
የተገኘው ገቢ የዕቅዱን 99.7 በመቶ ማሳካት የቻለ ሲሆን፣ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ33.2 በመቶ ከፍተኛ እድገት ማሳየቱ ተገልጿል።
እንደ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ ገለጻ፣ ተቋሙ የገቢ ምንጮቹን በማስፋትና የቴሌኮም አውታረ መረቡን በማሳደግ በርካታ ውጤታማ ሥራዎችን አከናውኗል።
በዚህም በበጀት ዓመቱ የሞባይል ጣቢያዎችን ቁጥር ከ10 ሺህ በላይ ማድረስ ተችሏል። በተጨማሪም የ4ጂ አገልግሎት ተደራሽነትን በማስፋት 264 ከተሞችን ማቃለል የተቻለ ሲሆን፣ አዳዲስ 7 ከተሞችን በመጨመር በአጠቃላይ በ33 ከተሞች የ5ጂ አገልግሎት መስጠት ተጀምሯል።
በሌላ በኩል የተቋሙ ጠቅላላ የደንበኞች ቁጥር 90.1 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን፣ ይህም የዕቅዱን 101.7 በመቶ ማሳካት አስችሏል። ከነዚህም ውስጥ የድምፅ አገልግሎት ተጠቃሚዎች 86.9 ሚሊዮን፣ የብሮድባንድ ተጠቃሚዎች 51.5 ሚሊዮን እንዲሁም የፊክስድ ብሮድባንድ ተጠቃሚዎች 1 ሚሊዮን መድረሳቸውን መግለጫው አመላክቷል።
ተቋሙ በዓመቱ 193 አዳዲስ አገልግሎቶችን ጨምሮ በአጠቃላይ 470 ምርቶችን ለደንበኞች ያቀረበ ሲሆን፣ ደንበኞች አገልግሎቶችን በተገቢው መንገድ መጠቀም እንዲችሉ የሚያግዝ የደንበኞች ትምህርት (Customer Education) ፕሮግራም እየተተገበረ እንደሚገኝም ተጠቁሟል።