07/06/2026
ሐዋሳ በልማት ያስመዘገበቻቸው ድሎች በስፖርቱም ዘርፍ ሊደገሙ ይገባል” – ከንቲባ ጥራቱ በየነ
ሐዋሳ፣ ግንቦት 30/2018 ዓ.ም
በሐዋሳ ከተማ በልማት መስኮች እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶች ለከተማዋ ነዋሪዎች ተስፋና ኩራት እየሆኑ ባሉበት ወቅት፣ ይህ መነቃቃት ስኬት በስፖርቱም ዘርፍ እንዲታይ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ጥሪ አቅርበዋል።
የሐዋሳ ከተማ ከንቲባና የሐዋሳ ከነማ እግር ኳስ ክለብ የበላይ ጠባቂ አቶ ጥራቱ በየነ ከክለቡ ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞች፣ የክለቡ አመራሮች እና የደጋፊ ማህበር አባላት ጋር ባደረጉት ውይይት፣ የቡድኑ ስኬት ከውድድር ውጤት ባለፈ የከተማዋን ሕዝብ ተስፋና ኩራት የሚወክል መሆኑን አስገንዝበዋል።
ከንቲባው በዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሐዋሳ ከነማ እያሳየ ላለው ጥሩ አፈጻጸም ምስጋና አቅርበው፣ በቀሪዎቹ ጨዋታዎች በተጨማሪ ቁርጠኝነትና ትጋት በመጫወት የውድድር ዘመኑን በላቀ ውጤት እንዲያጠናቅቁ ተጨዋቾችና የቡድኑ አባላት የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
በውይይቱ ወቅት ተጫዋቾች ያነሱትን ሀሳብ በትኩረት ያዳመጡት ከንቲባው፣ የከተማ አስተዳደሩ ለቡድኑ የሚያስፈልገውን ድጋፍና ማበረታቻ በቀጣይም እንደሚያደርግ ቃል ገብተዋል።
በመድረኩ የሐዋሳ ከተማ ስፖርት ክለብ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ መልኩ ማርቆስ በበኩላቸው በ2017 ዓ.ም የታዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ሰፊ ርብርብ መደረጉን ገልጸው የአስተዳደር፣ የፋይናንስና የውጤት ችግሮች በዝርዝር ተገምግመው በተወሰዱ እርምጃዎች የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉንና ዘንድሮም የውድድር ዘመን በድል ለማጠናቀቅ በቂ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል።
በውይይቱ የተሳተፉ ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞችና አመራር አካላት በበኩላቸው፣ ከንቲባው ያደረጉት ውይይትና ማበረታቻ በቀጣይ ጨዋታዎች ላይ ትልቅ መነቃቃት እንደሚፈጥር ገልጸዋል።