
27/05/2025
" ቆማ ፋሲለደስ ክበቡ ክበቡ
እንኳን ሳር ቅጠሉ ያስደምማል ካቡ "
( በታዴ የማመይ ልጅ )
የረቀቁ አብያተ ክርስቲያናት፣ የተዋቡ አብያተ መንግሥታት፣ እጹብ የሚያሰኙ ገዳማት ህብረት የፈጠሩበት ይህ ስፍራ የአምላክ ድንቅ ጥበብ ይታይበታል ።
ፈጣሪ አሳምሮ የሠራቸው ተራራዎች፣ ሸለቆዎች፣ ኮረብታዎች ታሪክ ይናገራሉ በምድሩ የበዙ ገዳማትና አድባራት ይገኛሉና ዙሪያ ገባቸው ቅዱስ መንፈስ ሞልቷል ። ።
ቆላማ ደጋማ በርሃና ወይንአደጋ የአየር ፀባይ በአንድነት የከተሙበትን ተፈጥሮዉን የተመለከተ ስም አዉጭም በጎ ለም ገር ምድር ነዉና በጌምድር ብሎታል ።
ታዲያ በዛሬው የቱሪዝም ማዕዳችን በዚሁ ግንደ ሃገር ጎንደር ደቡባዊ አቅጣጫ ተጉዘን ዘመናትን የተሻገረ ድንቅ ስፍራ ልንጎበኝ እስቴ ወረዳ ዘልቀን ልናስተዋዉቃችሁ ወደናል ። ታተርፋላችሁና ሃሳብ አስተያየት እየሰጣችሁ ተከተሉን።
ከታላቁ ንጉሥ አፄ ፋሲል ጋር ተያይዞ ስሙ ተደጋግሞ የሚነሳው “ቆማ የፋሲለደስ” መገኛዉ በደቡብ ጎንደር ዞን እስቴ ወረዳ ዉስጥ ሲሆን “ቆማ” ስያሜዋን ያገኘችው በአጼ ፋሲል እናት በንግሥት ወልደ ሳህላ እንደሆነ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ።
ስያሜው ቅዱስ ፋሲለደስ ቢሆንም ቆማ የሚለዉን መለያ ያገኘው እንዲህ ነበር ይባላል በአፈ ታሪክ ።
በ1657 ዓ.ም. በንጉሥ ሱስንዮስ ሚስት በአጼ ፋሲል እናት በንግሥት ወልደ ሳህላ የበላይ ተከታታይነት ቤተ መቅደሱ ተገንብቶ ከተጠናቀቀ በኋላ የክብረበዓሉ እለት
ለቤተመቅደሱ ምርቃት ሊታረድ የተሰናዳው ነጭ በሬ የእርድ ሂደቱን አቋርጦ አመለጠ። ህዝቡም በሬውን ለመያዝ ሲሮጥ ንግሥቲቱ “በሬውን አትያዙት” አሉ። “ዝምብላችሁ ተከተሉት” ህዝቡም የታዘዘውን ፈጸመ። ለንግሥቲቱ “በሬው የት ደረሰ?” ለሚለው ጥያቄ ሕዝቡ “ቆመ” ሲል የሰጠው ምላሽ እስካሁን የአካባቢው መጠሪያ በመሆን እያገለገለ ይገኛል።
ንግስቲቱ በሬው የቆመበት ሥፍራ አጋጣሚ ሳይሆን ፈቃደ እግዚአብሄር እንደሆነ ተቀበሉ። በመጀመርያ እድሞ (አጥር) እና እቃቤት በድንጋይ እና በኖራ አሰሩ። በመቀጠልም ቤተ-መቅደሱን አሳነጹ። ስለ አሰራሩ የሚያስረዱት የገዳሙ አባት “ግማሹ በኖራና በድንጋይ የታነጸው ቤተ-መቅደስ የተጠናቀቀው በጭቃ ነው። የበቁ አባቶች እድሜሽ አጭር ነው ስላሏት ሞትን ለመቅደም በጭቃ ተጠናቀቀ” ይላሉ።
“ቤተ ክርስቲያኑን በ1624 ዓ.ም. አፄ ፋሲል የደብርና የገዳም ሥርዓት እንዲፈፀምበት ርዕሰ አድባራት ወገዳማት ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ብለው ሰይሙታል” የሚሉትን ደግሞ
የገዳሙን መዛግብት እንዳሻቸው መመርመር የሚችሉት ገዳማዉያን ናቸው፡፡
