12/02/2026
በራስ የመተማመን ጥበብ
ታሪክ የሚሠራው በቃላት ሳይሆን በፅናት ነው! እውነተኛ በራስ መተማመን ደግሞ የሚመነጨው ዓለም በሚሰጥህ ጭብጨባ ሳይሆን፣ አንተ ለራስህ በሰጠኸው "የማንነት ክብር" ነው። ዛሬ በራስ የመተማመንን ምንነትና የማንነትን ክብር የሚመረምሩ፣ ሦስት ድንቅ የታሪክ አውዶችን ይዘንላችሁ ቀርበናል።
የሁለት መቶ ብሩ ኖት ምስጢር
በአንድ ትልቅ አዳራሽ ውስጥ በርካታ ሰዎች ተሰብስበዋል። አንድ ታዋቂ ንግግር አቅራቢ ወደ መድረኩ ወጣና አዲስና ንጹህ የሆነ የሁለት መቶ ብር ኖት ከኪሱ አውጥቶ ወደ ላይ ከፍ በማድረግ አሳያቸው። “ይህንን ገንዘብ የሚፈልግ አለ?” ሲል ጠየቀ። በአዳራሹ የነበሩት ታዳሚዎች በሙሉ ያለምንም ማመንታት እጃቸውን አወጡ። በመቀጠልም ንግግር አቅራቢው ገንዘቡን በእጆቹ መዳፍ ውስጥ አጣጥፎ ጨመደደው። መልሶም “አሁንም የሚፈልገው አለ?” አላቸው። አሁንም የሁሉም እጅ እንደወጣ ነበር።
በመጨረሻም ሰውየው ኖቱን መሬት ላይ ጣለው፤ በጫማውም ረገጠው። ቆሸሸም፤ መልኩም ጠፋ። ንግግር አቅራቢው አሁንም ያንኑ ጥያቄ ደገመው፤ “አሁንም ይህንን የቆሸሸ ገንዘብ የሚፈልግ ሰው አለ?” ታዳሚው አሁንም በአንድ ድምፅ ፍላጎቱን ገለጸ። በዚያን ጊዜ ንግግር አቅራቢው እንዲህ ሲል ታላቁን ትምህርት አስተላለፈ። “ይህ ገንዘብ ቢጨማደድም፣ ቢረገጥም፣ በጭቃ ቢለወስም ዋጋው ግን አልቀነሰም። አሁንም ያው ሁለት መቶ ብር ነው፤ የሚገዛውም ነገር አይቀየርም።”
ይህ ታሪክ የሚያስተምረን ቁምነገር ቢኖር፣ በህይወት ጉዞህ ሰዎች ሊተቹህ፣ ዝቅ ሊያደርጉህ ወይም ሊረግጡህ ቢሞክሩ እንኳ፣ ያንተ እውነተኛ ዋጋ የሚወሰነው በሌሎች ሰዎች አመለካከት ሳይሆን በውስጥህ ባለው ማንነት መሆኑን ነው። ማንም ሰው የማንነትህን ዋጋ እንዲቀንስ አትፍቀድ፤ አንተ በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ ብትሆን ውድ ነህ።
በዶሮዎች መካከል ያደገው ንስር
አንድ የንስር እንቁላል በስህተት ከዶሮዎች ጎጆ ውስጥ ይገባል። ጊዜው ሲደርስ ንስሩ ተፈልፍሎ ከጫጩቶቹ ጋር ማደግ ይጀምራል። ንስሩ ራሱን እንደ ዶሮ ስለቆጠረ፣ እንደ እነርሱ መሬት እየቧጠጠ ትል ይፈልጋል፤ እንደ ዶሮም ክንፉን እያማታ ጥቂት ሴንቲሜትሮችን ብቻ ይበራል። አንድ ቀን ወደ ሰማይ ቀና ሲል አንድ ግርማ ሞገስ ያለው ታላቅ ወፍ በሰማይ ላይ ሲቀዝዝ ተመለከተ። “ያ ግርማው የሚያስፈራ ወፍ ምንድነው?” ሲል ጠየቀ። አብረውት ያሉት ዶሮዎችም “እሱማ የንጉሶች ንጉስ ንስር ነው፤ እኛ ግን ተራ ዶሮዎች ስለሆንን እዚያ ከፍታ ላይ መድረስ አንችልም” አሉት።
ንስሩ ይህንን የዶሮዎች ቃል አምኖ ስለተቀበለ፣ ንስር ሆኖ ተፈጥሮ ሳለ እንደ ዶሮ መኖርን መረጠ። ሰማይን የመቅዘፍ ተፈጥሮአዊ ኃይል እያለው፣ በራሱ ላይ ባጣው እምነት ምክንያት መሬት ላይ እንደቧጠጠ ህይወቱ አለፈ።
ታሪኩ የሚነግረን በራስ መተማመን ማለት ሌሎች ስለ አንተ የሚሉትን ሳይሆን፣ አንተ ስለ ራስህ የምታምንበትን መቀበል መሆኑን ነው። በዙሪያህ ያሉ ሰዎች “አትችልም” ስላሉህ ብቻ ንስርነትህ አይቀየርም፤ ሊቀየር የሚችለው አስተሳሰብህ ብቻ ነው። አንተ ለሰማይ ከፍታ የተፈጠርክ ንስር መሆንህን ካመንክ፣ ክንፍህን ዘርግተህ መብረር ብቻ ነው የሚጠበቅብህ።
በድንጋዩ ውስጥ የታሰረው መልአክ
ታዋቂው የቅርጻ ቅርጽ ባለሞያ ሚካኤል አንጄሎ አንድ ትልቅ ድንጋይ ላይ በትጋት ሲሰራ አንድ ሰው ወደ እርሱ ቀረበ። ሰውየውም በሚካኤል አንጄሎ ድርጊት ግራ ተጋብቶ “ለምንድነው ይህንን ድንጋይ እንዲህ የምትደበድበው?” ሲል ጠየቀው። ጠቢቡ ሚካኤል አንጄሎም ቀና ብሎ እንዲህ ሲል መለሰለት፦ “ድንጋዩን እየደበደብኩ አይደለም፤ በዚህ ድንጋይ ውስጥ የታሰረ መልአክ አለ