08/12/2025
የዝናና ታዋቂነት ጥማት አዲሱ ጣኦት
💢💢💢💢💢💢💢💢💢💢💢
በአሕመዲን ጀበል
🔥🔥🔥🔥🔥🔥
ማህበራዊ ሚዲያ በሰዎች ልቦና የሚመለክ ጣኦት እየተከለ ነው።ሲጀምር የላይክ፥ የተከታይና የእይታ ብዛት፥ ቫይራል መሆን እያለ ነው።ቀጥሎም የእውቅና ቅቡለነትን መፈለግ ይከተላል። እነዚህ ሁሉ ለመልካም ዓላማና ስነምግባርን በተከተለ መንገድ ስንጓዝ የሥራችን ዉጤት ተከትለው የመጡ ከሆኑ ጠቃሚ ናቸው።
በማህበራዊ ሚዲያ ዝናና ታዋቂነት ወዲያው የሚገኝና አልጎሪዝም መር ናቸው። ከባዶ ጽሑፍ ከፎቶግራፍ ጋር የተለጠ ጽሑፍ ብዙ ሰው ይደርሳል። ከጽሑፍ ፎቶ ግራፍ ይልቅ ቪዲዮ በቀላሉ እይታ ያገኛል። ከተለመዱ ቪዲዮዎች ወጣ ያሉ ቪዲዮዎች የበለጠ ይሰራጫሉ።
የማህበራዊ ሚዲያ ይዘቶች እንዲሰራጩ የተቀመረው አልጎሪዝም የሚያበረታታውና የሚሸልመው የሰዎችን ትኩረት መሳብ ለሚችሉ ነገሮች ነው። ትኩረት በተሳበ ቁጥር ታዳሚ ይገኛል። ታዳሚ በተገኘ ቁጥር ማስታወቂያ የሚያሳያቸው ሰዎች በብዛት ይገኛሉ። እነርሱ በብዛት ተገኙ ማለት ማስታወቂያ ለማሰራት የሚመጡ ከፋዮች ይመጣሉ። ብዙ ከፋዮች ከመጡ ብዙ ገቢ ይገኛል። ከዚህ ስሌት በመነሳት አልጎሪዝሞቹ ብዙ ሰው እንዲሳብላቸው ወጣ ያሉና አነጋጋሪ ለሆኑ ድርጊቶችና ባህሪያት ቦታ ይሰጣሉ።
ከዚህ የተነሳ ይበልጥ ጋጠወጥና አነጋጋሪ የሆኑት በቀላሉ ታዋቂነትን መጎናጸፍ ይችላሉ። በዚህ ምክንያት ይህን የተረዱ ሰዎች እይታ ለማግኘት ሲሉ የራሳቸውን ሃይማኖት ህግጋት ጭምር ይጥሳሉ፤ የሌሎችንም ሃይማኖትና ማንነትን እስከ መሳደብ ደረሱ። ተከታዮችን ለመሳብ ሲሉም አጓጉል አለበባስ አልያም ወጣ ያለባህሪያትን በማሳየት ላይ ተጠመዱ። ይዘት ለመፍጠር ብለው ኃጢአት የሆኑና ትውልድ በካይ አስተሳሰቦችን ወደ ማግበስበስ ገቡ።
ከፍያለ እይታን ለማግኘት ሲሉ ከፊሎቹ ራሳቸው አወዛጋቢ አደረጉ። ከፊሎቹ ደግሞ አወዛጋቢ ነገሮችን እያነፈነፉና እየፈጠሩ በማስፈፋት ላይ ተጠመዱ። በዚህም የራሳቸውን ስብዕና አርክሰው የማህበረሰቡን የማንነትና የባህልን ድንበር ጣሱ። ለራሳቸው ገቢ ብቻ በማሰብ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ በሚረጩት አደገኛ መርዞች ቀጣዩ ትውልድ ከሞራልና ከባህል ያፈነገጠ አዲስ ማንነትና ባህል እንዲላበስ እየተጉ ነው።
ሌሎች ስምና ዝና የሚፈልጉ ተቋማት ምርታቸውን ለመሸጥ እንዲችሉ የነርሱ አዳማቂ ሆኑ። ሌሎች ደግሞ ከነርሱ ጎን ቆመው ታይታን ለማግኘት ሲሉ በነርሱ መድረክ እና ዝግጅቶች ላይ ታዳሚ ሆኑ።ሌሎች ደግሞ መወገዝን ፈርተው ዝምታን መረጡ። ሌሎች ደግሞ የጥፋቱን ገጽታ ቸል ብለው የጠቃሚነት ገጽታው ብቻ ጎልቶ እንዲታይ ተከላካይ ሆነው ቀረቡ።
በዚህም አካሄድ ስንትና ስንት ኃጢአቶችን ህዝቡን አለማመዱ። በፈጠራ ስም የአፍረተ ቢስነትን ልማድ ወጣቱ ላይ አስረጹ። በድራማ ስምም ጋጠወጥነት መዝናኛ ሆኖ ሕዝቡ እንዲጋት ተደረገ።ከዚህ የጥፋት ምንጭ የተጋተ ሰውም እየጣመው «እነርሱን አትንኩብኝ»፤ «አርኣያዎቼ ናቸው» ሲልም እስከ መደመጥ ተደረሰ። ሙስሊሞች ጭምር መገኘቱ በሚያሳፍር ቻናሎችና ይዘቶች ስር «ማሸአላህ» እያሉ ሲያዳንቁ መታየት ተለመደ።
ጥቂቶቹ ከሙስሊምነት ብዙውን ጥለው ሌሎች ደግሞ ሂጃብ መሳይ ሻሽ በራሳቸው ላይ ጣል አድርገው «በፍቅር ታሪክ ስም» የዝሙት ታሪኮችንና የሰዎችን ገበና እያፈላለጉ ለትውልዱ መጋት ተያያዙ። አላህ ሁላችንንም ወደ ቅኑ ጎዳና ይምራንና።
