08/02/2026
" ክልከላው በተለምዶ #ኩርቱ ፌስታልን ጨምሮ በተለያየ ዲዛይን የተሰሩና በቀላሉ በስብሰው ከአፈር ጋር የማይዋሃዱ ፌስታሎችን ያካትታል " - የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን
ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ የፕላስቲክ ከረጢቶችን መጠቀም የሚከለክለው አዋጅ ካሳለፍነው ጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ ተደርጓል፡፡
ህብረተሰቡ ጋር ግርታን የፈጠረው አንዱ ጉዳይ በአዋጁ ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ የተከለከሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች የትኞቹ ናቸው ? የሚለው ነው።
በአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የከተማ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ክትትል ዴስክ ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ዓለሙ ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን (ኤፍኤምሲ) በዚህ ጉዳይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ምን አሉ ?
" በአዋጁ የተከለከሉት የፕላስቲክ ከረጢቶች በተለምዶ #ፌስታል ተብለው የሚጠሩት ናቸው፡፡
እነዚህ ፕላስቲኮችም አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ውለው በቀጥታ የሚወገዱ ሲሆኑ በመልሶ ዑደትም ጥቅም ላይ አይውሉም።
በዚህም መሰረት ክልከላው በተለምዶ ኩርቱ በሚል ስያሜ የሚታወቀውን ፌስታል ጨምሮ በተለያየ ዲዛይን የተሰሩና በቀላሉ በስብሰው ከአፈር ጋር የማይዋሃዱ የፕላስቲክ ከረጢቶች ወይም ፌስታሎችን ያካትታል " ብለዋል።
፦ ከሰሞኑን በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ በተለይ በቲክቶክ " ትንሹ ስስ ፌስታል ብቻ ነው የተከለከለው፤ ትልልቆቹ ፌስታሎች (በተለምኮ ኩርቱ የሚባለው) እና ጠንካራ ፌስታሎች አልተከለከሉም " የሚሉ የተሳሳተ መረጃዎች በተለያዩ አካላት ሲሰራጩ ነበር።
NB. በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 መሰረት የፕላስቲክ ከረጢቶችን የተጠቀመ ወይም ለመጠቀም ይዞ የተገኘ ማንኛውም ግለሰብ ከ2 ሺህ ብር የማያንስ ከ5 ሺህ ብር የማይበልጥ የገንዘብ ቅጣት ይጣልበታል፡፡
#ፌስታል