11/07/2026
የአለታ ፍሬ አልጋ ወራሹ አሰልጣኝ — አምሃ ዘውዱ
*******************//**************
04/11/2018 ዓ.ም
ውልደቱና ዕድገቱ በሲዳማ ክልል አለታ ወንዶ ከተማ ነው። ባልተሳካው የተጫዋችነት ህይወቱ ተስፋ ያልቆረጠ፣ ነገውን አስቦ ለእያንዳንዷ ስኬት ዋጋ የከፈለ ትጉህ ሰራተኛ ነው። ከትምህርቱ ጎን ለጎን ጥሩ እግር ኳስ ተጫዋች መሆን ይሻ የነበረው አምሃ በአንድ ወቅት ያስተናገደው ጉዳት በፈለገው ልክ የሚወደውን እግር ኳስ እንዳይጫወት ማነቆ ሆነበት።
አገግሞ ለመመለስ የተቻለውን ሁሉ ቢያደርግም ነገሮች ግን ያንን ያክል ቀላል አልሆኑም።እንደ ቀልድ ስር የሰደደው ጉዳት እግር ኳስ መጫወትን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያቆም አስገደደው። ገና የሦስት ዓመት ልጅ ሳለ ነበር የትውልድ ቀዬውን ለቆ ወደ ሀዋሳ የመጣው። የአክስቱ ልጆች ጋርም ተቀምጦ ኑሮን አንድ ብሎ የጀመረባት ከተማ ወትሮም የሰው ፍቅርን ታውቅበታለችና አምሃንም በዋዛ አለቀቀችውም።
የወላጅ ናፍቆት ሲበረታ ክረምትን ጠብቆ ወደ አለታ ወንዶ ከተማ ያመራል። ምስጋና ለአሁኑ የሀዋሳ ከተማ አሰልጣኝ ተመስገን ዳና ይሁንና አምሃ ለመጀመሪያ ጊዜ ኳስን ማንከባለል የጀመረው በሸዋ ጨርቃጨርቅ ፕሮጀክት ነበር።ያ ጊዜ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የኤም አር አይ ምርመራ የሚደረግበት ወቅት በመሆኑ የዚህ ፕሮጀክት ታዳጊዎች በአግባቡ ተመዝነው ለተለያዩ የእግርኳስ ታዳጊ ቡድኖች የመጫወት ዕድልን አግኝተዋል።
አምሃ 2006 ላይ ከገጠመው ጉዳት በፊት ከሸዋ ጨርቃጨርቅ ፕሮጀክት በተጨማሪ ያኔ ትልቅ ስም ለገነቡት ለሴንትራል ሆቴል ፣ ለአለታ ወንዶ ተክሌ ሆቴል እና ለሌላኛው የአለታ ወንዶው ልዩ ሆቴል ተጫውቶ በዋንጫ የታጀቡ ዓመታትን አሳልፏል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከ31 ዓመታት ትዕግሥት በኋላ ሱዳንን አሸንፎ ለአፍሪካ ዋንጫ ሲበቃ አምሃ እንደ ኢትዮጵያዊነቱ ደስታውን መቋቋም አቅቶት አልቅሷል።ያ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ቡድን ለእርሱም ቢሆን አዲስ የህይወት መንገድ ፈጥሮለታል። "አሰልጣኝ መሆን ለመጀመሪያ ጊዜ የተመኘሁት ያንን ብ/ቡድን ስመለከት ነው።" የሚለው አምሃ "መምህር የነበሩት ጋሽ ሰውነት ያመጡት ስኬት ህልሜን በእውን አሳይቶኛል።" ይላል።
እርግጥ ነው ይህ በወሬ ብቻ የቀረ ምኞት አይደለም።ቀስ በቀስ እየተተገበረ የሚገኝ መሻት እንጂ።አምሃ ከመጀመሪያም የሰው እጅ አልጠበቀም። ገና የ17 ዓመት ታዳጊ እያለ ነበር ቢ ቤስት የተባለ የታዳጊ ፕሮጀክት በዛ ለጋ ዕድሜው በማቋቋም ሙያውን የተቀላቀለው። ቀን ቀን ተማሪ፣ አመሻሽ ደግሞ የእግር ኳስ አስተማሪ የሆነው አምሃ ከዓመታት ቆይታ በኃላ 2011 ላይ ከሀዋሳ ዩኒቨርስቲ በኮንስትራክሽን ቴክኖሎጂ እና ማኔጅመንት ኢንጅነሪንግ በመጀመሪያ ድግሪ ተመርቋል።
ወዲያውም በሙያው ስራ አግኝቶ ሀገሩን እያገለገለ ጎን ለጎን ደግሞ ብዙ የለፋበትን ቢ ቤስት ቡድኑን ያሰለጥናል። ይህን እያደረገ እንደምንም አንድ ዓመት ሞላው። "ሰዎች ስራህን እንደቀልድ እንዴት ታቆማለህ።"ይሉኛል።"እኔ ግን ልክ እንደ ስራው ሁሉ ኳሱን ማሰልጠን ማቆም አልችልም።"የሚለው አምሃ የተመረቀበትን ሙያ ሙሉ ለሙሉ ትቶ የሙሉ ጊዜ አሰልጣኝ ሆነ።
