22/01/2026
የዘንድሮ ነቖ የልጃገረዶች በዓል በዞኑ በሁሉም ወረዳና ከተማ አስተዳደሮች እንደሚከበር የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም መምሪያ ገለጸ።
በዞኑ የተቀዛቀዙና እየጠፉ የነበሩ የጉራጌ በህላዊ እሴቶችን በመታደግና በማልማት በሀገርና በአለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቁ በሚደረገው ጥረት ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበት ተጠቁሟል።
የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ መሰረት አመርጋ እንዳሉት የጉራጌ ማህበረሰብ ከጥንት ጀምሮ ለሴቶች የነበረውን አክብሮትና ነጻነት ማሳያ ነቖ/ረቐ ወይም አስትረ የልጃገረዶች በዓል አንዱ ነው።
ፈረንጆች March 8 mother's day እና Girl's day የሚባሉ ቀናት ባልታሰቡበት ዘመን አስቀድሞ ጉራጌ አስቀድሞ ለልጃገረዶችና ለእናቶች ነጻነት የሰጠ ማህበረሰብ መሆኑን የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱ አመላክተዋል።
ነቖ/ረቐ ለማህበረሰቡ ካለው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው በተጨማሪ ልጃገረዶች ነጻነታቸውን የሚያዉጁበት፣ የሚገናኙበት፣ የሚተያዩበት፣ አብሮነታቸውን የሚጠናከርበትና ለወደፊት ተስፋ የሚሰንቁበት በዓል ነው።
ከዚህም ባለፈ ሴቶች በራስ የመተማመን ብቃታቸው ከፍ የሚልበት፣ ከቤተሰብ ስጦታ የሚያገኙበት፣ የእርስ በእርስ መስተጋብር የሚጎለብትበትና ህብረብሔራዊነት የሚጎለብትበት በዓል በመሆኑ ፋይዳው ከፍተኛ ነው ያሉት።
ልጃገረዶች በየአካባቢያቸው በተለያዩ ስራዎች ሲደክሙ የነበሩትን የሚያርፉበት፣ የሚጨዋወቱበትና የሚዝናኑበት በዓል መሆኑን ያነሱት ኃላፊዋ ይህን እሴት ከጊዜ ወደ ጊዜ በቴክኖሌጂ፣ በአለም አቀፍ የባህል ወረራና በሌሎችም ምክንያቶች እየተቀዛቀዝ መምጣቱን አንስተዋል።
ይህንን ተከትሎ በዞኑ ባለፉት 4 አመታት የልጃገረዶች በዓል ነቆ/ረቐ እንዲያንሰራራ በእዣና ወረዳና በወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሲከበር እንደነበር አንስተው ይህ በዓል ወጥነት ባለው መልኩ በዞኑ በሁሉም መዋቅር እንዲከበር እቅድ በማቀድ ከታችኛው መዋቅር ጋር መግባባት መቻሉን ገልጸዋል።
በዞኑ ዘንድሮ በተለየ መልኩ በሁሉም ወረዳና ከተማ አስተዳደሮች የነቆ/ረቐ የልጃገረዶች በዓል ከጥር 15 ጀምሮ እስከ ጥር 30 ድረስ በትምህርት ተቋማት፣ በተመረጡ ቀበሌዎችና በማዕከል ደረጃ እንደሚከበርም ወይዘሮ መሰረት አስረድተዋል።
በዞኑ በዘንድሮ አመት ከ2 ሺህ በላይ ልጃገረዶች በበዓሉ እንደሚሳተፉ ያነሱት ኃላፊዋ ይህን እሴት ጎልቶ እንዲወጣ ባለሀብቶችና ሌሎችም እገዛ እንዲያደርጉም ጠይቀዋል።
በዞኑ መምሪያው የተቀዛቀዙና የጠፉ የጉራጌ ማህበረሰብ እሴቶችን እንዲያንሰራሩ፣ እንዲለሙና እንዲተዋወቁ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው እነዚህ እሴቶችን ጎልተው እንዲወጡ በቀጣይ በጥናትና ምርምር በማስደገፍ በሀገርና በአለም አቀፍ ደረጃ እንዲተዋወቁ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን እንደሚሰራ አመላክተዋል።
ይህ በዓል ከእምነት ጋር የማያያዝ ዝንባሌዎች እየተስተዋለ መሆኑን አንስተው ይህም የተዛቡ አመለካከቶችን ማስተካከል ላይ ወላጆችና ሌሎችም የበኩላቸውን ድርሻ መውጣት እንዳለባቸው አስረድተዋል።
እንደ ዞኑ ኮሚዩኒኬሽን ዘገባ የባህል ቱሪዝም ጽህፈት ቤቶች ከትምህርት መዋቅር ጋር በመቀናጀት ለልጃገረዶች በታሪካዊ አመጣጡ ዙሪያ ግንዛቤ የመፍጠር፣ ልጃገረዶች የመመልመል፣ ግጥሙ እንዲያጠኑና እንዲለማመዱ ማድረግ እንዳለባቸው አውስተው በተጨማሪም በዓሉ በጀፎረ፣ በጎጆ ቤትና በሌሎችም በማክበር የጉራጌ እሴቶችን ማስተዋወቅ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።