16/03/2026
የክልሉ መንግሥት የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ሕገ-ወጥ ተዋናዮችን በመከታተል ፍትሃዊ አቅርቦትና ስርጭት እንዲረጋገጥ በልዩ ትኩረት ይሠራል፦ አቶ አሻድሊ ሀሰን
*************
(አሶሳ፣ መጋቢት 07/2018 ዓ.ም) የክልሉ መንግሥት የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ሕገ-ወጥ ተዋናዮችን በመከታተል ፍትሃዊ አቅርቦትና ስርጭት እንዲረጋገጥ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በክልሉ በወቅታዊ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት ዙሪያ በአሶሳ ከተማ ከሚገኙ የነዳጅ ማደያ ባለቤቶች ጋር ውይይት አካሂደዋል።
አቶ አሻድሊ ሀሰን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ ነዳጅ በመንግሥት ከፍተኛ ድጎማ እየቀረበ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ ለፍትሃዊ ስርጭቱ በትብብር እና በቅንጅት መሥራት ይገባል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሁን ካለው የኢኮኖሚ እና የተለያዩ ፕሮጀክቶች እንቅስቃሴ መጨመር ጋር በተገናኘ የነዳጅ አቅርቦት እና ፍላጎቱ እየተጣጣመ አለመሆኑን ገልጸዋል።
በሌላ በኩል ወደክልሉ የሚመጣውን ነዳጅ በፍትሃዊነት በማሰራጨት በኩል የሚስተዋሉ አሻጥሮች በአስቸኳይ ሊታረሙ እንደሚገባ ጠቅሰው፣ መንግሥት ለነዳጅ ፍትሃዊ አቅርቦትና ስርጭት የተለዬ ቁጥጥር እና ክትትል ያደርጋል ብለዋል።
ለሕዝብ አገልግሎት የሚውል ናፍጣ ከማደያ በታሪፉ ቀድተው ሕዝቡን የተጋነነ የትራንፖርት ዋጋ የሚያስከፍሉ እና ወደጥቁር ገበያ የሚያቀርቡ አሽከርካሪዎች እና ሌሎች አካላት ከዚህ ድርጊት እንዲቆጠቡ አስገንዝበዋል።
ሕዝብን ወደ እንግልት የሚያስገቡ አካሄዶችን መንግሥት አይታገስም ያሉት አቶ አሻድሊ፣ የማደያ ባለቤቶችም
የሕዝብ አገልጋይነትን ተላብሰው ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የክልሉ መንግሥት ነዳጅ ከሚያቀርቡ ካምፓኒዎች ጋር ያሉትን ችግሮችን ለመፍታት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት አቅርቦቱ እንዲሻሻል እንደሚሰራም ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል።
በነዳጅ አቅርቦት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ ዓለማቀፍ ሁኔታዎች እስኪሻሻሉ ድረስ የሚገኘውን ነዳጅ እና ቤንዚል ለሕዝብ መገልገያ እና ለወሳኝ ፕሮጀክቶች በቁጠባ በመጠቀም ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ማሠራጨት ያስፈልጋል ብለዋል።
የማደያ ባለቤቶች በበኩላቸው፣ የመንግሥትን አቅጣጫ ተከትለው የሚገኘውን ነዳጅ በፍትሃዊነት ለማሠራጨት እንደሚሰሩ ጠቁመው፣ የመንግሥት ድጋፍ እና እገዛ ሊጠናከር እንደሚገባ ተናግረዋል።