ወጣቱም ተምሮ ለራሱና ለሀገር ጠቃሚ ዜጋ ከመሆን ይልቅ የማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን ሆነ ምኞቱ። እንደነርሱ በመሆን በአቋራጭ ዝነኛና ሀብታም መሆን ይቻላል ብሎ ወደማመን አዘነበለ። ይህም በየቤቱ የትምህርት መማሪያ መጽሐፍ ሳይሆን ዘመናዊ ተንቃሳቃሽ ስልክ እንዲገዛለት የሚወተውት ወጣት እንዲበራከት አደረገ።
ጊዜውንም እነዚያ ጋጠወጦችን እያደነቀ ከነርሱ ስር ተጥዶ ሲቀመጥ ከትምህርት እየራቀ ሄደ። በነርሱ መንገድ በመሄድ ይበልጥ እይታ ለማግኘት፥ ታዋቂና ዝነኛ ለመሆን ከነርሱ የላቀና አዲስ ነገር ይዞ መገኘት አስፈላጊ ሆነ።
በዚሁ መንገድ አንዳንዶች ባለበትዳር የሆኑ ጥንዶችን በካሜራ ፊት እንዲሳሳሙ እያደረጉ ሲያቀርቡም ታዩ። ሌሎችም ከትዳር ዉጭ ያለን ግንኙነት «ፍቅረኞች» በሚል ታፔላ ሲሳሙ እያሳዩ የዝሙት መንፈስን በወጣቱ ልቦና መትከል ተያያዙት። ሌሎች ደግሞ የቅርብ ዘመዳሞችን፣ ከቤት ሠራተኞች ጋርና ከቅርብ ጓደኞች የትዳር አጋር ጋር የሚፈጸምን ዝሙትና ዉስልትናን በድራማና መዝናኛ ስም ማሰራጨቱን ተያያዙ። በዚህ አካሄድ በዝምታ ከታየ በሀገራችን ግልጽ የወሲብ ፊልም የሚሰራጭበት ጊዜ ሩቅ አይመስልም።
ሰዎችን ስላለማመዱ ብዙ ሰው በድንዛዜ ተውጦ ምላሹ ዝምታ ሆነ። ተቃውሞ የሚያሰሙ ጥቂቶች ቢኖሩም ሰሚ አጡ። ለዚህ መደበቂና ሽፋኑ መብት፥ነጻነት፥ መዝናኛና ፈጠራ ሆነ። ይባስ ብለው ትውልድን ገዳይ በሆነው መስክ «የፈጠራ ሽልማት» በሚል መድረኮቹን የቀጥታ የሚዲያ ሽፋን የሚሰጡ እና ስፖንሰር የሚያደርጉ ተቋማትም ተቀላቀሏቸው።
ለዝና ዓላማ ልብስን መልበስ
💥💥💥💥💥💥💥💥💥
አንድ ሰው ከኢስላም መርህ ጋር እስካልተቃረነ ድረሰ የሚያምርበትን ዉብ ልብስ መልበስ ችግር የለበትም። ሆኖም ጎልቶ በመታየት፥ ትኩረት በመሳብ ፥የበላይነትን በማሳየት፥ የሰዎችን እይታን በመሳብ ዉድድር ዉስጥ የገቡ አካላት አሉ። እነርሱ ልዩ ሆነው ለመታየት እና ለመታወቅ ሲሉ ሁሌም የተለ የዝና ፍለጋ አለባበስ መልበስን መንገዳቸው ያደርጋሉ።
በዚህ አደገኛ በሆነው አካሄድ ዉስጥ የትኩረጥ ጥማት፥ በሰዎች የመወደስ ፍላጎት፥ ይዩልኝ(ሪያእ)፥ መመጻደቅ፥ከሌሎች በላይ ሆኖ መታየት፥ የቅቡልነት ጉድለት፥ የራስን ስሜት ማምለክ አለበት።
ሰዎች ትኩረታቸውና ፍላጎታቸው በአላህ ዉዴታ ሳይሆን በሰዎች ማረጋገጫና ምስክርነት ላይ ከተንጠለጠለ በቅን ልቦና አላህን ማመለክ አስቸጋሪ ይሆናል። ለዚህም ነው ተግባር በአላህ ዘንድ የሚያስቀጣ ወንጀል የሆነው። ከዐብደላህ ኢብኑ ዑመር(ረዐ) በተላለፈ ዘገባ የአላህ መልዕክተኛ(ሰዐወ) በዚህ ጉዳይ ላይ እንዲህ ብለዋል፦
عن ابن عمر قال: قال رسول الله صلى الله عليه وسلم: من لبس ثوب شهرة في الدنيا، ألبسه الله ثوب مذلة يوم القيامة. رواه أحمد وأبو داود وابن ماجه، والنسائي
«በምድራዊ ዓለም የዝናን ልብስ የለበሰ ሰው፥ አላህ በእለተ ትንሳኤ የዉርደት ልብስን ያለብሰዋል። ከዚያም የእሳት መቀጣጠያ ያደርጋል።»(አቡዳውድ፥ ኢማም አሕመድ፥ ኢብኑ ማጃህ የዘገቡት)
የእውቅናና ዝና ልብስ በመልበስ በገጽታ ብቻ ልቆ ለመታየት መጓጓት እንዲሁም የሕይወት ዓላማንና አቅጣጫን መታወቅ ጋር ማቆራኘት መዘዙ አደገኛ ነው።
የገንዘብና ክብር መሻት ጉጉት መዘዝ
🍎🍎🍎🍎🍎🍎🍎🍎🍎🍎🍎
