10/13/2025
መዝሙር 71
እሁድ ላይ እንደተለመደው ቤተ ክርስቲያን ነበርኩ ጥሩ ቀን አሳለፍን ፓስተራችንም ቀኑ የምስጋና ቀን ነበርና ስለምስጋና እየሰበከ ነው። እናም ለማጣቀሻነት የመረጠው አንድ ጥቅስ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ ሆነኝ ጥቅሷ ይህች ነች
"እኔ ግን ሁልጊዜ ተስፋ አደርግሃለሁ በምስጋና ላይ ምስጋናም እጨምራለሁ።" መዝ 71:14
ይህን አባባል ብዙ ጊዜ ሰምቼዋለው፣ በዝማሬም አውቀዋለሁ:: እናም ባለቅኔውን በምስጋና ላይ ምስጋና ለማምጣት ያነሳሳውን ለማወቅ ብዬ ቤቴ ገባው ይህ ክፍል (መዝ 71) ሙሉ መልሱ እንደሆነ እና በምስጋና ጫፍ ላይ ቆሞ የጸለየው እንደነበር ያስታውቃል። በውስጡም ምስጋናን በሁለንተናዊ መልኩ አሳይቷል በማሰብ፣ በመኖር፣ በመናገር እና በተለይ ከዝማሬ ጋር በሰፊው አያይዞ አቅርቦታል።
መዝሙር 71:22
"እኔም በበገና ስለ እውነትህ አመሰግንሃለሁ፤
የእስራኤል ቅዱስ አምላክ ሆይ፥
በመሰንቆ እዘምርልሃለሁ።"
ዘማሪው በዚህ ክፍል ብቻ በቀጥታ ከ ሰባት ጊዜ በላይ በተዘዋዋሪ ደግሞ ሶስት ጊዜ ያህል ጽድቅን ሲያጎላው አየሁ ገና ሲጀምር "በጽድቅህ ታደገኝ አስጥለኝም ይልና የጸሎቱን መጨረሻ ደግሞ "አንደበቴ ስለ ጽድቅህ ቀኑን ሙሉ ያወራል" ይላል። ይህችን በተለይ ሁለቴ ይደግማታል ስለዚህ የእርሱን ጽድቅ ማውራት፣ ስለእርሱ ማዳን ማሰብ እና በእዛው ህሳቤ ውስጥ መኖር፣ መዘመር እግዚአብሔርን ማመስገን እንደሆነ ተማርኩ። የእግዚአብሔር ሃሳብ ውስጥ መገኘት በራሱ ስራውን እንደማመስገን ነው ለካ።
ይህ ብቻ አይደለም "ጽድቅ" የጸሎትም፣ የአምልኮም የምስጋናም መጠቅለያ እንደሆነም መከረኝ። "አምላክ ሆይ ጽድቅህ እስከ ስማያት ይደርሳል ይልና አንተ ታላላቅ ነገሮችን አድርገሃል አምላክ ሆይ እንደ አንተ ያለ ማን ነው? እያለ ይጠይቃል። መዝ 71:19
ምስጋና እንደ አንተ ያለ ማን ነው? ለሚለው ጥያቄ ያለህ እውነተኛ መልስ እና የተደረገልህን ማሰብ ነው። ይህ ጥያቄ እንደ የሰው በብዙ መልክ ሊመለስ ይችላል...ግን ሌሎች ማድረግ የማይችሉት ለማንም ያልተሰጠ እና ብቻውን ይዞት ያለ አንድ ነገር "ፅድቅ" ይባላል።
እግዚአብሔርም ፅድቅን ለሰዎች ለማድረስ ያደረገውን እና የከፈለውን ያህል ታላቅ ነገር የለም። ይህ ዋጋ አንተ ጋር ሲኖር፣ በመዝሙር ስታቀርበው፣ በውሎህ ስትደገፈው እና በእውቀት ስታደርገው አምልኮ ይባላል። አምልኮ ስለ አምላክነቱ ፣ ስለስራው እና ስለውለታው ማሰላስል፣ መኖር፣ መዘመር፣ ማውራት፣ መጮህ እና የመሳሰሉትን በመተግበር ፅድቅን (ኢየሱስን) ማጉላት ነው።
የኔ የሁልጊዜ ምስጋናዬ
"አንደበቴ ስለ ጽድቅህ ቀኑን ሙሉ ስለ ማዳንህ ይናገራል ማቆሚያ ልኩንም አላውቅም።" መጥቼ የጌታ የእግዚአብሔርን ብርቱ ሥራ አውጃለሁ፣ የአንተንም ጽድቅ ብቻ እናገራለሁ። አምላክ ሆይ አንተ ከልጅነቴ ጀምሮ አስተማርኸኝ፣ እኔም እስከዛሬ ድረስ ድንቅ ሥራህን ዐውጃለሁ። (መዝ 71:15-17) ለዚህም ደግሞ አመሰግናለሁ
In Christ
Henok