26/07/2026
፦ የሕፃኑ ቂርቆስና የቅዱስ ገብርኤል አስደናቂ ምሥጢር!!!
#መግቢያ፦ በፈላው የብረት ጋን ፊት የቆመው የንጋት ኮከብ:-
አንድ አፍታ የሥጋ ዓይናችንን ትተን በልቡና ዓይናችንና በምናባችን ወደዚያ ዘመን እንጓዝ! ንጉሡ በእብሪት ተሞልቶ በቁጣ ዙፋኑ ላይተቀምጧል፤ በፊቱም ሰማይ ጠቀስ ነበልባል የሚተፋ ባለ ብዙ ኬሚካል የብረት ጋን እንደ እሳተ ገሞራ እየተንተከተከ በዙ ምዕራፍ በሚሰ'ማ' ነጎድጓዳማ ድምፅ እየደነፋ ነው፡፡ እሳቱ ዙሪያውን ያለውን አየር አሙቆታል፤ የጭስ ደመናና የነበልባል ድምፅ ልብን በሽብር ይሞላል።
በዚያ የሚያስፈራና ነፍስን በሚያርበደብድ ትዕይንት መሃል፣ አንዲት እናት (ቅድስት እየሉጣ) የሰውነትዋ አቅም ከድቷት በድንጋጤ ተውጣ ቆማለች፡፡ ከጎኗ ግን፣ የሦስት ዓመት ሕፃን (ቅዱስ ቂርቆስ) እንደ ንጋት ኮከብ ፈገግ ብሎ፣ የሞትን ጥላ በንጹሕ የልጅነት ዓይኖቹ ንቀት እየተመለከተ ቆሟል።
ይህ ተራ የታሪክ ማኅደር አይደለም፤ የተፈጥሮ ሕግ የተሸነፈበት፣ ቀይ እሳት ከሰማያዊ ጤዛ ጋር፣ የሰው ጭካኔ ከፈጣሪ ፍቅር ጋር የተላተመበት ታላቅ የሰማዕትነት ትእይንት አደባባይ ነው፡፡ የሕፃኑ ቂርቆስና የቅዱስ ገብርኤል ታሪክ፣ ዛሬም ድረስ በዘመናችን እሳት ለሚለበለቡ ነፍሳት ሁሉ የማይጠልቅ የብርሃን ጸዳል ነው፡፡
የሕፃኑ ቂርቆስና የእናቱ የቅድስት እየሉጣ የሰማዕትነት ጉዞ፣ ከሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል አዳኝነት ጋር ተዳምሮ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ደምቆ የሚታይ ሕያው ትምህርት ነው፡፡ ይህንን ታሪክ በጥልቀት ስንመረምረው የሕይወት ስንቅ የሚሆኑ በርካታ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምሥጢራትን እናገኛለን፡፡
፩. የሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አስገራሚ ማንነትና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምሥጢሩ:-
በክርስትና ታሪክ ብዙ ሰማዕታት ቢኖሩም፣ የቂርቆስ ታሪክግን እጅግ ልዩ ከሚያደርጉት ነገሮች መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፦
ሀ. የዕድሜው ማነስ (የ፫ ዓመት ሕፃን)፦ አንድ የሦስት ዓመት ሕፃን ስለ ክርስቶስ ፍቅር ይህን ያህል መከራ መቀበሉ አስገራሚ ነው፡፡ ይህ ታሪክ ንጉሥ ዳዊት በትንቢት መነጽር ተመልክቶ፤ > "ከሕፃናትና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ፤ ስለ ጠላትህ፥ ጠላትንና ቂመኛን ታጠፋ ዘንድ'' (መዝሙር ፷፥፪) ብሎ የዘመረውን ቃል በተግባር የፈጸመ ነው፡፡