ኢማም አህመድና ቲርሚዚይ ካዕብ ኢብኑ ማሊክን በማጣቀስ እንደዘገቡት የአላህ መልዕክተኛ(ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል:
«مَا ذِئْبَانِ جَائِعَانِ أُرْسِلَا فِي غَنَمٍ، بِأَفْسَدَ لَهَا مِنْ حِرْصِ الْمَرْءِ عَلَى الْمَالِ وَالشَّرَفِ لِدِينِهِ
‹‹በበግ(ፍየል) መንጋ መሃል የተለቀቁ ሁለት የተራቡ ተኩላዎች በመንጋው ላይ የሚያደርሱት ጥፋት፣ ለገንዘብና ለክብር(ስልጣን) ጉጉ የሆነ ሰው በዲኑ(ሃይማኖቱ) ላይ ከሚያደርሰው ጥፋት የከፋ አይደለም፡፡››
በዚህ ሀዲሳቸው የአላህ መልዕክተኛ(ሰዐወ) ሁለት የተራቡ ተኩላዎች በበግ መንጋ ላይ ከሚያደርሱት ጉዳት ፍጥነትና ስፋት ይልቅ የገንዘብ(المال) እና የክብር(الشرف) ጉጉት በአንድ ግለሰብ ሃይማኖት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ይከፋል። ለክብር መጓጓት የሚለው ከክብር ጋር የተያያዙ ለደረጃ፥ለዝና፥ ለስም፥ለስልጣን፥ለመወደስ ወዘተን መጓጓትን ይጨምራል።
ለገንዘብና ለክብር መጓጓት ሁለቱም የሰዎችን ዉስጣዊ ኒያን(የሀሳብ ዓላማን) ይበክላሉ። መመጻደቅን ያስከትላሉ። ሰዎችን እነርሱን ለማግኘት ሲል ወደ ኃጢአት ይመሩታል። ቅንነትን ያዳክማሉ። መተናነስን በማጥፋት ልታይ ልታይ ማለትን ያስከትላሉ።ሰዎች እነርሱን ለማግኘት ሲሉ የሃይማኖታቸውን ድንበር ጥሰውና እምነታቸውን ተቃርነው ጭምር እንዲጓዙ ይገፋፏቸዋል።
ለገንዘብ ሲሉ ኢስላምን እስከ መሸጥ ድረስ?
💥💥💥🍎🍎🍎💢💢💢🍎🍎💥💥
ሰዎች «የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው» የሚል ፈለግ ተከትለው ገንዘብን በየትኛው መንገድ የማግኘት ዝግጁነት ላይ ከደረሱ እጅግ አደገኛ ደረጃ ላይ ናቸው። አሁን ያለንበት ዘመን ሰዎች ለገንዘብ ሲሉ የማይሆኑት ነገር የሌለበት ደረጃ ደርሰው እያየን ነው። ሰዎች በቂላቂልነትም፥ በጋጠወጥነትም፥ ኢስላምን በመቃረንም፥ የሰዎችን ስም በማጥፋትም ሆነ ግጭት በመፍጠር ገንዘብ መስራት አለብን የሚሉበት ሁኔታ ተፈጥሯል።
በመሰል ሁኔታ ዉስጥ ሰምጦ አልያም በመሰል ሰዎች ተከቦ ያለሰው ሃይማኖቱ ራሱ አሳሰቢ ነው። ሙስሊም ነው ሲባል ሙስሊም የማይሰራውን ስራ ሲሰራ ይታያል። ጠዋት ደህና ሰው ነው ሲባል ማታ ሌላ ሆኖ ይገኛል። እንዴት በሚከተለው ኢስላም(ዲኑ) ላይ እንዲወስን አደረገው ብለን ልንገረም እንችላለን። ነገር ግን ይህን መሰል ሁኔታ ከአቡ ሁረይራ(ረዐ) እንደተላለፈው ዘገባ ነቢያችን(ሰዐወ) እንዲህ በማለት አስጠንቅቀውናል፦
"بادروا بالأعمال، فتناً كقطع الليل المظلم، يصبح الرجل فيها مؤمناً، ويمسي كافراً، أو يمسي مؤمناً ويصبح كافراً، يبيع دينه بعرض من الدنيا" رواه مسلم والترمذي وأحمد
«በመልካም ስራ ላይ ተሽቀዳደሙ። ከፊታችሁ እንደ ቁራጭ ሌሊት አይነት የጨለመ ፈተና አለ። አንድ ሰው አማኝ ሆኖ አንግቶ ከሃዲ ሆኖ ያመሻል፤ ወይም አማኝ ሆኖ ያመሽና ከሃዲ ሆኖ ያነጋል። ዲኑን (እምነቱን) በዱኒያዊ (ዓለማዊ) ጥቅማ ጥቅም ይሸጣል ።» (ሙስሊም፥ቲርሚዚና አሕመድ ዘግበውታል)
«ዋናው የተከታዮቼ መደሰት ነው»
🌄🌄🌄🌄🌅🌅🌅🌅🌅🌅
