03/08/2026
ሴቶች በልማት ሕብረት ተደራጅተው ሁለተናዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው ሊሠሩ ይገባል
ሆሳዕና፣ ሐምሌ 27/2018 (ሀድያ ዞን ኮሙኒኬሽን)
የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ሴቶችና ሕፃናት ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት የሴቶች ልማት ሕብረት ስቲሪንግ ኮሚቴ፣ ፆታዊ ጥቃትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች አስወጋጅ ግብረ-ኃይል የ2018 ዓ.ም ዕቅድ አፈጻጸም እና የ2019 ዓ.ም ዕቅድ፣ እንዲሁም የንቅናቄ ተግባራት ግምገማና የቀጣይ አቅጣጫዎች ዙሪያ የውይይት መድረክ አካሂዷል።
"የሴቶች አቅምና ንቁ ተሳትፎ ለዘላቂ ሰላምና ብልጽግና" በሚል መሪ ቃል በተካሄደው በዚህ የውይይት መድረክ ላይ የ2018 ዓ.ም ዕቅድ አፈጻጸም እና የ2019 ዓ.ም ዕቅድ ሰነድ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።
በውይይት መድረኩ ላይ የአመራር አካላት፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የስቲሪንግ ኮሚቴ አባላት፣ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች አስወጋጅ ግብረ-ኃይል አባላት፣ የሴቶችና የወጣት አደረጃጀቶች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።
የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ እና ረዳት የመንግሥት ተጠሪ ወ/ሮ በረከት ታደሰ ባደረጉት ንግግር፤ መድረኩ አረንጓዴ አሻራን ለማሳካት እንደ ሀገር ከ800 ሚሊዮን በላይ የአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ በተካሄደበት በዛሬው ዕለት መካሄዱ ልዩ እንደሚያደርገው ገልጸዋል። አያይዘውም ሴቶች በልማት ሕብረት ተደራጅተው ሁለተናዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ጠቁመዋል።
የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ሴቶችና ሕፃናት ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ስንታየሁ ምህርቱ በበኩላቸው፤ በከተማው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከባለድርሻ አካላት በመቀናጀት የሴቶችን ሁለተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት የተገኘውን አበረታች ውጤት ለማስቀጠል ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል።
የሀዲያ ዞን ሴቶችና ሕፃናት ጉዳዮች መምሪያ ምክትል ኃላፊ ወ/ሮ ሊረሴ ለማ በበኩላቸው፤ ባለድርሻ አካላት በከተማው የሴቶችን ሁለተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚከናወኑ ተግባራት የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆን እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል።
#የሆሳዕና ከተማ ኮሙኒኬሽን