ለ. እናትን የሚያጸና ሕፃን፦ በተፈጥሮ እናት ልጇን ታጸናለች፤ ትጠብቃለችም፡፡ እዚህ ጋር ግን እየሉጣ የፈላውን ውሃና እሳቱን አይታ በፈራች ጊዜ፣ "እናቴ ሆይአትፍሪ...'' ብሎ በማጽናናት የሃይማኖት ጀግንነትን አስተምሯታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ሲሞሉ ዕድሜ የሃይማኖት መለኪያ እንደማይሆን አሳይቷል።
ሐ. በከሃዲው ፊት የተመሰከረ እውነት፦ ገና በልጅነቱ አንደበቱ ተፈትቶ በከሃዲው ንጉሥ (በእስክንድሮስ) ፊት የክርስቶስን አምላክነት መመስከሩ፣ "በዚያች ሰዓት የምትናገሩት ይሰጣችኋልና... በውስጣችሁ የሚናገረው የአባታችሁ መንፈስ ነው'' (ማቴዎስ ፲፥፲፱-፳) የሚለውን የወንጌል ቃል ሕያው ያደርገዋል፡፡
፪. እሳቱ ሳይጠፋ ነበልባሉ መቀየሩ፦ የቅዱስ ገብርኤል አዳኝነት ጥልቅ ምሥጢር
ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ ቂርቆስና እየሉጣ የተጣሉበትን የፈላ የብረት ጋን እሳት (ነበልባል) ሙሉ በሙሉ አላጠፋውም፤ ነገር ግን የማቃጠል ባሕርዩን ወደ ቀዝቃዛ ጠልነት ቀየረው፡፡ ከዚህ የምንማረው ታላቅ የሕይወት ምሥጢር አለ፦
ሀ. መከራው ይኖራል፣ ግን አይጎዳንም፦ እግዚአብሔርሁልጊዜ መከራውን (እሳቱን) ከፊታችን ላይጠርግልን ይችላል። በባቢሎን እቶን እሳት እንደተጣሉት እንደ ሠለስቱ ደቂቅ (ሲድራቅ፣ ሚሳቅና አብደናጎ) እሳቱ ይነድዳል፣ እግዚአብሔር ግን በእሳቱ ውስጥ ከእኛ ጋርበመሆን የመከራውን የማቃጠል አቅም ያጠፋዋል (ዳንኤል ፫)። ችግሩ በዓይን ይታያል፣ ግን ውስጣዊ ሰላማችንን አይነጥቀንም፡፡
ለ. በፍጥረት ላይ ያለው መለኮታዊ ሥልጣን፦ እሳት በተፈጥሮው ያቃጥላል። ነገር ግን የፈጠረው አምላክሲያዝዘው፣ የተፈጥሮ ሕጉን ትቶ ለቅዱሳኑ የሰላም ማረፊያ ይሆናል፡፡ ይህ የሚያሳየው የቱንም ያህል የሚያስፈራ የተፈጥሮም ሆነ የሰው ኃይል ቢነሳ፣ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ውጪ አንዲት ጠጉር እንኳ ሊነካ እንደማይችል ነው፡፡
ሐ. የጠላትን ዓላማ ማክሸፍ፦ ጠላት (ንጉሡ) እሳቱ እየነደደ ሲያይ ተቃጥለዋል ብሎ አስቦ ነበር፡፡ እሳቱ አለመጥፋቱ ለጠላት እብደትንና ሞኝነትን፣ ለቅዱሳኑ ግን የእግዚአብሔርን አዳኝነትና የክብር መገለጫ ሆኗል።
፫. ሐምሌ ፲፱ (19) ለምን በታላቅ ድምቀት ይከበራል?
