05/11/2025
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር የሰብዓዊ አገልግሎቱን በተገቢ ሁኔታ ተደራሽ እንዲያደርግ የህዝብ የአባልነት ምጣኔን እና የገቢ አቅሙን ማሳደግ ይገባል ተባለ።
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ከምባታ ዞን ቅርንጫ ጽ/ቤት '' ለሰብዓዊነት እንኖረለን በሚል መሪ ቃል'' የአባላት ማበራከትና የገቢ ማሳደጊያ ዞናዊ የንቅናቄ መድረክ በዱራሜ ከተማ አካሂዷል።
የከምባታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ልዩ አማካሪ አቶ ደነቀ ደልከሶ ሰብዓዊነትን የተላበሰ የሚረዳዳ ፣ የሚተባበር ፣ ለወገኑ ጉዳት ፈጥኖ የሚደርስና ህዝባዊ መሠረት ያለው ተቋም ለመገንባት በቅንጅት መሥራት እንደሚገባ ገልፀዋል።
ተቋማት በተገቢ ሁኔታ መገንባት የተቋቋሙበትን ዓላማ በአግባቡ እንዲፈጽሙና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲያረጋግጡ በንቅናቄ የሚመሩ ሥራዎች ወደ ተግባር መቀየር አለባቸውም ብለዋል።
ቀይ መስቀል ማህበር እንደ ከምባታ ዞን የህዝብ ተጋላጭነትን በመመከት የህዝብ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን ያብራሩት አቶ ደነቀ ደልከሶ የተቋሙን ሁለንተናዊ አቅም ለማሳደግ ስለ ተቋሙ ተግባራት ለህብረተሰቡ በየደረጃው ግንዛቤ መፍጠርና ማስተባበር ይገባልም ነው ያሉት።
የቀዲዳ ጋሜላ ወረዳ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪና የማህበሩ ቦርድ ሰብሳቢ የተከበሩ ወ/ሮ ውባየሁ በቀለ ቀይ መስቀል ተቋም የሰብዓዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋም ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል።
ማህበሩ በ1985 ዓ/ም ጀምሮ በከምባታ ዞን በማስተባበሪያ ጽ/ቤት ደረጃ ተቋቋሞ አለም አቀፍ የሰብዓዊ አገልግሎት መርሆችን መሠረት ያደረጉ በርካታ የሰብዓዊ ተግባራትን ስፈጽም መቆየቱን የገለፁት የተከበሩ ወ/ሮ ውባየሁ በቀለ በመድኃኒት አቅርቦት፣ በአፈር ጥበቃ፣ በደን ልማት፣ በከተማ ውኃ ዝርጋታ፣ ለአደጋ ተጋላጮች ፈጣን ምላሽ መስጠትና መሰል ተግባራትን እየፈፀመ ይገኛልም ብለዋል።
የተከበሩ ውባየሁ በቀለ አክላውም ተቋሙ ህዝባዊ መሠረት ይዞ ሰብዓዊ አገልግሎቱን በሚገባ ተደራሽ ማድረግ እንዲችል አባላትን በማፊራትና የገቢ አቅሙን ከማጠናከር አኳያ ልዩ ትኩረት በመስጠት በየደረጃው በቅንጅት መሥራትና ውጤታማ እንዲሆን ማስቻል ከሁሉም የሚጠበቅ ኃላፊነት በመሆኑ ጊዜ ልሰጠው አይገባም ነው ያሉት።
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ከምባታ ዞን ቅርንጫ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጥላሁን ወንታሞ ተቋሙ ከአስቸኳይ ጊዜ እርዳታን ተደራሽ ከማድረጉ ባሻገር በተለያዩ የልማት ሥራዎችም ንቁ ተሳትፎ እያደረገ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
የተቋሙ ዋንኛ የገቢ ምንጭ ከአባላት የሚገኝ መዋጮ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጥላሁን ወንታሞ ነባር አባላት የሚከፍሉ መዋጮዎችን ሳይጠባጠብ በአግባቡ መሥራትና ማስተባበር፣ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና በጎ ፈቃደኞች አዳዲስ አባላትን በብዛትና በጥራት ማፍራት፣ የተቋሙን አቅም ለማጠናከር ያግዛልም ብለዋል።
እንደዞን ከ36,130 አባላት ብቻ እና ከ2.5 ሚሊየን የማይበልጥ ገቢ በየዓመቱ መሰብሰቡ ሰብዓዊ አገልግሎቱን በአግባቡ ተደራሽ ለማድረግ ተግዳሮት እየፈጠረ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በተያዘው በጀት ዓመት የአባላት ቁጥሩን ወደ 138,168 በማሳደግ ከ35.9 ሚሊየን በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ልዩ እቅድ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን አቶ ጥላውን ገልፀዋል።
ማህበሩ ሰብዓዊ አገልግሎቱን የበለጠ ተደራሽ እንዲያደርግ ይህ ልዩ እቅድ ስኬታማ እንዲሆን አመራሩና ባለድርሻ አካላት በየደረጃው የተቀናጀ ርብርብ እንዲያደርጉም አቶ ጥላሁን ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
በተዘጋጀው የማህበሩ አባላት እና ገቢ ማሳደጊያ የንቅናቄ ሰነድ ቀርቦ ሰፊ ውይይት የተደረገ ሲሆን አመራሩም ማህበሩ ህዝባዊ መሠረት ይዞ የገቢ አቅሙን አሳድጎ ሰብዓዊ ተግባሩን የበለጠ ተደራሽ በማድረግ ከአቻ ዞኖች ጋር ተወዳዳሪ እንዲሆን የማጠናከር ሥራ ለመስራት የጋራ ተግባቦት ተፈጥሮ መድረኩ ፍፃሜውን አግኝቷል።
በመድረኩ የከምባታ ዞን ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ_ጉባኤ የተከበሩ ወ/ሮ አስካለ ሰሶ፣ የከምባታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ተወካይና የዞኑ ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ መልካሙ ማቴዎስ፣ የከምባታ ዞን መንግስት ዋና ተጠሪ ተወካይ አቶ ምህረቱ መኬቦን ጨምሮ የሁሉም ወረዳ አስተዳዳሪዎች ፣ ከንቲባዎች፣ የፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊዎችና የማህበሩ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝቷል።