19/04/2026
ንጉስ ነጃሺ አክሱምና ዉቅሮ
✅✅✅✅✅✅✅✅
በአሕመዲን ጀበል፥ክፍል አንድ
🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴
ይህ ጹሑፍ በትግራይ ጦርነት ጊዜ የነጃሺ መስጂድ ላይ ጥቃት በተፈጸመ ጊዜ ተጽፎ በሦስት ተከታታይ ክፍሎች በኔ በአሕመዲን ጀበል የፌስቡክ ገጽ እእና የግል ፕሮፋይል ላይ በጃኑዋሪ 2፥ 2021 ተለጥፎ ነበር። ዛሬም በድጋሚ ሦስቱ ክፍሎች በተከታታይ ይቀርባል። መልካም ንባብ።
🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁
ነቢዩ (ሶ.ዐ.ወ) በእምነት ነጻነት፣ እጦት ጭቆናና መከራ ከባልደረቦቻቸው መከላከል እንደማይችሉ ሲገነዘቡ ወደ ሐበሻ ምድር እንዲሰደዱ መከሯቸው። እንዲህም አሏቸው፡-
‹‹ወደ ሐበሻ ተሰደዱ፤ በእርሷ አንድ ንጉሥ አለ። ከእርሱ ፊት ማንም ተበዳይ አይሆንም። … (ስለዚህ ተሰደዱ)፤ አላህ ካላችሁበት ሁኔታ አውጥቶ ድል እስክንጎናጸፍ ድረስ…፡፡››(ሙሐመድ ጦይብ ኢብን ሙሐመድ ኢብን ዩሱፍ፣ ኢትዮጵያ እና ኢስላም (ትርጉም)፣ ነጃሺ ማተሚያ ቤት፣ ገጽ 9)
ሰሀቦችም በሁለት ዙር ተሰደው ወደ ኢትዮጵያ-አክሱም መጡ፡፡በንጉስ ነጃሺ ዘንድ ነጻነትን ተጎናጸፉ፡፡ የነቢዩ ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) ባልደረቦች በሐበሻ የገጠማቸውን ሁኔታ እንዲህ ሲሉ መስክረዋል፡-
‹‹ሐበሻ ገባን። መልካም ጎረቤቶችንም አገኘን። በሃይማኖታችን ምክንያት የሚደረግብን ተፅእኖ አልነበረም። አላህንም በሰላም መገዛት ጀመርን። አንድም ችግርና መከራ አላጋጠመንም። የምንጠላውን ነገር አልሰማንም።››
(አህመዲን ጀበል፣ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ከ615-1700 የጭቆናና የትግል ታሪክ፣2003፣ገጽ 35)
መናገሻ ከተማውን አክሱም ከተማ አድርጎ ይመራ የነበረው ንጉስ ነጃሺ በኢስላም ኃይማኖት ታላቅ ስፍራ ከሚሰጣቸው ስብዕናዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ ለሙስናና የስጦታ ድለላ ሳይታለል የእምነት ነጻነትን ጨምሮ ሙሉ ነጻነትና ጥገኝነትን ለነቢዩ ሙሐመድን(ሰ.ዐ.ወ) ባልደረቦች በመስጠቱና በኃላ ላይም ኢስላምን ተቀብሎ ኦክቶበር/ኖቬምበር 630 (ረጀብ ወር 9ኛ ዓ.ሂ.) ሲሞት የርሱን ሞት መልዓኩ ጂብሪል ሲነግራቸው ለርሱ ነቢዩ(ሰ.ዐ.ወ) ለሞቱ ሙስሊሞች ላይ የሚሰገደውን ሰላትን ሰግደዋል፡፡
(ኢማሙ ጦበሪ፣ ታሪኽ አል ሩሱል ወል ሙሉክ፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 81፤ ኢብኑ ከሲር፣ አል-ቢዳያ ወኒሃያ፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 99፤ ኢብኑል አሲር፣ አል-ካሚል ፊ ታሪኽ፣ ጥራዝ 1፣ ገጽ 347)
አላህም ንጉሥ ነጃሺ ኢስላምን መቀበሉን በማረጋገጥ የሚከተለውን የቁርኣን አንቀጽ አወረደ፡-
وَإِنَّ مِنْ أَهْلِ الْكِتَابِ لَمَنْ يُؤْمِنُ بِاللَّهِ وَمَا أُنْزِلَ إِلَيْكُمْ وَمَا أُنْزِلَ إِلَيْهِمْ خَاشِعِينَ لِلَّهِ لَا يَشْتَرُونَ بِآيَاتِ اللَّهِ ثَمَنًا قَلِيلًا أُولَئِكَ لَهُمْ أَجْرُهُمْ عِنْدَ رَبِّهِمْ إِنَّ اللَّهَ سَرِيعُ الْحِسَابِ (سورة : آل عمران آية: 199)
ከመጽሐፉ ሰዎች መካከል አላህን ፈሪዎች፣ በአላህ አናቅጽትም ጥቂትን ዋጋ የማይሸምቱ ሆነው በአላህ የሚያምኑ፣ ወደ እናንተ የተወረደውንም ወደነርሱ የተወረደውንም (እውነት የሚቀበሉ) ወገኖች በእርግጥ ይገኛሉ። እነርሱ ከጌታቸው ዘንድ (የላቀ) ምንዳ ተዘጋጅቶላቸዋል። አላህ ምርመራው ፈጣን ነው። (ቁርኣን፣ዓሊ ኢምራን፣ 3፡199)
(ይህ የቁርኣን ጥቅስ የወረደው በነጃሺ ምክንያት መሆኑን በርካታ የኢስላም ሊቃውንት በመጽሐፍቶቻቸው አብራርተዋል። ለምሳሌ፡- ኢብኑ ከሲር፣ ተፍሲር አል ቁርአን አል ዓዚም፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 199፤ ኢማሙ ጦበሪ፣ ጃሚዑል