የማይታመን ተግባር ቢመስልም እርሱ ለእግር ኳሱ ተሰጥቷልና ሳያቅማማ አድርጎታል። ያመናት እግርኳስ አልካደችውም።ቀስ በቀስ ለተሻለ ማዕረግ አበቃችው እንጂ።ሀዋሳ ከተማን በሲዳማ ልዩ ልዩ ሻምፒዮና አሸናፊ ያደረገው አምሃ፣ የሲዳማ ከ17 ዓመት በታች ቡድንን ደግሞ 2016 ላይ በሀገር አቀፍ ውድድር ለፍፃሜ አብቅቶ በኢትዮ ኤሌክትሪክ በመለያ ምት ተሸንፎ 2ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል።
ይህ ሰው ከ2 ዓመት በፊት 2014 ላይ የተወለደባትን ከተማ አለታ ወንዶን በአሰልጣኝነት ይዞ በኢትዮጵያ ክልል ክለቦች ሻምፒዮና ውጤታማ በማድረግ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ሊግ አብቅቷል። ይህም በአካባቢው የጀግና ያክል ተቆጥሮ እንዲወደድ አድርጎታል። ከአምሃ አፍ ሁሌም የማይጠፋ አንድ አሰልጣኝ አለ። "እሱ ሙያዬን እንዳሻሽልና ሙሉነት እንዲሰማኝ ዋጋ ከፍሎልኛል።"ይላል።ይህ የተባለው ሰው የወቅቱ የመቻል እግርኳስ ክለብ አሰልጣኝ የሆነው ሙሉጌታ ምህረት ነው።
የሀዋሳው ፍሬ ሙሉጌታ ምህረት አምሃ ለፈለገው ነገር ሁሉ ቅርቡ ነበር።አንዳንዴማ የራሱን ቡድን እንዲያሰለጥንና ሙያውን እንዲያሳድግ ያደርገው ነበር። አንዳንዴ ደግሞ ከአምሃ ቡድን ጋር የራሱን ቡድን የወዳጅነት በማጫወት ለታዳጊዎች ልምዱን ያካፍላል። "ለዛሬ መድረሴ አንድም በእርሱ ነው።" ሲል አምሃ ተናግሯል።
2017 ላይ የሲዳማ ከ20 ዓመት በታች ቡድን ዋና አሰልጣኝ ተደርጎ የተሾመው አምሃ ለታመነበት ቦታ የሚመጥን ሰው መሆኑን ለማሳየት ጊዜ አልወሰደበትም። አሰላና ቡራዩ ላይ በነበረው የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ፕሪሚየር ሊግ ሲዳማ ቡናን እየመራ ምድቡን በአንደኝነት አጠናቀቀ።
ሀዋሳ ላይ በነበረው የማጠቃለያ ውድድር ደግሞ በፍፃሜው አዳማ ከተማን 2 ለ 1 በማሸነፍ ሲዳማ ቡናን ለዋንጫ አበቃው። በዓመቱ ዳግም ቡድኑን ለዋንጫ ያበቃው አምሃ ታዳጊ ቡድኑ በመድረኩ ወጥነት ያለውና ኢ-ተገማች እንዲሆን በማድረግ ስኬትን በስኬት ላይ ደርቧል።
የዲ ላይሰንስ ፍቃድ ያለው አምሃ አንድ አሰልጣኝ የሲ ላይሰንስ ፍቃድ እንዲኖረው ክለብ መያዝ አለበት የሚለው የፌዴሬሽኑን ህግ ጠብቆ ከወራት በኋላ ደግሞ ደረጃውን ወደ ሲ ላይሰንስ ያሳድጋል። ለዚህ ዕድገት ሲዳማ ቡና መንገድ ጠርጎለታል።
አምሃ በ2 ዓመት ውስጥ 12 ተጫዋቾችን ለሊጉ ክለቦች አብቅቷል። ዛሬ በሲዳማ ቡና ዋናው ቡድን ውስጥ የሚገኙት አስቻለው ሙሴ ፣ ፍቃዱ ማጃ ፣ አላዛር እያሱና እያሱ ሮንዴ የእርሱ ሙያ ያረፈባቸው ታዳጊዎች ናቸው። በኢትዮጵያ ቡና የሚገኘው ናትናኤል ፍሬው እና ለሀዋሳ ከተማ የሚጫወተው ናትናኤል ሸገሙ እንዲሁ ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው።
አምሃ ይናገራል "ህልሜ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን በአሰልጣኝነት እየመራሁ ለዓለም ዋንጫ ማብቃት ነው" ይላል። መማር የማይሰለቸው፣ ለማወቅ የሚጥርና የተማረውን ለመተግበር እንቅልፍ የሚያጣ ሰው መሆኑ ህልሙ ሊሳካ በትክክለኛው መንገድ ላይ ለመገኘቱ ያሳለፈው ህይወት ምስክር ይመስላል።
በአብርሃም ተስፋዬ
#አምሃ
ከኢቲቪ መዝናኛ የፌስቡክ ገፅ የተወሰደ