አክለዉም በገዳሙ ዙርያ ያሉ 44 አድባራት የሚገኙ ምእመናን ለገዳሙ ግብር እንዲያስገቡ በ318 አገልጋዮች እንዲገለገል፤ በደናግል መነኮሳት እና አስራ ስምንት ዓመት ባልሞላቸው ዲያቆናት አገልገሎት እንዲሰጥ እንዳደረጉ ያብራራሉ።
በንግሥቲቱ የተሰጠ ሰፊ የእርሻ መሬትም ነበረው። የድመት መሬት (ለእቃ ቤት ጠባቂዋ ድመት የእርሻ መሬት ተዘጋጅቶ ኑግ እየተዘራ ትመገብ ነበር)፣ ለአጽጂዎች፣ ለብረት ባለሙያዎች፣ ለሸማኔዎች መሬት ነበራቸው ይላል የገዳሙ ታሪክ ።
ለርዕስ አድባራት ወገዳማትነት መገደም አጼ ፋሲለደስ እናት ከፍ ያለ አስተዋጽኦም አበርክተዋል ።
የጥንቱ ሕንጻ ኪነ-ቅርጽ ከፋሲል ግቢ ጋር የሚመሳሰል ሲሆን በክብ ቅርፅ የተሰራ ነው። ሦስት ክፍል አለው። በእንክብካቤ እጥረት ቢጎዳም ውበቱን ጨርሶ አልጠፋም። ከመሬት ወደ ላይ 6 ሜትር ከፍታ የካብ ዕድሞ /አጥር/፣ የትምህርት መስጫ ባለ ሰገነት ጉባኤ ቤት አለው።
ቤተ ክርስቲያኑ በሰማዕቱ ቅዱስ ፋሲለደስ ስም የተደበረ ከመሆኑም በላይ ንጉሱ ርዕሰ ገዳማት እንዲሆን አድርገዋል በዘመናቸው መስከረም 11 እና ታህሳስ 11 ክብረ በዓሉ ደማቅ የነበረ ከመሆኑም በላይ ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ክብረ በዓሉን የእስልምና ተከታዮችም ያከብሩት እንደነበር የደብሩ አባቶች ያስረዳሉ።
የንቀት ይሁን ከእዉቀት እጥረት በ 2005 በተደረገለት እድሳት የቤተ ክርስቲያኑ የውጭ ገፅታ በሲሚንቶ የተሰራ በመሆኑ ታሪካዊነቱን አጥፍቶታል። የቤተመቅደሱ እና የቅድስቱ ግድግዳ ግን ጥንት እንደነበረ ስለመሆኑ ሸበቶ ገፅታው ያሳብቃል ።
ለታሪክ ግድ የለሾች በቀመርና በእርጋታ ኖራን ከእንቁላል ተቀይጦ የተሰራዉን በቻይና ስሚንቶ መርገዉ ሞገሱን ቢያደበዝዙትም ታሪክ ዘካሪዎቹ በቅድስቱ ውስጥ 12 የእንጨት ምሰሶዎች አሉ። ምሶሶዎቹ ወይራ እና ጥድ ከእንቧጮ ዛፍ ጋር በማጣበቅ ይዘጋጃል። እንጨቶቹ የተያያዙትም ካለምንም ማጣበቂያ እርስ በርስ በማያያዝ ነው። ምሰሶዎች ሲተከሉ ቤተክርስቲያኑን የሚገነቡት ሰዎች ምሶሶዎቹን መትከል ከብዷቸው ትተውት ሲሄዱ አንድ ባህታዊ ብቻቸውን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እንደተከሉት ይነገራል።
የተቆርቋሪ ማጣት የባለሙያዎች ግዴለሽነት ምክንያት የሌለ ያህል የተረሳውና ለአካባቢው የቱሪዝም መስህብ መዳረሻ መሆን የሚችለው ገዳም በአባቶች ተጋድሎና ጠባቂነት ዛሬም ድረስ አራት መቶ አመታትን የተሻገሩ እንድንመለከተው የተፈቀዱና ያለውን ተፈቀዱ ብዙ ጥንታዊ ቅርሶችን ይዞል ከአፄ ፋሲል፣ ከንግሥት ወልደሳህላ እና ከሌሎች ነገሥታት የተበረከቱ የብራና መጻሕፍት፣ የብረት ደውል፣ የብር ከበሮ፣ ነጋሪት፣ የወርቅ መስቀል እና ልዩልዩ ጥንታዊ ቅርሶች ጎብኝ ሊመለከታቸዉ የሚችሉ መካከል ይጠቀሳሉ ።
