25/08/2026
የዕለቱ አጫጭር ዜናዎች……..ነሐሴ 20/2018
ኦባሳንጆ በትግራይ …….
የአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ የሰላም ልዑክ ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ በትናንትናው ዕለት በትግራይ ዋና ከተማ መቐለ ተገኝተው ከክልሉ ባለስልጣናት ጋር ተወያዩ፡፡ የትግራይ ክልል ባለስልጣናት ዛሬ ባወጡት መግለጫ፣ የኦሊሴጎን ኦባሳንጆን ጉብኝት አረጋግጠው፣ ከክልሉ ፕረዝደንት ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ጋራ መምከራቸውን ገልፀዋል፡፡ ይሁንና ጉብኝቱ የታቀደና ቀድሞ በተያዘ መርሀግብር መሰረት የተከናወነ አልነበረም፣ ድንገተኛ ነው ብለዋል፡፡ በሰላም ልዑኩ ጉብኝት ደስተኞች እንዳልሆኑ የገለፁት ባለስልጣናቱ፣ ከዚህ ቀደም ሰኔ ወር በመቐለ ተገናኝተው በተነጋገሩባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ለውጥ እንዳልመጣ ገልፀዋል፡፡ ኦባሳንጆ ግን በጉዳዩ ዙሪያ ከፌደራሉ መንግስት ጋር ተነጋግረው በሁለት ሳምንት ውስጥ ወደ መቐለ እንደሚመለሱ ቃል ገብተዋል፡፡
በትግራይ የድሮን ጥቃት ቀጥሏል…..
በትግራይ ክልል በፌደራሉ መንግስት የሚፈፀመው የድሮን ጥቃት መቀጠሉን የክልሉ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ በትናንትናው ዕለት በሰሜን ምዕራብ ትግራይ እንዳባጉና አካባቢ እና በደቡብ ትግራይ ራያ አካባቢ ሁለት የድሮን ጥቃቶች ተፈፅመዋል፡፡ በጥቃቶቹ የደረሰ ጉዳት አይነትና መጠን በትክክል ባይገልፅም፣ ጉዳት መድረሱን ግን ሚዲያዎቹ አመልክተዋል፡፡ ትናንት እኩለ ሌሊት ላይ ደግሞ በምስራቅ ትግራይ አፅቢ አካባቢ፣ ተመሳሳይ የድሮን ጥቃት እንደተፈፀመ ተገልፆዋል፡፡ በተከታታይ እየተፈፀሙ ስላሉት የድሮን ጥቃቶች እስካሁን ከፌደራሉ መንግስት በኩል የተሰጠ አስተያየት የለም፡፡
የ 12ኛ ክፍል ተማሪዎች ውጤታቸውን ከዛሬ 1፡00 ጀምሮ ማየት ይችላሉ…
የ 12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ይፋ መሆንን ተከትሎ ተማሪዎች ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት ጀምረው ውጤታቸው ማየት እንደሚችሉ የትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት አስታወቀ፡፡ የ2018 ትምህርት ዘመን የኢትዮጵያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ማጠናቀቂያ ፈተና ውጤት የሚገለጽባቸው አድራሻዎችም በተቋሙ ይፋ ሆነዋል፡፡ ውጤታቸውን ለማየትም የሚከተሉትን አማራጭ ማስፈንጠሪያዎችን መጠቀም እንደሚችሉ ተገልፆዋል፡፡
ውጤት የሚገለጽባቸው ማስፈንጠሪያዎች፡-
በድረ ገጽ ፡ https://result.eaes.et
ቴሌግራም፡ https://result.eaes.et/telegram
አጭር የጽሑፍ መልዕክት፡ https://result.eaes.et/sms
በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ አባላት ተገደሉ…
በደቡብ ሱዳን ጆንገሌ ግዛት በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሁለት የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ አባላት መገደላቸው ተሰማ፡፡ የሰላም ማስከበር አባላቱ ተሽከርካሪ ላይ የታጠቁ ሀይሎች በዛሬው ዕለት በፈጸሙት ጥቃት ሁለት አባላት ሲገደሉ ሰባት አባላት ቆስለዋል ተብሏል፡፡ ከቆሰሉት መካከልም 3 ኢትዮጵያውያን ሰላም አስከባሪ አባላት፣ 2 የደቡብ ሱዳን ብሔራዊ ፖሊስ አባላትና 2 ድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች ይገኙበታል ተብሏል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶንዮ ጉተሬዝ ጥቃቱን አውግዘዋል፡፡
ሱዳን ከኢትዮጵያ የተነሳን ድሮን መታሁ አለች….
የሱዳን መንግሥት፣ ከኢትዮጵያ የተነሳ ያለውን ድሮን በትናንትናው ዕለት መጥቶ መጣሉን አስታወቀ፡፡ ድሮኑን የመታው ብሉ ናይል ግዛት ውስጥ እንደሆነም ጠቅሶዋል፡፡ ድሮኑ ተመትቶ የወደቀው የድንበር ከተማ በሆነችው ኩርሙክ አካባቢ መኾኑንም የሱዳን መከላከያ ሚንስቴር ተናግሯል፡፡