03/26/2026
መሪነት ከፊት መቆም ብቻ አይደለም፤ ብርሃን ሆኖ መንገዱን ማሳየትም እንጂ!
በአመራር ዓለም ውስጥ ተቋማዊ ሽግግርንና እውነተኛ ለውጥን (Transformation) ማምጣት የሚቻለው መሪው ሥልጣኑን እንደ ዱላ ሳይሆን ውስጣዊ ማንነቱን እንደ ብርሃን ሲጠቀምበት ብቻ ነው። ይህ ጉዞ የሚጀምረው መሪው ሌሎች ገና ያላዩትን አድማስ ቀድሞ በሚያይበት ራዕይና ግልጽ ዓላማ ውስጥ ነው። መሪ ማለት "ወዴት እየሄድን ነው?" ለሚለው የብዙኃኑ ጥያቄ ትርጉም ያለውና የሚያነቃቃ ምላሽ መስጠት የሚችል ባለራዕይ ሲሆን ይህ ግልጽ አቅጣጫ በቡድኑ ውስጥ የሚፈጠሩ መዘናጋቶችንና ግጭቶችን በማስወገድ ሁሉም ወደ አንድ ግብ እንዲተም ያደርጋል። ራዕይ የሌለው መሪ እንደ ጨለማ መንገድ መሪ ነው፤ ራዕይ ያለው ግን የተከታዮቹን መንፈስ ቀስቅሶ ወደማይታሰብ ስኬት ይመራቸዋል።
የዚህ ሁሉ ስኬት መሠረትና የአመራር ቋጥኝ ደግሞ ታማኝነትና ሥነ-ምግባር ነው። መሪው የሚናገረውን የሚኖርና ማንም በማያየው ስውር ስፍራ እንኳ ሳይቀር እውነትን የሚከተል ሲሆን በሰዎች ዘንድ የማይናወጥ ተዐማኒነትን (Trust) ይገነባል። የግል ጥቅሙን ከጋራ ዓላማ በታች የሚያደርግ መሪ ተከታዮቹ ለውጡን በሙሉ ልባቸው እንዲደግፉና መስዋዕትነት እንዲከፍሉ የማድረግ ኃይል አለው። ያለ ታማኝነት የሚገነባ አመራር በአሸዋ ላይ እንደቆመ ቤት በመሆኑ ለውጥ አምጪ መሪ መጀመሪያ የራሱን ቃልና ሕይወት በማጽናት የተከታዮቹን ልብ ድል ያደርጋል።
በተጨማሪም በጭንቀትና በግርግር ወቅት የማይደነግጥ፣ የራሱንና የሌሎችን ስሜት በጥልቀት መረዳት የሚችል የስሜት ብልህነት (Emotional Intelligence) ለአንድ መሪ ወሳኝ መሣሪያው ነው። እንዲህ ያለው መሪ የሰዎችን ስጋትና ፍላጎት በአንክሮ የሚያዳምጥ በመሆኑ በቡድኑ ውስጥ ንትርክ ሳይሆን መግባባት የሰፈነበት የተረጋጋ የሥራ ድባብ ይፈጥራል። ይህ ባሕርይ ከውሳኔ ሰጪነት ባለፈ ሰብዓዊ ትስስርን የሚያጠናክር በመሆኑ ለውጥ የሚያመጣው ግፊት ከማስገደድ ሳይሆን ከመረዳዳት እንዲቀዳ ያደርጋል። ስሜቱን የሚገዛ መሪ ተቋሙን ከማዕበል የመታደግ ብቃት ይኖረዋል።
ለውጥ በባሕርይው ፈታኝና መሰናክል የበዛበት በመሆኑ መሪው የማይበገር ስብዕና ወይም ቁርጠኝነትና ጽናት ሊኖረው ይገባል። ከባድ ውሳኔዎችን ለመወሰን የማይፈራና ከውድቀት ተምሮ ዳግም የሚነሳ መሪ ተከታዮቹ ተስፋ በቆረጡበት ወቅት እንደ ዐለት ጸንቶ በመቆም ለቡድኑ ብርታትን ይሰጣል። ይህ ጽናት በችግር ጊዜ ሰዎችን አንድ አድርጎ የሚያቆይ ማጣበቂያ ሲሆን መሪው ለሚቆምለት ዓላማ ማንኛውንም ዋጋ ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን በተግባር ሲያሳይ ተከታዮቹም የእርሱን ፈር ተከትለው የማይቻለውን ተራራ ይወጣሉ።
በመጨረሻም እውነተኛ መሪ ሥልጣን የሚቀማ ሳይሆን ሥልጣን የሚያካፍል ሰዎችን የማብቃት ታላቅ ጥበብ ሊኖረው ይገባል። ዋነኛ ሥራው ተከታዮችን ማፍራት ሳይሆን መሪዎችን መቅረጽ በመሆኑ ለሰዎች ውክልና በመስጠትና ችሎታቸውን በማሳደግ ላይ ያተኩራል። መሪው ባይኖር እንኳ ተቋሙ በላቀ ሁኔታ የሚቀጥልበትን ተተኪነት የሚያረጋግጠው ይህ ባሕርይ ነው። ሀብትና ቴክኖሎጂ ተራ ቁሳቁሶች ሲሆኑ እነዚህን አስተባብሮ ታላቅ ውጤት የሚያመጣው ግን የሰዎችን ነፍስ ማንቀሳቀስ የሚችል መሪ ነው።
ዛዲግ አብርሃ
የአፍሌክስ ፕሬዝደንት