02/09/2025
🇪🇹
💪
⚡ የታላቁ የህዳሴ ግድብ ዓመታዊ የኃይል ምርት አቅሙ 15,760 ጊጋ ዋት ነው።
🟢 የታላቁ የህዳሴ ግድብ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኛል ተብሎ ይታመናል።
የታላቁ የህዳሴ ግድብ የመሰረት ድንጋይ ከተቀመጠለት መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም. በአምስት ዓመታት ግንባታውን ለማጠናቀቅ ቢታቀድም ግንባታውን ለማጠናቀቅ 14 ዓመታትን ፈጅቷል።
ግድቡ ሲጠናቀቅ ቀድሞ በ16 ተርባይኖች 6,450 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል ተብሎ የነበረ ቢሆንም አሁን ላይ ኃይል የማመንጨት አቅሙ በ13 ተርባይኖች 5,150 ሜጋ ዋት ነው። ከተባለው 1,300 ሜጋ ዋት እና የ3 ተርባይኖች ቅናሽ ያሳያል።
ለመሆኑ ለምን ይመነጫል በተባለው የኃይል መጠን ላይ ቅናሽ ታየ ?
ቲክቫህ ኢትዮጵያ ታላቁ ህዳሴ ግድብን በጉባ ተገኝቶ በጎበኘበት ወቅት የፕሮጀክቱ ከፍተኛ አመራሮች ለጥያቄው ምላሽ ሲሰጡ የተከታተለ ሲሆን የተለያዩ ባለሞያዎችንም አነጋግሯል።
በዚህም የታላቁ የህዳሴ ህዳሴ ግድብ ኃይል የሚያመነጨው በዋነኛነት በሰበሰበው የውኃ መጠን ሲሆን ይህም ማለት ኃይል የማመንጨት አቅሙ የውኃ ፍሰቱ ላይ መሰረት ያደረገ ነው።
ባለሞያቹ እንደገለጹት የአባይ ወንዝ አማካኝ ዓመታዊ የፍሰት መጠኑ 50 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር (BCM) ነው። ይህም በዓመት ማመንጨት ይችላል ተብሎ የሚጠበቀው ከ15 ሺ እስከ 16 ሺ ጊጋ ዋት በዓመት ነው።
ይህ ማለት አሁን ባሉት 13 ተርባይኖች ማመንጨት የምንችለው ዓመታዊ የኃይል ምርት በተመሳሳይ በ16 ተርባይኖች ከምናመርተው ዓመታዊ የኃይል ምርት ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ ያስረዳሉ።
የታላቁ የህዳሴ ግድብ ዓመታዊ የኃይል ምርት አቅሙ 15,760 ጊጋ ዋት በዓመት ሲሆን ከዚህ የተቀነሰ ነገር እንደሌለ ኃላፊዎቹ ገልጸዋል።
ይሄንን በምሳሌ ሲገልጹም
አንድ ገበሬ በአንድ አንድ ሄክታር መሬት አርሶ 50 ኩንታል እህል እንደሚያገኝ ቢነገረው እና በአንዱ ደግሞ ሁለት ሄክታር አርሶ ተመሳሳይ 50 ኩንታል እህል እንደሚያገኝ ቢነገረው ገበሬው ያለ ጥርጥር የሚመርጠው አንድ ሄክታሩን ማረስ ነው።
ለዚህም በተመሳሳይ የተርባይኑ ቁጥር ከ16 ወደ 13 እንደዚሁም የማመንጨት አቅም ከ6450 ወደ 5150 መቀነሱ በአመታዊ የኢነርጂ ምርት ላይ ለውጥ እንደማያመጣ ነው ባለሞያዎች ያስረዱት።
ከ16 ተርባይን ወደ 13 ተርባይን መቀነሱስ ምን ጥቅም ያስገኛል ?
ይህ ውሳኔ በመወሰኑ ከፍተኛ ወጪን መቀነስ ተችሏል። ከላይ እንደተገለጸው ለሦስት ተርባይኖች ሊወጣ የሚችል በመቶ ሚሊዮን ዶላሮችን ማዳን ተችሏል ተብሏል።
ከዚህም በተጨማሪ ወጪ በመቀነስ ከግድቡ ሊገኝ የሚችለውን ትርፍ የሚጠበቅበትን ጊዜ ማሳጠር ተችሏል።
ህዳሴ ግድብ የወጣበትን ወጪ ከ5 እስከ 7 ዓመት ውስጥ ውስጥ ይሸፍናል ተብሎ ሲጠበቅ፤ ይህም ከግድቡ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኛል የሚል ግምት ተቀምጧል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ 🇪🇹