ሰዎች ከወደዱልኝ፥ ከተከተሉኝም፥ ካደነቁልኝም፤ ዝነኛ ከሆንኩ የአላህ መውደድ ወይም መጥቀም ደንታዬ አይደለም ማለት ነው። በማህበራዊ ሚዲያ ዓለም ሰዎች እይታን እንዳያጡ ሲሉ ተከታዮቻቸውን ማስደሰት፥ የነርሱን ፍላጎትና ጥያቄን መሙላት ቀዳሚ ዓላማቸው ይሆናል። ይህ ለሰዎች ሳይታወቃቸው ከልካይና ፈቃጃቸው አላህና ነቢዩ(ሰዐወ) መሆናቸው ቀርቶ ታዳሚያቸው ይሆናሉ። በሂደትም የታዳሚን ፍላጎት እየተከተሉ ርቀው ይሄዳሉ።
በሂደትም የሕዝብ አስተያየት አምላካቸው፥ እይታን ካስገኘ ጋጠወጥነት ማርኬቲንግ (የገበያ መሳቢያ) መገንዳቸው፥ መታየትና እይታ ማግኘት ማንነታቸው፥ የትኩረት ማዕከል መሆን ደግሞ ዓላማ ይሆናል። ሰዎችን ለማስደሰት ሲሉ ከአላህ ርቀው እርሱን ያስከፉታል። ለጊዜው ከበሬታ ያገኙ ቢመስላቸውም በሂደት ግን ለገንዘብ ሲሉ ምንም ከመሆን ወደ ኋላ የማይሉ እንደሆኑ ሲታወቁ በሰዎች ልብ የነበራቸው ስፍራ ይወርዳል። ይናቃሉ። ይጠላሉ።
በዚህ ጉዳይ ላይ ከዓኢሻ(ረዐ) በተላለፈ ዘገባ የአላህ መልዕክተኛ(ሰዐወ) አንዲህ ይሉናል፦
من التمس رضى الله بسخط الناس رضي الله عنه وأرضى الناس عن، ومن التمس رضا الناس بسخط الله سخط الله عليه وأسخط عليه الناس
«አላህን ለማስደሰት ሲል ሰዎችን ያስቆጣ ሰውን አላህ ይወደዋል፤ ሰዎችም እንዲወዱት ያደርጋል። ሰዎችን ለማስደሰት ሲልም አላህን ያስቆጣን ሰው አላህ ይቆጣበታል። ሰዎችም እንዲጠሉት ያደርገዋል።»(ቲርሚዚይ፥ ኢብኑ ሂባን እንዲሁም አልባኒ የዘገቡት)
«አላህን ፍራ» ሲባል በትዕቢት መወጠር
❌❌❌❌❌❌❌❌❌❌❌❌
ከሃይማኖት ተቃርኖም ጭምር ቢሆን ዝናና ክብር፥ ገንዘብና ዉዳሴ ማግኘት የግለሰቡን ዉስጣዊ ማንነት ነጸብራቅ ነው።የደካማ እምነት ማንነት ማሳያ ነው። ለራስ ያነሰ ዋጋ የመስጠት እና በስሜት የመነዳት ማሳያ ነው።አንዳንዶች ይህን አውነታን ለመሸፋፈን «ልቤ ንጹሕ ነው። ዋናው ልብ ነው» የሚል መደበቂያ ምሽግ እስከ መገንባት ይደርሳሉ። እንደሚባለው ጽኑ እምነት በልቦና ቢኖር በእርግጥ ወደዉጭ ሳይወጣና ተደብቆ አይቀርም ነበር። የነርሱ ግን በግልጽና በሚታይ ሁኔታ ከአላህና መልዕክተኛው(ሰዐወ) ትዕዛዛት ሲቃረኑ ይታያሉ።
ይህ ጉዞ በመጨረሻ ግለሰቡን ከሃይማኖቱ እንዲርቅ በልቡም ከአላህ ይልቅ የዝና ጥማትና የገንዘብ ጉጉት እየነገሰ ይሄዳል። ከዚህ የተነሳም ከሃይማኖቱ የተቃረነ አለባበስ፥ ስነምግባር፥ በዓሊሞችና ዳኢዎች ላይ መሳለቅ፤ እንዲሁም ትኩረት ለመሳብ አወዛጋቢና አነጋጋሪ ነገሮችን ሆነ ብሎ ይተገብራል። ተከታይም ያፈራበታል።
በዚህ ደረጃ ላይ የደረሰ ሰው አላህን እንዲፈራ ቢመከር እንኳ ታዋቂነቱና ከርሱ ጋር ተያይዞ በተፈጠረበት የኩራት ስሜት ከስህተቱ ለመመለስ ሞት ሆኖ ይታየዋል። ከመመለስ ይልቅ «እኔ እኮ ብዙ ተከታይ አለኝ። መብቴም ነው። ስለኔ ምን ያገባችኋል!» በሚል ኩራት ልቡ በትዕቢት ይዋጣል።
ልቢናውን እያደነደነ በዚያው የኃጢአት ጉዞው ይቀጥላል። አላህ ከዚህ ይጠብቀንና ይህ የጥንት መናፍቃን ባህሪም ነበር። አላህ(ሱወ) በቁርኣን ስለነዚህ ዓይነት ሰዎች እንዲህ ይላል፦
وإذا قيل له اتق الله أخذته العزة بالإثم فحسبه جهنم ولبئس المهاد
«ለእርሱ በተባለም ጊዜ፤ትዕቢቱ በኃጢአት(ሥራ) ላይ ትገፋፈዋለች። ገሀነምም በቂው ናት፤(እርሷ) በእርግጥ የከፋች ምንጣፍ ናት።»(ሱረቱ አል-በቀራህ 2፡206)
ስሜት አምላኪ ትውልድ የመፈጠር አደጋ!
⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽⚽
ኢስላም እንደሚያስተምረው በአማኝ ልብ ዉስጥ በብቸኝነት መንገስ ያለበት አላህ ብቻ ነው።ከአላህ ጋር ሌላ ጣኦት ማንገስ አይቻልም። በዝናና እውቀና ጥም የተሞላ ልብ በተመሳሳይ ጊዜ በአላህ ዉዴታ ሊሞላ አይቻለውም። የሰው የተፈጠረለት አንድ እንጂ ሁለት ልብ የለውም።አላህ(ሱወ) እንዲህ ይላል፦
مَا جَعَلَ اللّٰهُ لِرَجُلٍ مِنْ قَلْبَيْنِ فِي جَوْفِهِ
«አላህ ለአንድ ሰው በሆዱ ዉስጥ ሁለትን ልቦችን አላደረገም።»(አል-አሕዛብ፡4)
የሰው ልጅ ባለው አንዲት ልቦና ዉስጥ በዋናነት መንገስ ያለበት አንድ አላህ ብቻ ነው።በአላህ ምትክ ሌላ አካል እንዲነግስ ከተደረገ መዘዙ አደገኛ ነው። የታዋቂነት፥ የዝነኝነትና የላቀ ክብር ፍለጋ ጉዞ በሰዎች ልቦና ዉስጥ ቀስበቀስ በራስ መደነቅ፥ መወደስ መፈለግና ከንቱ ዉዳሴን የማሸት ስሜትን እያለመለሙ ነው።
ተገቢውን ትውልድ የማዳን ሥራ ካልተሰራ ቀጣዩ ትውልድ ከአላህ ይልቅ ዝንባሌውን አምላኩ አድርጎ የሚይዝ፥ ከቁርኣን ይልቅ በዝንባሌው የሚመራ ትውልድ ሊሆን እንደሚችል ምልክቶች እየታዩ ነው። ጊዜ ወስደን ማህበራዊ ሚዲያን ብንመለከት አላህ ምን ይላል? ነቢያችንስ(ሰዐወ) በዚህ ጉዳይ ላይ ምን አሉን? የሚለው ደንታቸው ያልሆነ ሙስሊሞች ጭምር እየተፈጠሩ ነው።
አይናችንን ከገለጥን እኛም ከአላህ ይልቅ ስሜቱን አምላኩ አድርጎ ስሜቱ የሚያዘውን ፍላጎት ለመሙላት የሚጣጣር ሰው ማየት ከባድ አይሆንም። መሰል ሰዎች እንደሚኖር አላህ ባይነግረን ኖሮ ስሜቱን የሚያመልክ ሰው ይኖራል ብሎ መናገር በከበደ ነበር። አላህ(ሱወ) እንዲህ ይለናል፦
أَفَرَأَيْتَ مَنِ اتَّخَذَ إِلَهَهُ هَوَاهُ
«ዝንባሌውን(ስሜቱን) አምላኩ አድርጎ የያዘውን ሰው አየህን!» (ቁርኣን፤ ሱራ አል-ጃሲያህ፡23)
«ሙስሊሞች ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን የለባቸውምን?»
🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉🏉
በአዕምሯችሁ «ታዲዮ ሙስሊሞች ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን የለባቸውም ማለት ነውን?» የሚል ጥያቄ ሊፈጠር ይችላል። መልሱ እያንዳንዱ ሙስሊም ተጽዕኖ ፈጣሪ ሊሆን ይገባል ነው። ግን ተጽዕኖ ራሱ ምንድነው?
