13/12/2025
የለውጡ መንግሥት ውስብስብ ችግሮችን በመፍታት ታላላቅ ሀገራዊ ድሎችን ማስመዝገቡን በብልፅግና ፓርቲ ዋና ጽ/ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ ገለጹ
*************
(አሶሳ፣ታህሳስ 4/2018 ዓ.ም) የለውጡ መንግሥት ውስብስብ ችግሮችን በመፍታት ታላላቅ ሀገራዊ ድሎችን ማስመዝገብ መቻሉን በብልፅግና ፓርቲ ዋና ጽ/ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ ገለጹ።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል "የጉባ ብስራቶች፤ የመደመር መንግስት ትሩፋቶች" በሚል መርህ ሀሳብ ህዝባዊ የውይይት መድረክ በአሶሳ ከተማ ተካሂዷል።
በመድረኩ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ ዋና ጽ/ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ፣ በመደመር መንግስት የብሔሮች ብሔረሰቦች እና ህዝቦች በጠንካራ ህብረ ብሄራዊ አንድነት የተጋመደ ብልፅግናን እንዲያረጋግጥ በርካታ እርምጃዎች መወሰዱን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያን ታላላቅ በረከቶችን ለማጨናገፍ የሚታትሩ ባንዳዎችን በታላላቅ ብስራቶችና ትሩፋቶች ማምከን ተችሏል ብለዋል።
የህዝቡ አብሮነት እና አንድነት እንዲቀጥል በርካታ መስዋዕትነት መከፈሉን የተናገሩት አቶ ፍቃዱ፣ ታሪካዊ ጠላቶችን በጋራ መታገል እንደሚገባም ገልጸዋል።
እንደ ሀገር ውስብስብ ችግሮችን በመቋቋም ታላላቅ ድሎችን ማስመዝገብ መቻሉን ጠቅሰው፣ መንግስት የህዝቡን ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ በመፍታት ዘላቂ ሰላምና ብልፅግናን ለማረጋገጥ እየተራ ነው ብለዋል።
የተጀመሩ ፕሮጀክቶች በመፍጠን፣ መፍጠር እና መዝለል እሳቤ የተቃኘ በማድረግ በጥራትና በፍጥነት እንዲከናወኑ በቅርበት እንደሚሰራም ጠቁመዋል።
የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ የሚያስችሉ የሌማት ትሩፋት፣ የአረንጓዴ አሻራ፣ የክረምትና የበጋ ወራት አገልግሎቶችን በማስቀጠል ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ያስፈልጋል።
በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ኢሳቅ አብዱልቃድር፣ ባለፉት ዓመታት በክልሉ ተከስቶ የነበረው የፀጥታ ችግር በዕቅድ የተያዙ መሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ አዳጋች እንደነበር ገልጸዋል።
ይሁን እንጂ ክልሉን ወደሰላም በመመለስ እና የተገኘውን ሰላም በመጠቀም በርካታ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ሲሆን፣ ለዚህ ስኬት የህብረተሰቡ ድጋፍ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።
ከለውጡ ወዲህ ክልሉ ያለውን እምቅ ሀብት በማልማት ህብረተሰቡ ከዘርፉ ተጠቃሚ እንዲሆን የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አቶ ኢሳቅ ጠቅሰዋል።
በክልሉ በተለያዩ ከተሞች የኑሮ ውድነት እንዲባባስ በማድረግ እና ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት የሚታትሩ አካላት ከድሪጊታቸው ሊቆጠቡ እንደሚገባም አቶ ኢሳቅ አስገንዝበዋል።
የሶማሌ ክልል ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሀሊሞ ሀሰን በበኩላቸው፣ መንግስት የህብረተሰቡን አዳጊ ጥያቄዎችን በመለየት ደረጃ በደረጃ እየፈታ ይገኛል ብለዋል።
መንግስት የዜጎችን የኑሮ ውድነትን ለማሻሻል የጀመረውን እርምጃ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ጠቁመዋል።