27/08/2026
ኮሪደር ዳግም እንዲወልዳት ምመኛት ወልቂጤ
ወልቂጤ ከተማ የእንግዳ ተቀባይነቷን ያህል የመዝናኛና የመናፈሻ ቦታዎች እጥረት እንደ ውሃ ጥም ያንገበገበው ሕዝብ መኖሪያ እንደሆነች ሀቅ ነው።
አመሻሽ ላይ ቤተሰብ አብሮ ወጥቶ የሚተነፍስበት፣ ሕፃናት የሚፈነጩበት፣ ወጣቶችም የዕለቱን ድካም የሚያወጡበት ንጹሕና ውብ የሕዝብ መዝናኛ ማጣት የከተማዋን ነዋሪዎች ረጅም ዘመናት ሲያስቆዝም የኖረ እውነት ነው።
እኔ አዲስ አበባ ሃዋሳ ቡታጀራ በስራ በተለያየ ምክንያት በመዝናኛ ስፍራዎች ሰላም አግኝቼ እመለሳለሁ። የእኔ ሱስ ሻይ ወይም ውሃ አዝዤ መንገድ ዳር አለዚያም ፀጥ ያለ ውብ ስፍራ ላይ ማሳለፍ ነው።
አሁን እንደሚታወቀው በሃገራችን በተለያዩ ከተሞች እውን እየሆነ ያለው የኮሪደር ልማት ብስራት፣ ለወልቂጤም አዲስ ተስፋና ትንሳኤ ይዞ ይመጣ ብዬ ሁልጊዜ በጉጉት እጠብቃለሁ። በተለይ በሰላም በር እና በስታደየም መካከል እንዲሁም ጉብሬ አደባባይ ባለው ቦታ ከታች ያሰፈርኩት መዝናኛ ቦታ ይናፍቀኛል።
የወልቂጤ ነዋሪዎች ምኞት
የኮሪደር ልማት ከተማን የማስዋብና የትራፊክ ፍሰትን የማስተካከል ሥራ ብቻ አይደለም፤ ለሕዝቡ የመንፈስ እርካታን የሚሰጡ አረንጓዴ ስፍራዎችን፣ የእግር መንገድ ኮሪደሮችንና ዘመናዊ መዝናኛዎችን የሚያስገኙ የሕይወት ትሩፋቶች ናቸው።
የወልቂጤ ሕዝብም ይኸው የኮሪደር ልማት በከተማቸው በስፋትና በፍጥነት ተተግብሮ ሕፃናትና ወጣቶች በአስተማማኝ ቦታ የሚጫወቱበትን፣አዛውንቶች በአረንጓዴ ልምላሜ መካከል የሚዝናኑበትን ስፍራ ይሻሉ።
የከተማዋን ድምቀትና ውበት ከፍ የሚያደርጉ ዘመናዊ የሕዝብ መናፈሻዎችን በአይኑ ለማየት በታላቅ ጉጉት ይጠብቃል።
የኔ ምኞት ብቻ አይመስለኝም።
ወልቂጤ የላቧን ያህል እንድታብብ፣ ስሟንና ታሪኳን የሚመጥን የኮሪደር ልማት ትሩፋት ባለቤት እንድትሆንና የሕዝቧም የመዝናኛ ጥም እንዲቆርጥ ጥሪው ይደርሳችሁ።
ከተማውን አቧራውን አራግፋ ለመድመቅ ምታደርገው ጥረት የሚደነቅ ብሎም የሚበረታታ ነው።
የወልቂጤ የኮሪደር ልማት እውን ሆኖ፣ ውቧ ከተማችን በአዲስ ገጽታ ፈክታ የምናይበት ቀን ቅርብ ይሁን!