14/04/2026
ሃሜትን ማስወገድ ይቻላል?
ሃሜት በሰው ልጆች መካከል ጥላቻን በመዝራት ለዓመታት የዘለቀን ጓደኝነት የሚንድ፣ በግለሰቦች መካከል አለመግባባትን በመፍጠር በጥላቻ መንፈስ እንዲተያዩ መንገድ የሚጠርግ እና በጥቅሉ ማህበረሰቡን ለማይወጣው ማህበራዊ ቀውስ የሚዳርግ ሲሆን ይህ ማህበራዊ በሽታ በባለትዳሮች፣ በቤተሰብ፣ በጎረቤትና በጓደኝነት መካከል ያለውን መልካም ግንኙነት በማሻከር፣ የሰው ልጅ በፍቅር፣ በሰላምና በመተማመን መኖር እንዳይችል እንቅፋት ይሆናል።
ሃሜትን በግልጽ ውይይት በመፍታት ሰላማዊ ኑሮን ማስቀጠል እንደሚቻል ታውቃላችሁ?
ብዙዎች ሃሜትን እንደ ተፈጥሮአዊ ባህሪ ቆጥረው ማስወገድ እንደማይቻል ቢያምኑም፣ የአውራ አምባ ማህበረሰብ መስራች የሆነው ዙምራ ኑሩ ግን ሃሜትን በውይይት በመፍታት ሰላማዊ ኑሮን ማስቀጠል እንደሚቻል በተግባር ያስተምራል።
ዙምራ ኑሩ ይህንን ስር የሰደደ ችግር ለመቅረፍ እንደ ዋነኛ መፍትሄ የሚያስቀምጠው ነጥብ፣ ግልጽነትና እዚያው ባለበት የመነጋገር ባህልን ማዳበር ነው። አንድ ሰው ሲሳሳት ወይም ስህተት ሲሰራ ሲታይ፣ ጉዳዩን ለሌላ ሶስተኛ ወገን ወስዶ በማማት የሰውን ስም ከማጥፋት ይልቅ ለባለቤቱ እዚያው በግልጽ መናገር ይገባል። ቁጣን አስወግዶ በፍቅር እና በፈገግታ “ይህን ነገር እንዴት አየኸው?” ብሎ መጠየቅ፣ ሃሜት ሳይወለድ እዚያው እንዲቀር በማድረግ ትልቅ ሚና ይጫወታል።
ወሬን ከማመላለስ ይልቅ ግለሰቡ ስህተቱን እስኪያስተካክል ድረስ በግልጽ በመመካከር እውነትን ማምጣት የሰው ልጅ ዋነኛ ተግባር ሊሆን ይገባል። የሌላውን ሰው ሀብትና ንብረት እንደምንጠብቀው ሁሉ፣ በሃሜት ምክንያት የሚጠፋውን የሰው ስም እና ስብዕና መጠበቅም የራስን ሀብት እንደመጠበቅ ይቆጠራል።
በአጠቃላይ ሃሜት የሰውን ስም ብቻ ሳይሆን የራስን የህሊና ሰላም እና ክብር የሚያፈርስ ማህበራዊ ቀውስ በመሆኑ፣ እንደ በሽታ ተቆጥሮ ሊታከም ይገባል። ዙምራ ኑሩ እንደሚመክረው፣ እውነትን ፊት ለፊት የመናገርን መድሃኒትነት በመጠቀም የራስንና የሌላውን ሰብዕና መጠበቅ ይቻላል። ይህን የግልጽነትና የውይይት ባህል በተግባር በማዋል፣ በጥላቻና በጥርጣሬ ፋንታ ፍቅርንና መተማመንን የሰፈነበት ማህበረሰብ መገንባት የሁላችንም ድርሻ ነው።
ሙሉ ቪዲዮውን ለመከታተል https://youtu.be/Jb-RwZo5dSg