26/08/2026
ዜና: የአውሮፓ ህብረት እና አጋሮቹ በሰሜን #ኢትዮጵያ አዲስ ግጭት እንዳይቀስቀስ አስጠነቀቁ
በኢትዮጵያና በአፍሪካ ህብረት የሚገኙ የአውሮፓ ህብረት ልዑካን፣ የአባል ሀገራት ኢምባሲዎች እንዲሁም የካናዳ፣ #ኖርዌይ እና #እንግሊዝ ኤምባሲዎች በጋራ ባወጡት መግለጫ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ሁኔታ በአንክሮ እየተከታተሉት መሆኑን አስታውቀዋል። አምባሳደሮች እና የልዑካን ቡድኖች ሁሉም ወገኖች የፕሪቶርያ የዘላቂ ተኩስ ማቆም ስምምነቱን በቅንነት እና በግልጽነት እንዲተገብሩ ጥሪ አቅርበዋል።
የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት እና የአፍሪካ ህብረት ከፍተኛ ተወካይ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ በአዲስ አበባ እና በመቐለ ያደረጉትን ውይይት ያደነቀው የመግለጫው አካል፣ በድርቅ እና ከፍተኛ ሰብአዊ ቀውስ በተጎዳው የትግራይ ክልል እንደገና ወታደራዊ ግጭት ቢቀስቀስ በህዝቡ ላይ የከፋ ውድመት እንደሚያስከትል አሳስቧል።
በተመሳሳይ #አሜሪካ በበኩሏ የኦባሳንጆን ጉብኝት የደገፈች ሲሆን፣ በሰሜን ኢትዮጵያ እንደገና ግጭት ሊቀስቀስ ይችላል የሚለው ስጋት እየጨመረ መምጣቱን ገልጻለች። የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ እና የአፍሪካ ህብረት የአሜሪካ ሚሲዮን ጉዳይ ፈጻሚ ዋልተር ፖርክስ ፣ #ኦባሳንጆ የአፍሪካ ህብረት መመሪያቸውን ለመወጣት የሚያደርጉት ጥረት ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ በቅርቡ ወደ #ትግራይ እንደሚመለሱ ተስፋ አድርገዋል። የሁለቱ ሀገራት የዲፕሎማሲ ተወካዮች መሪዎች ሚሊዮኖችን እየጎዳ ያለውን ድርቅ ቅድሚያ እንዲሰጡ እና ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ አሳስበዋል።
በሌላ በኩል የህወሓት-መራሹ የትግራይ ክልል አስተዳደር ባለስልጣናት ኦባሳንጆ ነሐሴ 18 ቀን በመቐለ ያደረጉት ጉብኝት ያለ ቅድመ ቀጠሮ የተደረገ መሆኑን ገልጸው፣ ከፌደራል መንግስት በኩል ለሰላምና ደህንነት ወሳኝ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የተገኘ አዲስ ሃሳብም ሆነ ተጨባጭ ውጤት አለመኖሩን አስታውቀዋል። ክልሉ በሰኔ ወር ለድርድር መነሻ ይሆናሉ ያላቸውን አምስት ነጥቦች ያቀረበ ሲሆን፣ እነሱም “ኢኮኖሚያዊ እገዳውን እና ከበባውን ማንሳት፣ ወታደራዊ ከበባውን ማቆም እና የደህንነት ስጋቶችን መቀነስ፣ የተያዙ ቦታዎችን መመለስ፣ ተፈናቃዮችን ወደ ቀደመ ቀያቸው መመለስ እንዲሁም የህወሓትን ህጋዊ እና ፖለቲካዊ ህልውና ማረጋገጥ” ናቸው።
ኦባሳንጆ በሰኔ ወር ውይይት አድርገው ከተመለሱ በኋላ በሁለት ሳምንት ውስጥ እመለሳለሁ ቢሉም ተከታታይ እርምጃ አለመወሰዱን ያስታወቀው ህወሓት-መራሹ አስተዳደር፣ ባለፉት አራት ዓመታት የተደጋገሙ ያልተፈጸሙ ቃል ኪዳኖችን የመድገም ፍላጎት እንደሌለው ገልጿል። ሆኖም ሂደቱ በዋና ዋና ዓለም አቀፍ አጋሮች የሚደገፍ ከሆነ በጊዜ የተገደበ ድርድር ለማድረግ አሁንም ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።