በተጨማሪም በዚህ ቤተክርስቲያን ከሚገኙ ጥንታዊና የማይቀሳቀሱ ቅርሶች መካከል የግድግዳ ላይ ሥዕሎች፣ በጎንደር ዘመነ መንግሥት የግንባታ ጥበብ የተሰሩት የቤተክርስቲያኑ አጥር፣ እቃ ቤት እና ሕንፃ ቤተክርስቲያኑ ናቸው።
ከዚህም ባሻገር ይህን ቤተክርስቲያን ልዩ ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ እቃ ቤቱ እና የቤተክርስቲያኑ ጉልላት ላይ ያሉ መስቀሎች ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተሰሩ መሆናቸው ነው። ሌሎችም ለበርካታ ዓመታት የኖሩ ቅርሶች ከብር፣ ከወርቅ፣ ከእምነ በረድ ከሌሎች ማዕድናት የተሰሩ ንዋየ ቅድሳት ይገኛሉ።
ቆማ ፋሲለደስ በጣልያን ወረራ ወቅትም ለመዳፈር በሞከሩት ወራሪዎች ላይ ተዓምር ተፈፅሞበታል ።
ሌላው የዚህ ገዳም መገለጫ ደግሞ ዜማው ነዉ ።
የቆማ ዜና ርክርኩ(ጉሮሮ) ረዥም በመሆኑ አንድ አንድ ቦታ ላይ ዘሩ (ቁጥሩ) የሚለይ መሆኑ እና ዜማውን ለመማር ክብደት ያለው በመሆኑ ከሌሎች ዜማዎች ይለያል። የቆማ ዜማ ድጓ መጻሕፍት በታላላቅ ገዳማትና አድባራት የሚገኝ ሲሆን በአክሱም፣ ላሊበላ እና በመካነ ኢየሱስ እንደሚገኝ ይገመታል። የቆሜ ዜማ ምስክርነት የሚሰጠው በቆማ ፋሲለደስ ቤተክርስቲያን ነው።
እንደ አንድ የታሪኬ ጉዳይ ያገባኛል የአባቶቼ ልጅ ነኝ ለሚል ሰዉ ይህ ቅርስ የተያዘበት ሁኔታን ተመልክቶ ማዘኑና አይቀርም ለነገሩ እንዲህና መሰል የማንነት ምልክቶች አተኩሮ የሚሰራው የራዲዮ ዝግጂታችን በስፖንሰር ማጣት በአጋዥ አለመኖር ለመቆም ጫፍ ላይ ባለበት ሁኔታ ከእዝነት ዉጭ ሌላ የማድረግ አቅሙ የለኝምና ዝም ብዬ አንድ እንኳን ሃገር ወዳድ ቢገኝ ያየሁትን አስጊ የህልውና አደጋ ጠቁሟ ላብቃ ።
በአሁኑ ወቅት በቤተ ክርስቲያኑ በርካታ ረዥም እድሜ ያስቆጠሩ ቅርሶች ቢገኙም የሌላ የጠላት ንብረት ይመስል በአያያዝ ችግርና ባለመጠገናቸው እየተበላሹ መሆኑን ታዝቢያለሁ ። እነዚህም ችግሮች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ የግድግዳ ሥዕሎች መበላሸት እና በእቃ ቤቱ የሚገኙ ቅርሶች በቦታ ጥበት ምክንያት ተደራርበው በመቀመጣቸው እየተጎዱ ይገኛሉ ትኩረት ይሻሉ። እናም ሲያሻን በዘፈን ወይም በግጥም የ ነገስታትን የጀብደኝነት ታሪክና የእነሱ ልጅነት ደጋግሞ መናገር ሳይሆን አሻራቸውን መጠበቅ ነዉ የእዉነተኛዉ ልጅነት መገለጫ እያልኩ ላብቃ ።
ዮፍታሔ መጻሕፍት መደብር Yoftahie Bookstore
t.me/yoftahiebooks