ተጽዕኖ ማለት በሌሎች አስተሳሰብ፥ አመለካከት፥ ባህሪ፥ ዉሳኔ፥ ድርጊት ወዘተ ላይ ለውጥ ማምጣት ነው።
ጥያቄው ለውጡ አላህንና መልዕክተኛውን (ሰዐወ) ያስደስታቸዋል ወይንስ ያስቆጣቸዋል? የዝና ጥማት ግን ኢጎ፥ትኩረት መፈለግ፥ ዉጫዊ የሌሎች ምስክርነትና ዉዳሴን መሻት ነው።
ኢስላም ሙስሊሞች በመልካምና ሥነ ምግባርን በተከተለ መንገድ ተጽዕኖ ፈጣሪ እንዲሆኑ ይፈልጋል።ተጽዕኖ ፈጣሪ ሆኖ ለሃይማኖታቸው፥ ለሕዝባቸውና ለሀገራቸው መልካም አስተዋጽዕኖ እንዲያበረክቱ ይሻል።በዚህም በጠቃሚነት ልቀው እንዲገኙም ይፈልጋል።
አላህም ዘንድ በልጠው የሚገኙትና የበለጠ የሚወደዱት በዚህ በመልካም መንገድ ከሌሎች በከተፍተኛ ደረጃ ጠቃሚ ሆነው በመገኘታቸው ነው። አላህ ዘንድ መለኪያው ታዋቂነት ሳይሆን ጠቃሚነት ነው። አላህ በሚወደውና የርሱን መመሪያ ለልተቃረነ መልኩ ከሌሎች የበለጠ የሰው ልጆቸን የበለጠ ሰው አላህ ዘንድ ይበልጥ ተዳጅና ይበልጥ በላጭ ነው።የአላህ መልዕክተኛ (ሰዐወ) እንዲህ ይላሉ፦
خير الناس أنفعهم للناس
«ከሰዎች ሁሉ በላጩ ይበልጥ ለሰዎች ጠቃሚ የሆነው ነው።» (ጠበራኒ በአውሰጥ ላይ የዘገቡትና አልባኒ ሰሂህ ሲሉ ያጸቁት)
«ከሰዎች ሁሉ አላህ ዘንድ ይበልጥ ተወዳጁ ለሰዎች ይበልጥ ጠቃሚ የሆነው ሰው ነው።» (ጠበራኒ)
أحب الناس إلى الله أنفعهم للناس
በተቃራኒ ደግሞ አንዳች ጠቀሜታ በሌለው ጉዳይ ራስን መጥመድ፥ አላህን ማስደሰትን ወይንም ለራስም ሆነ ለሌሎች ጥቅም ማስገኘት በሌለበት መልኩ ዝናና ስም ማግኘትን ኢላማ ያደረገ ለታይታ የሚደረግ ነገር ሁሉ የተወገዘ ነው።በዚህ ዉስጥ የዝናና ዉዳሴ ሱሰኛ መሆን፥ ለመታወቅ ዓላማ መታወቅ፤ ትኩረት ለመሳብ ሲሉ ጋጠወጥ ተግባራትን ማድረግ ሁሉ የተወገዘ ነው።
ችግሩ ምኑ ላይ ነው?
🎁🎁🎁🎁🎁🎁
ስነምግባርን በተላበሰ መልኩ ዓላማው ወገንን ለመጥቀም በሚያበረክቱት እውቀት፥ ክህሎት ወይም በአገልጎት መታወቅ ወንጀል አይደለም። በማህበራዊ ሚዲያ ዓለም ችግሩ የሚያጋሩት ቁም ነገር አል ይዘት(content) ማመንጨት የማይችሉ በሆኑበት ሁኔታ መታወቅ መፈለግ ነው። ያኔ የሚያጋሩት እውቀት፥ ክህሎት፥ አገልግሎት ወይም አንዳች ጠቃሚ ነገር ስለማይኖራቸው ይዘቱ እነርሱ ራሳቸው ይሆናሉ። አካላቸው፥የአናኗር ሁኔታቸው፥ የቤታቸው ገበና፥ እና ፎቶ ግራፋቸው ይሆናል።
የመታየት፥የመታወቅ፥ የዝናና የትኩረት ፍላጎቱ የማህበራዊ ሚደያቸው ይዘቱ እነርሱ ራሳቸው ስለሆኑ ይበልጥ ራሳቸውን እንዲያራቁቱ፥ ይበልጥ ገበናቸው እንዲያጋልጡና ራሳቸውን እንዲያዋርዱ ይገፋፋቸዋ።
ዓላማው ወገንን ማገልገል ሆኖ በሚሰጡት ትምህርት፥ በምክር፥ በእርዳታ፥ ጠቃሚ ነገርን በመፍጠር እና ሌሎችን በቅንነት በመምራት መታወቅ ጥሩ ነገር ነው።ነገር ግን በተደጋጋሚ የራስን መልክ እየለጠፉ የሌሎችን አስተያየት መፈለግ፤ የራስን አካል፥ የህይወት ዘይቤ፥ ስሜቶች፥ የትዳር ሕይወት፥ ወዘተ ወደ መዝናኛ ይዘት መለወጥ፤ ትኩረት ለመሳብ የራስን ምስል ደጋግሞ መለጠፍ፤እውቅናን ሆነ ዝናን በሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ላይ ሳይሆን በራስ መልክ፥ ጸጉር፥ አካል ማድረግ፤ የራሰን ስብዕና የሕዝብ ፍጆታ ማዕክል ማድረግ፤
በሚያበረክቱት ጥቅም ሳይሆን እንደሰው ዝም ብሎ መወደድ፥ መደነቅ ወይም ሰዎች እንዲከተሉት መፈለግ ወዘተ ናቸው።
የማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ እየፈጠረው ያለው አዝማሚያ አደገኛ ነው። በዝምታ ከታየ የቀጣዩ ትውልድ ሁኔታ አስጊ ነው። ተግቶ ሠርቶ ቁም ነገር ላይ መድረስ ፋራነት ተደርጎ ወደ መታየት ጀመረ።ሞራል፥ እምነትንና ሕግን ተቃርኖም ቢሆን ለሁሉም ነገር አቋራጭና ዉጤት የሚገኝበት መንገድን መፈለግ በተዳጊዎች ልቦና እየሰረጸ ነው።
የነቢያችን(ሰዐወ) ትንቢት ተፈጸመ
💢💢💢💢💢💢💢💢💢💢
የማህበራዊ ሚዲያዎቹ አልጎሪዝም ቀመር ትኩረት ሳቢና አነጋጋሪ ነገሮችን ማጉላት ላይ የተመሠረተ ነው። ከዚህ የተነሳ ትኩረት ለመሳብ ደፋር የሆኑት እየጎሉ እውቀትና ትምህርት፥ ምሁራዊ እይታና ስነምግባርን የተከተሉ ይዘቶች የሚገባቸውን ትኩረት ተነፈጉ። ከአዋቂነት ይልቅ ታዋቂነት ሚዛን አነሳ። ከጠቃሚነት ይልቅ ደፋርነት ቦታ አገኘ። በሚዲያዎቹ ላይ ተጽዕኖ ፈጣሪዎቹ ሊቃውንት ሳይሆኑ ደፋር ቂላቂሎቹ በረከቱ።
ትኩረት ለመሳብና ተከታይ ለማብዛት በማይመለከታቸው ና እውቀቱ በሌላቸው ወሳኝ የሀገርና የሕዝብ ጉዳዮች ሁሉ የሚዘባርቁ በረከቱ። ይህ ደግሞ በእውቀት ያልጎለበቱ ተከታዮች አደናገረ። ብዙዎች ታዋቂነትና አዋቂነት አምታታቸው። ለገንዘብና ዝና ሲሉ ሐሰት እየፈበረኩ የሚያሰራጩት ታዋቂ በመሆናቸው ብቻ እንደ እውነተኞች ተቆጠሩ። እውነተኞች ደግሞ ታዋቂ ባለመሆናቸው ብቻ እንደሐሰተኞች ቦታ ተነፈጉ። ዘመኑ አደናጋሪ ሆነ። የሀገር እጣ ፈንታ፥ ወሳኝ በሆኑ የሕዝብ ጉዳዮች ቂላቂሎችና በእውቀታቸው ተራ የሆኑ ሰዎች የሚፈተፍቱበት ሆነ። ይህ ዘመን እንደሚከሰት ነቢያችን(ሰዐወ) የነገሩን ትንቢትም ተፈጽሞ ታየ።
ከአነስ ኢብኑ ማሊክ(ረዐ) እና ከአቡሁረይራ (ረዐ) በተላለፈ ዘገባ የአላህ መልዕክተኛ (ሰዐወ) እንዲህ በማለት ተናግረዋል፦
- سيأتِي على الناسِ سنواتٌ خدّاعاتٌ؛ يُصدَّقُ فيها الكاذِبُ، ويُكذَّبُ فيها الصادِقُ، ويُؤتَمَنُ فيها الخائِنُ، ويخَوَّنُ فيها الأمينُ، وينطِقُ فيها الرُّويْبِضَةُ . قِيلَ : وما الرُّويْبِضةُ ؟ قال : الرجُلُ التّافِهُ يتَكلَّمُ في أمرِ العامةِ
« አሉ። በዚህን ጊዜ «ሩወይቢዳዎች ማን ናቸው?» ተብለው ተጠየቁ። እርሳቸውም «ሩወይቢዳ ማለት ቂላቂል(ተራ) ሰው በአጠቃላይ ሕዝብ ጉዳይ የሚናገር ነው።» በማለት መለሱ።(ኢብኑ ማጃህ፥ አልባኒ በሰሂህ አል-ጃሚዕ ላይ የዘገቡት)
መፍትሄው ምንድነው?
🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴
የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ማህበራዊ ሚዲያን ራቅ አልያም ተጽዕኖ ፈጣሪ አትሁን አይደለም። ዓላማው በግልጽ ተብራርቷል። አንድ ሰው አንድን ሥራ የአላህን ዉዴታ ፈገጎ በመልካም ሁኔታ አሳምሮ ሲሰራ ሰዎች በስራው ሊደሰቱ እና ሊወዱት ይችላሉ። ይህ አንዳች ችግር የለውም። የእርሱ አላማ አላህን ማስደሰት ነበር። አላህም ተደሰተበት። ሰዎች እንዲወዱመም አደረገ።
ስለዚህ ጉዳይ ከአቡዘር አልጊፋሪ(ረዐ) በተላለፈው ዘገባ የአላህ መልዕክተኛ(ሰዐወ) እንዲህ በማለት ተጠየቁ፦
الرجلُ يعملُ العملَ للهِ فيُحبُّهُ الناسُ عليهِ قال ذلك عاجلُ بشرى المؤمنِ
«አንድ ሰው መልካም ተግባርን ለአላህ ብሎ ሠርቶ ሰዎች በሥራው ምክንያት ቢወዱትስ? ተብለው ተጠየቁ። መልዕክተኛውም(ሰዐወ) «ያ ለአማኝ ቀድሞ የመጣለት ብሥራት ነው።» (ሙስሊም፥ ኢብኑ ማጃህ የዘገቡት)
