27/10/2025
"...አክሊለ ጽጌ ማርያም ለጊዮርጊስ ቀጸላ መንግሥቱ።" ብለን ስንዘምር ምን ማለታችን ነው?
+++++++++++++
✍️ "ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ እምዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ። ዘተጽሕፈ ብኪ ትእምርተ ስሙ ወተዝካረ ሞቱ። አክሊለ ጽጌ ማርያም ለጊዮርጊስ ቀጸላ መንግሥቱ። አንቲ ኵሎ ታሰግዲ ሎቱ። ወለኪሰ ይሰግድ ውእቲ።"
➾ትርጉም፦ የጊዮርጊስ የስሙ(የሰማዕትነቱ) ምልክትና የሞቱ መታሰቢያ የተጻፈብሽ፤
ባሕርይ ከሚባል ከሚያበራ ዕንቍ ይልቅ የጠራ የክብር ጌጥ የኾንሽለትና በክብር የነገሠብሽ የክብር አክሊል ማርያም ሆይ አንቺ ለጊዮርጊስ ኹሉን ታሰግጂለታለሽ፥ እሱ ግን ለአንቺ ይሰግዳል።
➦"ቀጸላ" በብዙ ቍጥር ቀጸላት ሲባል በቁሙ የራስ ልብስ ጌጥ ሽልማት፤
➻አክሊል ዘውድ፣ ኵፌታ ቆብ መጠምጠሚያ፣ ባርኔጣ ኹሉ ቀጸላ ሊባል ይችላል።
➦ዕጨጌዎችና አበ ምኔቶች በቆባቸው ላይ የሚለብሱት፤ የሚከናነቡት ሻሽ ነጠላ ቀጸላ ይባላል።
➦"በራሳቸውም ላይ ወርቅ እንደሚመስሉ አክሊሎች ነበሩአቸው፥..." ራእ. 9፥7 የሚለውን ግዕዙ "ወዲበ ርእሶሙ ቦሙ ቀጸላ በአምሳለ ወርቅ።" ይላል።
➥"በራሶቹም ላይ ሰባት ዘውዶች ነበሩ፥" ራእ. 12፥3 በግዕዙ መጽሐፍ ቅዱስ "ሰብዐቱ ቀጸላት" ይላል።
➤ቀጸላ ቅጽል ኾኖ በስምና በግብር የሚጨመር ቃል ሲኾን የአካልንና የግብርን አኳኾን ጠባዩን መልኩን የሚገልጥና የሚያስረዳ ነው። ነዊኅ፥ ሠናይ፥ ጸዐዳ እንደማለት ነው።
➔አክሊል የክብር ምልክት፥ የክብር መጨረሻ ነው። የሚቀዳጁትም ትልቅ ማዕርግና ታላቅ ክብር ያላቸው ሰዎች ናቸው።
➾ እግዚአብሔር አሮንን እና ልጆቹን ለክህነት ከለያቸው(ከመረጣቸው) በኋላ መፈጸም የሚገባውን ሥርዐት ለሙሴ ሲነግረው፦ "ወታነብር አክሊለ ዲበ ርእሱ፥ ወታነብር ቀጸላ ዘወርቅ ዲበ አክሊሉ፦ መጠምጠሚያውንም በራሱ ላይ ታደርጋለህ፥ የተቀደሰውንም አክሊል በመጠምጠሚያው ላይ ታኖራለህ።" ዘጸ.29፥6። ይኽም ስለ ሊቀ ካህናቱ ክብር ነው።
➬ስለ ታቦቱ ክብርም፦ "በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በእርሱም ላይ በዙሪያው የወርቅ አክሊል አድርግለት።" ዘጸ.25፥11
➲ አክሊል(ዘውድ) የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው። የብዕለ ሥጋ ፍጻሜው ዘውድ እንደኾነ ኹሉ የብዕለ ነፍስ ፍጻሜ አክሊል(ዘውድ) የምትባል መንግሥተ ሰማያት ናትና። "ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፥ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፥ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም።" 2ኛ ጢሞ. 4፥8።
