06/09/2026
የዘመናት እንቅልፍ አብቅቷል፤ መሬት እና ማዕድን ለአገራዊ ብልጽግና
በሀገር ልማት ውስጥ «አራቱ የኢኮኖሚ ሀብቶች» ወይም የምርት ማሳለጫዎች የሚባሉት ለየትኛውም ምርት እና አገልግሎት መፈጠር መሠረት የሆኑት ዋና ዋና ሀብቶች ናቸው። ከእነዚህም ዋነኛው መሬት (Land) ሲሆን በውስጡ ማንኛውንም የተፈጥሮ ሀብት ያጠቃልላል። የሚታረስ መሬት፣ ደኖች፣ የውሃ አካላት እንዲሁም ወርቅና ነዳጅን የመሰሉ ማዕድናት በሙሉ በዚህ ሥር ይመደባሉ።
ይህንን ሀቅ ይዘን የኢትዮጵያን እምቅ የተፈጥሮ ጸጋ ስንመለከት አገራችን ከጥንታዊ ሥልጣኔዋ ጀምሮ በከርሰ ምድሯ ያቀፈችው የማዕድን ሀብት ለዘመናት ይህ ነው የሚባል የኢኮኖሚ እሴት ሳይፈጥር መቆየቱ በእጅጉ ያስቆጫል።
በማዕድን ዘርፉ ለዘመናት የነበረው ጉዞ ውጣ ውረድ የበዛበት ነበር። በንጉሠ ነገሥቱ ዘመን በውጭ ኩባንያዎች ላይ ብቻ የተንጠለጠለ አሠራር፣ በደርግ ዘመን ሀብትን ሙሉ በሙሉ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ያደረገና በጦርነት የተስተጓጎለ ጉዞ እንዲሁም በኢህአዴግ ዘመን ለግል ባለሃብቶች በሩ ቢከፈትም ዘርፉ ለሀገራችን አጠቃላይ ምርት ያለው አስተዋፅዖ ከ0.8 በመቶ በታች ሆኖ የቆየበት ጊዜ ነበር።
ዛሬ ግን የመደመር መንግስት ስትራቴጂያዊ አቅጣጫ ሀብቱ በመሬት ውስጥ ተቀብሮ እንዳይቀር፣ የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ ትብብርን በማጠናከርና የዲጂታል ካዳስተር ሥርዓትን በመዘርጋት ዘርፉን ወደ ዘመናዊ የእሴት ሰንሰለትና የቴክኖሎጂ ሽግግር አድርሶታል።
በዚህ የእመርታ ጉዞ ውስጥ በወርቅ ገበያ ሪፎርም የተገኘው ውጤት የለውጡ ሞተር ሆኗል። ሕገ-ወጥ ንግድን በመቆጣጠርና የግብይት ሥርዓቱን በማሻሻል በተወሰደው ርምጃ ቀድሞ 100 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የነበረው ገቢ በማሳደግ ከ5.5 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማግኘት ተችሏል። በዚህም የኩርሙክ፣ የቱሉ ካፒ፣ የሚድሮክ መተከልና የኤትኖ ማይኒንግ ግዙፍ ፕሮጀክቶችም ይህንን የወርቅ ምርት እመርታ ይበልጥ ወደ ላቀ ምዕራፍ እያሸጋገሩት ይገኛሉ።
ከወጪ ንግድ ባሻገር፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት ፖሊሲው ሌላው ትልቁ የእመርታ ማሳያ ነው። በዓመት ከ300 ሚሊዮን ዶላር በላይ ይወጣበት የነበረው የድንጋይ ከሰል በአርጆ ማቀነባበሪያና በሌሎች አራት አዳዲስ ፋብሪካዎች አማካኝነት ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ምርት መተካት ችሏል።
በሲሚንቶ ኢንዱስትሪውም «ለሚ ናሽናል ሲሚንቶ» ወደ ምርት በመግባት የሀገራችንን የሲሚንቶ ፍላጎት 50 በመቶ ሲሸፍን፣ የዳንጎቴ ሲሚንቶ የማምረት አቅሙን እጥፍ ለማድረግ እየሠራ ነው።
በግንባታና ሴራሚክስ ዘርፍም የባይጂያ እና የግራንድዩር ሴራሚክስ ፋብሪካዎች የተፈጥሮ ጋዝ ኃይልን ጭምር በመጠቀም ኢንዱስትሪውን እያዘመኑት ነው።
የኢኮኖሚ አቅምን በማሳደግ ረገድ የነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ ስትራቴጂካዊ ፕሮጀክቶች የፈጠሩት መነቃቃት እጅግ የጎላ ነው። በሶማሌ ክልል ኦጋዴን ተፋሰስ የሚገኘው የካሉብ የፈሳሽ ነዳጅ ፕሮጀክት በመጀመሪያው ምዕራፍ በዓመት 111 ሚሊዮን ሊትር እያመረተ ሲሆን በቀጣይ እስከ 1.33 ቢሊዮን ሊትር ለማድረስ እየተሠራ ይገኛል።
ከዚህም ጋር የ108 ኪሎ ሜትር የጋዝ ቧንቧ መስመር፣ የ1,000 ሜጋ ዋት የጋዝ ኃይል ማመንጫ እንዲሁም የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያና በዓመት 3 ሚሊዮን ቶን የሚያመርተው የዳንጎቴ ዩሪያ ማዳበሪያ ፕሮጀክቶች የዚህ እመርታ ተጨባጭ ፍሬዎች ናቸው።
በተጨማሪም እንደ ሊቲየምና ታንታለም ያሉ ወሳኝ ማዕድናት እንዲሁም ኤመራልድና ሳፋየርን የመሳሰሉ የጌጣጌጥ ድንጋዮችም ዓለም አቀፍ የገበያ ትኩረትን እየሳቡ ይገኛሉ።
ይህ ሁሉ ስኬት በዘፈቀደ የመጣ ሳይሆን ዘርፉን ከሚደግፉ የተጠናከሩ የመሠረተ ልማት፣ የኃይል አቅርቦትና የአካባቢ ጥበቃ ሪፎርሞች ጋር የተሳሰረ ነው። የዛሬው የእመርታ ጉዞ መነሻ እንጂ መድረሻ አይደለም፤ ማዕድንን ከመሬት ማውጣት ብቻ ሳይሆን ምርትን ወደ ኢንዱስትሪ፣ ኢንዱስትሪን ወደ ብልጽግና የመቀየር ሂደት ነው።
ልክ የዛሬዉ ጳጉሜን 1 አዲስ ተስፋን ሰንቆ ወደ አዲስ ዘመን እንደሚያሻግረን ሁሉ፣ የኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍም የተፈጥሮ ሀብትን በእውቀትና በቴክኖሎጂ አዋህዶ የዜጎችን ሕይወት ወደሚቀይርበት እውነተኛ የእመርታ ምዕራፍ ተሸጋግሯል።