
27/07/2025
የተወለደው በምድረ አንጾኪያ ሶርያ በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው፡፡
በቤተ ክርስቲያን የሰማዕታት አለቅነት ከተሰጣቸው ሰማዕታት አንዱ ነው፡፡ አባቱ ዮሐንስ በትውልድ ግብጻዊ የሆነ ክርስቲያን ነው፡፡ እናቱ ግን አስቸጋሪና ጣዖት አምላኪ ሶርያዊት ነበረች፡፡
ባልና ሚስት አብረው ሲኖሩ ሚስት ባሏ ክርስቲያን መሆኑን አታውቅም ነበር፡፡ ቴዎድሮስ የእግዚአብሔር ስጦታ ማለት ነው፣ በተወለደ ጊዜ ግን ጠብ ተነሳ፡፡ እሱ ክርስትና ለማስነሳት፣ ሚስት ደግሞ ወደ ጣዖት ቤት ለመውሰድ ተጋጩ፡፡ ሚስት ወገኖቿ ባለስልጣኖች ናቸውና ልጁን ቀምታ ባሏን ዮሐንስን ወደ ግብፅ አሳደደችው፡፡ ዮሐንስ በስደት ባለበት ሃገር ስለ ልጁ ፈጽሞ ይጸልይ ሲያለቅስ እግዚአብሔር ልመናውን ሰማ፡፡ ማር ቴዎድሮስ ወጣት በሆነ ጊዜ ማንም ሳይጠራው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔዶ ተማረ፣ ተጠመቀ፡፡ በየዕለቱም ለጾምና ጸሎት፣ ለምጽዋት ጋር ያበዛ ድንግልናውንም ለመጠበቅ ይተጋ ነበር፡፡
ገና በ20 ዓመቱ ኃያልና ብርቱ፣ በጸባዩም የሚወደድ ቅን፣ መልከ መልካምም ሆነ፡፡ ከተወዳጅነቱ የተነሳም ነገሥታቱም የአንጾኪያ የጦር ሠራዊት አለቃ አድርገው ሾሙት፡፡ አሁንም ድረስ "የሠራዊት አለቃ" በሚለው ስያሜ የሚጠራው ማር ቅዱስ ቴዎድሮስ በተሳተፈባቸው ጦርነቶች ሁሉ ተሸንፎ አያውቅም፡፡ ይልቁኑ ጠላትን በመማረክ ነበር የሚታወቀው፡፡ በአንድ ወቅት ከፋርስ ሰዎች ጋር በተደረገ ጦርነት ብቻውን አሸንፏቸዋል፡፡ በዚህ ውጊያ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶ ሰይፍ ሰጠው፡፡ ፋርሶችን "በከንቱ ከምትጠፉ ወደ ሃገራችሁ ተመለሱ" ሲላቸው ተሳለቁበት፡፡ ከፈረሱ ወርዶ ወደ ምስራቅ ዙሮ ጸልዮ በመስቀል ካማተበ በኋላ በመካከላቸው እየተመላለሰ በመልአኩ ሰይፍ ፈጽሞ አጠፋቸው፡፡
ማር ቴዎድሮስ አንድ ቀን ወደ አንድ ከተማ ሲገባ 24 ክንድ የሚረዝም ዘንዶ ሲመለክና የአንዲት ክርስቲያን ልጆችንም ለመስዋዕትነት ሲያቀርቧቸው ተመለከተ፡፡ በፈረሱ ላይም እንዳለ በስመ ሥላሴ አማትቦ ዘንዶውን በጦር ገደለው፡፡ ከጊዜ በኋላ ስለ አባቱ ያለውን እውነታ ሲሰማ አፈላልጎ አገኘው፡፡ ሕይወቱ እስኪያልፍም አብሮት ቆይቶ ወደ አንጾኪያ ሲመለስ ክርስቶስ ተክዶ፣ ጣዖት ቁሞ፣ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለው፣ የክርስቲያኖች ደም ፈሶ፣ ከተማዋ በግፍ ተሞልታ ተመለከተ፡፡ ማር ቅዱስ ቴዎድሮስም በዚያች ሰዓት የክብር ልብሱን አውልቆ ባጭር ታጥቆ በንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ ፊት ቆሞ “እኔስ የክብር ባለቤት ክርስቶስን በፍጹም ልቤ አመልከዋለሁ፣ ለእርሱም ብቻ እሠዋለሁ::" አለ፡፡ ንጉሡም በቁጣ መሬት ላይ ጥለው እንዲደበድቡት አዘዘ፡፡ ወታደሮቹ ደሙ እስኪንጠፈጠፍ ገረፉት፡፡
ብዙዎች የሚመኙት ዓለማዊ ክብር ቢኖረውም ስለ ክርስቶስ ፍቅር ስጋን የሚያስመርር የተለያየ ስቃይ ሲያደርሱበት በደስታ ተቀበለው፡፡ በእሳት ሲያቃጥሉትም በጸሎቱ እሳቱን ውሃ አደረገው፡፡ ከበዛ ስቃዩም በእግዚአብሔር ኃይል ጸና፣ ታገሠም፡፡ በመጨረሻም ጌታችን በግርማ ወርዶ "ወዳጄ ቴዎድሮስ ስምህን የጠራ፣ መታሠቢያህን ያደረገ፣ ገድልህን ዜናህን የጻፈ፣ ያጻፈ፣ ያነበበ፣ ገዝቶ በቤቱ ውስጥ ያኖረውን ሁሉ እምርልሃለሁ፣ በስምህም ረድኤት ይደረጋል" ብሎት ዐረገ፡፡ ወታደሮቹ አንገቱን ሲሰይፉትም የክብር አክሊል ተቀብሏል፡፡ ተጋድሎውን አይተው ያመኑ እጅግ ብዙ ሺህ ሰዎችም አብረውት ተሰይፈዋል፡፡ ዓለምንና ክብራቸውን ስለክርስቶስ ፍቅር የናቁ ገዳማውያንም የጸሎታቸው በረከት ለብዙዎች ይተርፋል፣ የነፍስ ምህረት የስጋ ድህነት ያሰጣልና ገዳማቸውን እናግዝ በዓታቸውንም እናጽና፡፡
ድጋፍ ለማድረግ:- ሙትአንሳ ማር ቅዱሰ ሚካኤል አንድነት ገዳም
ኢትዮጲያ ንግድ ባንክ
1000442598391
ወይም
አቢሲኒያ ባንክ
141029444
የገዳሙ ስልክ ቁጥር:-0918077957 ወይም 0938644444