
22/01/2025
ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ መግለጫ!
| የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የከተራ፣የጥምቀትና የቃና ዘገሊላ በዓላት በመላ ሀገራችን ከፍተኛ ቁጥር ባስመዘገበ ምልዓተ ሕዝብ በሰላም ተከብሮ በመዋሉ ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋናዋን ታቀርባለች።
የ2017 ዓ.ም የጥምቀት በዓል በመላ ሀገራችን በድምቀት ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ በማዕከልም ሆነ በአህጉረ ስብከት ደረጃ በሊቃነ ጳጳሳት ተቋቁመው ሥራቸውን በሚገባ የተወጡ የሥራ ኃላፊዎችና የጥምቀት በዓል ዝግጅት አስተባባሪዎች፣
ካህናት፣የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች፣በዓሉ በድምቀት እንዲከበር አደባባዮችን በማስዋብና ሥነሥርዓትን በማስከበር ትልቁን ሚና የተጫወቱ ኦርቶዶክሳዊያን ወጣት ልጆቻችን ምዕመናንና ምዕመናት በሙሉ በዓላቶቻችን ያለአንዳች ችግር በሰላም ተከብረው እንዲውሉ ስላደረጋችሁ ቅድስት ቤተክርስቲያን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርብላችኋለች።
በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ ጃን ሜዳ የተከበሩት ሦስቱ በዓላት በታላቅ ድምቀትና ውበት ተከብረው መዋል እንዲችሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ልዩ ትኩረት በመስጠት የክብር እንግዶች የሚቀመጡበት መድረክ ከነ ሙሉ ግብዓቱ፣የድምጽ ማጉያና መሰል ለበዓል አከባባሩ የሚያስፈልጉትን ሁሉ በከተማ አስተዳደሩ ወጪ በመሸፈን ስላቀረቡልን እንዲሁም ከኮሪደር ልማቱ ጋር በተያያዘ የታቦታት እንቅስቃሴ እንዳይስተጓጎል አስፈላጊውን መመሪያ በመስጠትና አፈጻጸሙን በቅርበት በመከታተል ከልማቱ ጋር የተያያዘ ምንም አይነት መጉላላት እንዳይፈጠር በማድረግ በዓሉ የጋራችን መሆኑን የሚያረጋግጥ ሥራ በመሥራት ላበረከቱት የላቀ አስተዋጽኦ ቤተክርስቲያናችን ምስጋናዋን ታቀርባለች።
በዓላችን ያለምንም የጸጥታ ችግር በሰላም ተከብሮ እንዲውል ለማድረግ የመንግስት የጸጥታ ተቋማት በተለይም የጸጥታና የደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል፣ የአዲስ አበባ ፓሊስ ኮሚሽንና ሌሎች የጸጥታ ተቋማት ያለመታከት ላደረጉት አስተዋጽኦ ቅድስት ቤተክርስቲያን የተሰማትን ደስታ በመግለጽ ምስጋናዋን ታቀርባለች።
በተያያዘ የአራዳ ክፍለ ከተማ አስተዳደር የበዓል አከባበር ሂደቱን በቅርበት በመከታተልና እንቅፋቶች እንዳይፈጠሩ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ በመስራትና የታቦታት ማለፊያ ቦታዎችን በማጽዳት ያበረከተው አስተዋጽኦን ቅድስት ቤተክርስቲያን የምታደንቀውና ምስጋናም የምትቸረው ነው።
በዓላችን በመላ ሀገራችን በልዩ ድምቀትና ውበት ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ በየ ክልሉ የሚገኙ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች መዋቅራቸውን በመጠቀም ታቦታት የሚጓዙበትን ቦታዎች በሚገባ ዝግጁ በማድረግ ለታቦታት ማክበሪያ የሆኑ ይዞታዎችን በመፍቀድና በሰነድ የተረጋገጠ የባለቤትነት መብትን በማጎናጸፍ እንዲሁም በዓሉ በምልዓተ ሕዝብ በሰላም ተከብሮ እንዲውል ላደረጉት ድጋፍና ትብብር ቅድስት ቤተክረስቲያን ምስጋናዋን ታቀርባለች።
በዓለም አቀፍ ደረጃ በማይዳሰስ ቅርስነት የተመዘገበው የጥምቀት በዓል የሀገራችን ኢትዮጵያና የመላው ሕዝባችን በዓል መሆኑን በተግባር በማረጋገጥ ደረጃ በተለይም ሙስሊም ወንድሞቻችን ያሳያችሁት ፍቅርና አንድነትን የሚገልጽ ተግባር በእጅጉ የሚያስመሰግን አንድነትና አብሮነትን የሚያጠናክር በመሆኑ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ላሳያችሁት ፍቅርና ክብር በልዑል እግዚአብሔር ስም ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።
በአጠቃላይ የዘንድሮ የከተራ፣የጥምቀትና የቃና ዘገሊላ በዓላት በመላ አገራችን እጅግ ከፍተኛ ቁጥር የተመዘገበበት ሕዝበ ክርስቲያን በአደባባይ ተገኝቶ በልዩ ውበት በሰላም ያከበራቸው መሆኑን ከመላ አገራችን የደረሰን ሪፖርት የሚያመለክት ሲሆን በዚህ ልክ በዓላቶቻችን በሰላም ተከብረው መዋላቸው ደግሞ በእጅጉ የሚያስደስትና ለአገራችን የቱሪዝም እድገትና የገጽታ ግንባታም ላቅ ያለ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ቤተክርስቲያን ታምናለች።
ስለሆነም በዓላቶቻችን በዚህ መልኩ ተከብረው መዋል እንዲችሉ ለማድረግ አቅማችሁን በማስተባበር ዋጋ ለከፈላችሁ ልጆቻችን በሙሉ እግዚአብሔር አምላክ ዋጋችሁን እንዲከፍላችሁ ቤተክርስቲያን የዘወትር ጸሎቷ መሆኑን ስትገልጽ በልጆቿ መንፈሳዊ ተጋድሎ ከፍተኛ ደስታ የተሰማት መሆኑን በመግለጽ ጭምር ነው።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት
ጥር 12 ቀን 2017 ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