ዝናና ስምን ለማጋበስ ሳይጓጉ ሚናን በአግባቢ መወጣትን ተከትሎ የሚገኝ እውቅና የአላህ ብሥራት ነው።ነገር ግን ሆነ ብሎ ለመታወቅና በሰዎች ለመደስ ብሎ ሥራ መሥራት ደግሞ ይዩልኝ ነው፤ ሆነ ብሎ ዝናና እውቅና ለማግኘት ሲሉ ኃጢአት መሥራት ደግሞ ድርብና እጥፍ ጥፋት ነው። የይሁልኝ በሽታ+ ኃጢአት ማለት ነው።
የዝናና ታዋቂነት ሱስ ደግሞ የቅንነት(ኢክላስ) ብክለት፥ የመልካም ሥራ መበላሽት ነው። ለመታወቅ ሲሉ መጥቀም ግን የይዩልኝ ዝና ፍለጋ ተግባር ነው።ስለሆነም «ሰግጥ ፈምስ» የሚለው ላንተ አይሰራም። አንተ በአላህ የምታምን ሙስሊም ነህ። አንቺም ነቢያችን የምትከተይ ሙስሊም ነሽና። የመጨረሻ ምክሬ የሚከተሉት ናቸው፦
1. ዓላማህ ትኩረት መሳብ ሳይሆን በቅን መንገድ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን ይሁን።
2. ጭብጨባና ሙገሳን የሚያሳድድ ሳይሆን ጠቃሚ ሆነህ መገኘት ላይ ትጋ።
3. ሌሎችን ማገልገል ላይ እንጂ ተከታይ ማፍራትን ኢላማህ አታድርግ።
4. ለዝናና ክብር የምትጋጋጥ ሳትሆን በተጽዕኖው ወደ ቅን መንገድ የሚመራ መሪ ሆነህ በመገኘት ጣር።
5. የአላህን ዉዴታን ማግኘትን እንጂ የሰዎችን ሙገሳና እርካታ ማግኘነን ግብህ አታድርግ።
6. የዝና ጥማትን ለሀገርና ወገን ወደ ሚጠቅም ተጽዕኖ ፈጣሪነት ለውጠው።
7. የመወደስ ረሀብ በዉስጥህ ከተፈጠረ ራስህን ገምግመህ ከዚያ ለመውጣት ትጋ።
8. በእጅህ ያለውን ማህበራዊ ሚዲያን ተጠያቂነት እንዳለብህ በመረዳት አላህንና ነቢዩን(ሰዐወ) በሚያስደስቱ ጉዳዮች ድምጽ ወደ መሆን የላቀ ግልጋሎት ፍላጎት አዙር።
9. ተኩረት የማግኘት ሱስን አላህን ማዕክል ባደረገ ማንነት በመገንባት ተካው።
10. ተጽዕኖ ፈጣሪነትነን አላህን በሚያስደስት፥ መልካም ትውልድን ለመፍጠር በቅንነትና በኃላፊነት ስሜት ተጠቀምበት።
11. የምትከተላቸውን ሰዎች ለይ። የምታጋራቸውን ነገሮች አስተውል። የመልካሞችን እንጂ የእኩያንን ፋናና ተጽዕኖን በማስፋት ላይ ተባባሪ አትሁን።
ዛሬም ሆነ ነገ፥ በዚህ ምድርም ሆነ በቀጣይ ዓለም በሰውም ሆነ በአላህ ፊት የሚያሳፍር ስፍራ ላይ አትገኝ።፥ የሚያስወቅስ ተግባር ተባባሪ አትሁን። የማህበራዊ ሚዲያ ዓለም አንዴ የጻፍካቸው ጽሑፎች፥ የተናገርከውን ንግግሮች እና የሠራኻቸው ቪዲዮዎች ከአጅህ ከወጡ በኋላ ላይመለሱ ተሰራጭተዋል። ሀሳብህን ብትቀይር ወይም መሳሳትህን አምነህ ይቅርታ ብትጠይቅ እንኳ የተሰራጩት እይታ እያገኙ ይቀጥላሉ።
አላህ ዘንድ የምትጠየቀው በአንተ ገጽ ላይ ባሉ ተከታዮች ብቻ አይደለም። ስንቶች ሞተው ጭምር አሻራቸው በማህበዊ ሚዲያ ላይ ለዓመታት ሲዘዋወሩ እያን ነው። ያንተን ፈለግ (አሻራ) ማለት ሀሳብን የተጋሩና የደረሳቸው ሁሉ የሚተገብሩነን ያጠቃልላል።ለነርሱ ተግባራት ሚና ነበረህና የነርሱ መጠየቅ እንዳለ ሆኖ በሚሠሩት ጥፋት ሁሉ አንተም ትጠየቅበታለህ ። ሞተህም ጭምር በመልካም ሥራህ እንደትወደሰው የእኩይ ሥራዎችህ ፋና(አሻራ) ይጻፍብሃል።በዚህ ጉዳይ ጌታችን አላህ(ሱወ) እንዲህ ይላል፦
إِنَّا نَحْنُ نُحْيِي الْمَوْتَىٰ وَنَكْتُبُ مَا قَدَّمُوا وَآثَارَهُمْ ۚ
وَكُلَّ شَيْءٍ أَحْصَيْنَاهُ فِي إِمَامٍ مُّبِينٍ
«እኛ ሙታንን በእርግጥ ሕያው እናደርጋለን። ያስቀደሙትንም ሥራ ፈለጎቻቸውንም እንጽፋለን። ነገሩን ሁሉ ገላጭ መሪ በኾነው መጽሐፍ ዉስጥ አጠቃለልነው።»(ሱራ ያሲን፡ 36፡12)
አላህ በሚወደው መንገድ ተጽዕኖ ፈጣሪ ለመሆን ቆርጠን እንነሳ።አበቃሁ።
Ahmedin Jebel-አሕመዲን ጀበል