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐምሌ ፲ ፱ ቀን በድምቀት (በተለይም በቁልቢ፣ በባታና በተለያዩ አድባራት) የሚከበርበት ዋነኛ ምክንያት የቅዱሳኑ የዕረፍት ቀን ስለሆነ አይደለም፦
ሀ. የተአምሩ መታሰቢያ፦ በዚህ ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ታዞ በመውረድ ሕፃኑን ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት እየሉጣን ከፈላው የብረት ጋን ውስጥ በተአምራት እሳቱን አብርዶ ያዳነበት ዕለት ስለሆነ ነው፡፡
ለ. የመዳን ተስፋ፦ ምእመናን 'በእሳትና በውሃ ውስጥ ያለፍነውን ያዳነ፣ ለቂርቆስ የደረሰ መልአክ ዛሬም ለኛ ይደርሳል" በሚል ጽኑ እምነት የእግዚአብሔርን ኃይልና የመልአኩን ተራዳኢነት በማሰብ በታላቅ ምስጋና ያከብሩታል።
ሐ. ዛሬም የሚደረግ ተአምር:- በእነ ቅዱስ ቂርቆስ እምነት ለተሞሉ ምእመናን ዛሬም ይህ የመልአኩ ፍጡን ረድኤት በሥራ ላይ ነው:: ከተነገሩና ከተፃፉ ተአምራት ያልተነገሩና ያልተፃፉት ይበዛሉ::
፬. ለዛሬው ሕይወታችን የምንወስደው ስንቅ:-
የእነዚህ ቅዱሳን ታሪክ የትናንት ትዝታ ብቻ ሳይሆን፣ ለዛሬው ክርስቲያናዊ ሕይወታችን መስታውት ነው፦
ሀ. የዘመናችን እሳት፦ ዛሬ ቃል በቃል ወደ እሳት ባንጣልም፣ የጭንቀት፣ የበሽታ፣ የድህነት፣ የጦርነት እና የፈተና እሳት ይከበናል። ፈጣሪ እነዚህን እሳቶች ቢያበርድልንና ወደ ሰላም ቢቀይርልን እንጂ በእሳቱ ጥንካሬ ልንወድቅ አይገባም፡፡
ለ. ድፍረት በጸሎት፦ እንደ ቂርቆስ "አትፍሪ" የሚል ጠንካራ የውስጥ ድምጽ ሊኖረን ይገባል፡፡ እሳቱን ሳይሆን፣ እሳቱን የሚያበረደውን አምላክ በማየት በእምነት ጸንተን ልንቆም ያስፈልጋል።
ሐ. ፈተናችን እያለ የሌለ ይሆናል:- እግዚአብሔር ሁልጊዜ እሳቱን ከፊታችን አያጠፋውም፤ ነገር ግን በእሳቱ መሃል ከእኛ ጋር ሆኖ የማቃጠል ኃይሉን ይነጥቀዋል።
#ማጠቃለያ፦ የማይጠፋው ነበልባልና የማያቃጥለው እሳት:-
እሳቱ ነደደ፣ ነገር ግን አላቃጠለም፤ የከሃዲው ንጉሥ ዛቻም እንደ ከንቱ ጢስ በነፋስ ተበተነ። በፈላው የብረት ጋን ውስጥ የገባው የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል የብርሃን ክንፍ፣ ገሀነማዊውን እሳት ወደ መንፈስን የሚያለመልም ሰማያዊ ጠልነት ለወጠው፡፡
የሕፃኑ ቂርቆስና የእናቱ የቅድስት እየሉጣ ታሪክ የሚያስተምረን ትልቁ እውነት ይህ ነው፦ እግዚአብሔር ሁልጊዜ እሳቱን ከፊታችን አያጠፋውም፤ ነገር ግን በእሳቱ መሃል ከእኛ ጋር ሆኖ የማቃጠል ኃይሉን ይነጥቀዋል። አወን! እግዚአብሔር ፈተናችን እያለ የሌለ ሊያደርግልን ይችላል:: ይህም የእርሱ ተግባር መሆኑን መለያ ነው::
ዛሬም ቢሆን በእያንዳንዳችን ሕይወት ውስጥ የሚንከተከት የየራሳችን "የብረት ጋን" ሊኖር ይችላል፡፡ የጭንቀት፣ የበሽታ፣ የጦርነት ወይም የፈተና እሳት ዙሪያችንን ከቦን ይሆናል፡፡ ነገር ግን እሳቱን አይተን አንፍራ! ከእሳቱ ግለት ይልቅ፣ በረድኤት የሚጠብቀንን የቅዱስ ገብርኤልን ክንፍ እናስብ።
ዛሬም ዘመኑ ለለኮሰብን ማንኛውም አይነት እሳት፣ እግዚአብሔር የማዳን ጠሉን ይዞልን ይመጣል። ከእኛ የሚጠበቀው እንደ ሕፃኑ ቂርቆስ "አልፈራም፣ አምላኬ ከእኔ ጋር ነው!'' የሚል የማይናወጥ የልብ ጽናት ብቻ ነው! የቅዱሱና የቅዱሳኑ ፍቅር ትብዛልን! አሜን!
ፍ ቅ ረ ፍ ቅ ር ዘ ፍ ቅ ር :- አቤቱ ወዳጄ ሆይ እወድህ ዘንድ እወዳለሁ!!!