➔"ወእሁበከ አክሊለ ሕይወት፦ መንግሥተ ሰማያትን አወርሳለሁ።" ሐተታ፦ አክሊል አላት፤ የብዕለ ሥጋ ፍጻሜ ዘውድ እንደ ኾነ የብዕለ ነፍስም ፍጻሜ መንግሥተ ሰማይ ናትና።" እስከሞት ድረስ የታመንህ ሁን የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ።" ራእ.2፥10 እንዲል።
➺እመቤታችን አክሊል ተቀዳጅታ መታየቷ ከፍጥረታት ኹሉ በላይ የኾነውን ክብሯን፥ ማዕረጓን የሚመሰክር ነው። መልዕልተ ፍጡራን መትህተ ፈጣሪ ናትና።
➛በሌላ በኵል ደግሞ የነቢያት የሐዋርያት የጻድቃን የሰማዕታት የሊቃውንት የካህናትና የምእመናን አክሊል እርሷ ናት።
➦ቅዱስ ኤፍሬም "አክሊለ ምክሕነ፥ ወቀዳሚተ መድኃኒት፥ ወመሠረተ ንጽህነ፦ የመመኪያችን ዘውድ፥ የድኅነታችን መጀመሪያ፥ የንጽህናችንም መሠረት"[ውዳሴ ማርያም ዘሠሉስ]
➔"ለራስ ጌጥ ቀጸላ ሁኚኝ የምስጋናሽ ፍጻሜ ወዳለበት እደርስ ዘንድ በክንፈ ሕሊናዬ ወደ አየር ተነጠቅሁ።"[አርጋኖን ዘሠሉስ]
➺"ሰአል ለነ ጊዮርጊስ ሰማዕተ ኢየሱስ ክርስቶስ።"[መጽሐፈ ሰዓታት]
➦"ለሚጋደሉ ኹሉ አክሊላቸው ድንግል ሆይ የመሃይምናን(የምእመናን) የሃይማኖታቸው ቀጸላ የቅዱሳን ሽልማት የነቢያት ልጃች የሐዋርያት እናታቸው የሰማዕታት መመኪያቸው የደናግል የመነኮሳት ጌጣቸው።" [አርጋኖን ዘሐሙስ]
➺"ሰላማዊት ሆይ፥ ለተጣሉት አስታራቂያቸው ለተራቆቱትም የደስታ ልብሳቸው አንቺ ነሽ። ለቀረቡት መዳኛቸው፤ ለራቁትም አክሊላቸው ነሽ።" [የማክሰኞ እንዚራ ስብሐት]
➦"የሰማዕታት የክብር አክሊላቸው የሕጻናት እናታቸው የአብያተ ክርስቲያናት መመኪያ፤ የደናግልና የመነኮሳት የንጽህናቸው መሠረት በሁለት ወገን ድንግል የምትኾኚ ማርያም ሆይ ነይ..."[መዓዛ ቅዳሴ ዘደረሰ በመንፈስ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ]
➦ሐራሴ ወንጌል(የወንጌል ገበሬ) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የተሰሎንቄ ክርስቲያኖችን "የመመኪያችን ክብር" ብሏቸዋል። "ወአክሊለ ምክሕነ፦ የመመኪያችን ክብር ማነው?" "...የትምክህታችን አክሊል ማን ነው?" 1ኛ.ተሰ.2፥19 እንዲል።
➺"የመሐይምናን(የምእመናን) እናታቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስትኾን አባታቸው እግዚአብሔር ነው"[መጽሐፈ ቀሌምንጦስ ዘሮም፤ ምዕራፍ 10፥44]
ምንጭ © ዘማርያም ዘለቀ
https://t.me/Hailemariamderese
ቤተ ዮሴፍ - Bete Yosef