09/04/2026
በአለታ ወንዶ ከተማ የነዳጅ ምዝበራና የባለሥልጣናት እጅ ህዝቡን በምሬት ላይ ጥሏል!
================================
AWP ሚያዝያ 01 2018፣ዓ.ም
ሐዋሳ
በአለታ ወንዶ ከተማ የሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ለህዝብ አገልግሎት መስጠት ሲገባቸው፣ ከከተማው ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመመሳጠር ለህገ-ወጥ ንግድና ለምዝበራ መጋለጣቸውን አፊኒ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ካሰባሰበው መረጃ ለማወቅ ተችሏል።
እንደ መረጃ ምንጮቻችን ገለጻ፣ መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም ሌሊት በከተማዋ በሚገኘው ቶታል ማደያ (ዘርዓብሩክ ሆቴል አጠገብ) እና ታች ሼል ማደያ አስገራሚ ድርጊት ተፈጽሟል።
የቀኑን ውክቢያ ተቋቁመው፣ ለሊቱን በሙሉ በሰልፍ ሲጠበቁ የነበሩ አሽከርካሪዎች ባሉበት ሁኔታ፣ በ"አይሱዙ" (Isuzu) ተሽከርካሪዎች በበርሜል የተሞላ ነዳጅ ጭነው ከማደያዎቹ ወጥተዋል።
ይህ ድርጊት የተፈጸመው አሽከርካሪዎች ለነዳጅ እጥረት ተዳርገው ስራ አቁመው ባለበትና ህዝቡ ለትራንስፖርት ችግር ተጋልጦ በሚገኝበት ወቅት መሆኑ ምሬቱን አክሮታል።
ከከተማ አስተዳደሩ ውስጥ የሚገኙ የመረጃ ምንጮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ለአፊኒ ሚዲያ እንደገለጹት፣ ይህ ህገ-ወጥ ተግባር የሚከናወነው በከተማዋ አመራር አካላት ቀጥተኛ ድጋፍና መሪነት ነው። የማደያ ባለቤቶችና የአስተዳደር አካላት በፈጠሩት የጥቅም ትስስር፣ ነዳጅ ለህዝብ ከመቅረብ ይልቅ በጥቁር ገበያ እንዲሸጥ እየተደረገ ይገኛል።
"አመራሩ ህግ ከማስከበር ይልቅ ከባለሀብቶች ጋር በመመሳጠር የድሃውን ህዝብ እንጀራ እየነጠቀ ነው" ሲሉ አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የከተማዋ ነዋሪ በቁጭት ተናግረዋል።
የመረጃ ምንጮቻችን ጨምረው እንደሚያመለክቱት፣ እነዚህ አካላት አሁን ላይ በመካከለኛው ምስራቅ የተከሰተውን የጂኦ-ፖለቲካ ውጥረትና የነዳጅ ዋጋ መናር እንደ መልካም አጋጣሚ ተጠቅመውበታል። "ነዳጅ ከምንጩ ጠፍቷል" የሚል የሀሰት ሰበብ በማቅረብ፣ ያለውን ክምችት ለግል ጥቅማቸውና ለህገ-ወጥ ንግድ እያዋሉት መሆኑን ምንጮቻችን አረጋግጠዋል።
ይህ ስር የሰደደ የሙስና ሰንሰለት በአለታ ወንዶ ከተማ ነዋሪዎችና አሽከርካሪዎች ላይ ከፍተኛ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫና እየፈጠረ ይገኛል።
የሚመለከተው የክልልና የፌዴራል አካል በከተማዋ አመራሮችና በማደያ ባለቤቶች ላይ ጥብቅ ቁጥጥርና ምርመራ እንዲያደርግ ህብረተሰቡ ጥሪውን እያቀረበ ነው።
ዘገባው የአፊኒ ሚዲያና ኮሚዩንኬሽን ነው።