20/08/2026
በሚዛን አማን ከተማ የስማርት ሲቲ የፕላን ጥናት ላይ የተዘጋጀ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው
የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከተማዋን ዘመናዊና ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችላትን የስማርት ሲቲ የፕላን ጥናት ስራ አስመልካች ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል።
በመድረኩ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊና የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማን፣ የከተማዋ ከንቲባ ኢንጂነር ሰለሞን ሌዊን ጨምሮ የዞን፣ የከተማና የቀበሌ አመራሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በመድረኩ ላይ የሚዛን አማን ከተማ ከንቲባ ኢንጂነር ሰለሞን ሌዊ፤ ስማርት ሲቲ በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር ብቻ ሳይሆን የነዋሪዎችን ህይወት ቀላል፣ ጤናማና ቀልጣፋ የሚያደርግ ዘላቂ የልማት ስልት መሆኑን ገልጸዋል።
ከተማዋ እያሳየች የሚገኘውን ፈጣን የኢኮኖሚና ማህበራዊ እድገት ታሳቢ በማድረግ በጋቸብ፣ እድገትና አማን ስትራቴጂካዊ አካባቢዎች ላይ ሰፊና ጥልቅ የስማርት ሲቲ ጥናት መካሄዱን ከንቲባው ጠቁመዋል።
አያይዘውም በመልእክታቸውም፤ የከተማዋን ሀብት በብቃት ለመጠቀም፣ የኃይል ፍጆታን ለመቀነስና ቢሮክራሲን በማቃለል ፈጣን የህዝብ አገልግሎት ለመስጠት የጥናቱን ውጤት ወደ ተግባር መቀየር ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ለእቅዱ ስኬታማነትም የሁሉም ባለድርሻ አካላት ንቁ ተሳትፎና ባለቤትነት አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
በመድረኩ በምን ያምር አማካሪ ድርጅት በኩል የተሰሩ የጥናት ውጤቶችና ዋና ዋና የትኩረት አቅጣጫዎች በድርጅቱ ስራ አስኪያጅ በኢንጂነር ፋናዬ ታደሰና በዘርፉ ባለሙያዎች እየቀረቡ ይገኛሉ።