01/03/2026
ዕቅበተ እምነት የክርስትናን ያክል ዕድሜ ጠገብ ነው። ለርትእ በመወገን ሐዋርያቱን የቀደመ አልነበረም። ትንሳኤ ሙታንን ሰዎች ሲክዱና ሲጠራጠሩ የጠረቀ ሙግት ያቀረበው የጠርሴሱ ቅዱስ ጳውሎስ ነው። (1ኛ ቆሮ 15)። ክርስቶስ በስጋ የተገለጠ መኾኑ ሲካድ (Docetism) ቀድሞ ሙግት ያቀረበ ቅዱስ ዮሐንስ ነው። (1ዮሐ 1:1-4)። ስለ ተቀበልነው ተስፋ ጥያቄ ሲነሳ ምላሽ ለመስጠት የተዘጋጀን እንድንኾንም ያሳሰበን አእማዱ ቅዱስ ጴጥሮስ ነው። (1ኛ ጴጥ 3:15)።
እቅበተ እምነታዊ ጥናቶች ካበረከቱ ሰዎች መኻል ናቸው። ጆን ሊኒንክስ፣ አለቪን ፕላቲንጋ(የኔ የብዙ ግዜ የመጀመሪያ ምርጫዬ)፣ ፍራንሲስ ሻፈርና አሊስተር ማግራዝም ሰፊ እቅበተ እምነታዊ ስራን ለቤተ ክርስቲያን ያበረከቱ ምሁራን ናቸው። በኛም ሀገር የዶ/ር ተስፋዬ ሮበሌን ትጋትና ጥረት ማንሳት እንችላለን።
በምሁራንና ቤተ ክርስቲያንን በሚወዱ አሳቢዎች ይመራ የነበረው ይኽ አገልግሎት በአላዋቂ ሳሚዎች እየተጠለፈና እየተመረዘ ነው። ነገር በማይጠግቡና በሚያመነዥጉ ዕቡያን እየተጎሳቆለ ነው። ከክብሩ እያሽቆለቆለ ነው። ተልእኮውንና ግቡን እየሳተ ነው። ከእውቀትና እውነት እየፈታ ነው። ከንቱ ብሽሽቃችንና ማለቂያ የሌለው ንትርካችን ዘርፉንና አገልግሎቱን ምን ያክል እንዳስነቀፈ ባወቅን! ክርስትናንንና የወንድማማች ኅብረትን ምን ያክል እንዳጎደፍን ባስተዋልን! ለችኮላችንና ድፍረታችን፤ ለጥበታችንና ርኅራኄ ማጣታችን እቅበተ እምነት ዋጋ ሊከፍል አይገባውም። ለክብር ጥማታችንና ራስን መቆለላችን ምካቴ ክርስትና መደቆስ አይኖርበትም። እውነትን በፍቅር መያዝ ባልሰለጠኑ ሰነፎች እጅ እውነትም እውቀትም ፍቅርም መገፋት አይኖርባቸውም!
ኢብሳ ቡርቃ