06/06/2026
ምስጋናና ዕውቅና መግለጫ‼
ሠላም ለኢትዮጵያ ጥምረት በ7ኛው አጠቃላይ ሀገራዊ ምርጫ በተበደሉ፣ በተጨቆኑ፣ ከልማት ተገልለው በቀሩ፣ ሰላምን ለሚሹ፣ ፍትህና እኩልነትን ለሚናፍቁ፣ እንዲሁም ማንነታቸውና ሉዓላዊነታቸው በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ለሚገኝ ህዝባችን ድምፅ የሚሆኑ ብቁ፣ ስነ-ምግባራቸው የተመሰገነ፣ በዕውቀት የበለጸጉ፣ በህዝባዊ ፍቅር የተነሱ እና ለህዝባቸው መብት ለመታገል ቁርጠኛ የሆኑ ዕጩዎችን ማቅረቡ የማይካድ እውነታ ነው።
እነዚህ እውነተኛ የህዝብ ልጆች በተወዳደሩባቸው የምርጫ ክልሎች ሁሉ በግልም፣ በቡድንም፣ በጥምረትም ሳይደክሙና ሳይሰለቹ፣ ፀሐይና ዝናብ፣ አቧራና ጭቃ ሳይገድባቸው በትጋት የምርጫ ቅስቀሳቸውን አካሂደዋል።
በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት በተለያዩ አካባቢዎች የደረሱብን የመንቀሳቀስ ገደቦችና የመብት ጥሰቶች በአንድ ጽሑፍ የሚገለጹ አይደሉም። እነዚህ ክስተቶች ለትውልድ ትምህርት እንዲሆኑ በተገቢው መልኩ ተሰንደው ወደፊት ይቀርባሉ።
በዚህ አጋጣሚ ለተለያዩ አካላት ያለንን ክብርና ምስጋና መግለጽ እንወዳለን።
1. ለመላው ህዝባችን
በምርጫ ቅስቀሳ ጉዞዎቻችን ወቅት ላሳያችሁን ፍቅር፣ ክብር፣ አቀባበልና ለደህንነታችን ላደረጋችሁት ጥበቃ በጥምረታችንና በራሴ ስም ከልብ የመነጨ ምስጋና እናቀርባለን።
2. በሀገር ውስጥና በውጭ የምትኖሩ ማህበረሰብ አንቂዎች
ለህዝባችን ግንዛቤ ለመፍጠር፣ በዕጩዎቻችን ላይ የተፈጸሙ ጫናዎችንና በደሎችን በማጋለጥ እና በመቃወም ላደረጋችሁት ቀንና ሌሊት ያልተቋረጠ ህዝባዊ ተጋድሎ ከፍተኛ ምስጋናችንን እንገልጻለን።
3. ለወጣቱ ትውልድ
ከገጠር እስከ ከተማ ድረስ በጽናት ከጎናችን በመቆም፣ የደረሰባችሁን ጫናና ወከባ በመቋቋም ላሳያችሁት ቆራጥነትና ህዝባዊ ተሳትፎ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባችኋል።
4. ለሞተርና ባጃጅ ሹፌሮች
በተለያዩ ጫናዎች፣ ማስፈራሪያዎችና ዛቻዎች መካከል ሆናችሁ ለጥምረቱ ያበረከታችሁት አገልግሎትና የሞራል ድጋፍ በታላቅ ክብር የሚታሰብ ነው። ለዚህም ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን።
5. ለአገው ምሁራን
በሃሳብ ማመንጨት፣ በምክር፣ በትግል አቅጣጫ ማሳየት እና ገንቢ አስተያየቶችን በመስጠት ላደረጋችሁት ውድ አስተዋጽኦ ከፍተኛ አድናቆታችንንና ምስጋናችንን እንገልጻለን።
እንዲሁም በዚህ መግለጫ በስም ሊጠቀሱ ያልቻሉ ሁሉም ወገኖች በመጀመሪያው ነጥብ ስር የተገለጸው ከፍተኛ ምስጋና እንደሚመለከታቸው በአክብሮት እናሳውቃለን።
በመጨረሻም፣ ሠላም ለኢትዮጵያ ጥምረት በ2018 ዓ.ም. ሀገራዊ ምርጫ አቅሙ የፈቀደውን ሁሉ በትጋት ለመፈጸም መሞከሩን እየገለጽን፣ እንደሠራናቸው ጠንካራ ሥራዎች ሁሉ ሊሻሻሉ የሚገባቸው ድክመቶችም እንዳሉብን በግልጽነት ለህዝባችን ማስገንዘብ እንፈልጋለን።
ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. በተካሄደው ሀገራዊ ምርጫ ዙሪያ በህጋዊ ሂደት እየተንቀሳቀስን በመሆናችን፣ የደረስንበትን ውሳኔ በተገቢው ጊዜ ለህዝባችን በይፋ እንደምናሳውቅ በአክብሮት እንገልጻለን።
ሠላም፣ ፍትህ፣ እኩልነትና ዴሞክራሲ ለህዝባችን!
አዲሱ መኮንን (ዶ/ር)
የሠላም ለኢትዮጵያ ጥምረት ምክትል ፕሬዝዳንት
እንጅባራ፣ ኢትዮጵያ
ግንቦት 29 ቀን 2018 ዓ.ም.